
“የጠቆሩ ልቦች”
ይቺ አጉል ዘመናይ፣ የወንዜ ልጅ እቱ
አፍሪካዊ መልኳ፤ “ደብሯት” ጥቁረቱ
ፊቷን በ“ሜክ አፕ” እጇን በእንሶስላ
ፀጉሯን ባንዳች ቀለም፣ ቀባችው ልትቀላ፡፡
ግን ባይገባት እንጂ፣ እንዲህ የምትደክም
እንዲህ የምትለፋ …
የቆዳችን ሳይሆን፣ የልባችን መጥቆር ነው አገር ያጠፋ፡፡
ሰለሞን ሽፈራው
“ተወራራሽ ሕልሞች” መጽሐፍ
ባለፈው “ሕልም እንኳ የታለ?” በሚል ርዕስ ላወጣነው ጨዋታ ምላሽ በመስጠት ጨዋታውን ላደመቃችሁት ዱባለ፣ በለው፣ inkopa እና Yekanadaw kebede ምስጋናችን እጅግ ከፍ ያለ ነው፡፡ በተለይ በዚህኛው አስደናቂ ቅኔዎችም ተዘርፈዋል፤ ወላድ በድባብ ተሂድና አገራችን አሁንም ባለቅኔዎችንና ጥበበኞችን እንዳላጣች እናንተ ምስክር ናችሁ፡፡ ክብረት ይስጥልን፡፡ ለዚህኛው ጨዋታ ደግሞ እስቲ ተቀኙልን! (ፎቶውን ያገኘነው ከፌስቡክ ነው፤ ባለቤቱ ካስታወቀን ዕውቅና እንሰጣለን)
^^^^^^^^^^^^^^^^^^
አይ ውበት ! አይ ድምቅት !
ተፈጥሮ ያደለሽ እንደ ማር ወተት
የጥቁር ውብ ቆንጆ የሀገሬ ወጣት
ማን ሊሥተካካለው ጥቁርን ሰውነት ?
የፀጉርሽ ላይ ጌጥ የአካልሽ ንቅሳት
የዓይኖችሽ ድምቅት የጥርስሽ ንፃት
ነጭን ስትደርቢ በጥቁር ሰውነት
እንዳያስመስልሽ ውሃ የገባች ድመት
ነጭ በጣም ይጎላል ጥቁርን ለማጥፋት
የቆዳሽን ጥቁረት ኩሪበት ኩሪበት
ልብሽን በፍፁም ከቶ እንዳታጠቁሪያት
ዓይንሽ በርቶ ጆሮሽ ነቅቶ ክብርሽን ጠብቂያት
ታላቅ በረከት ነው ኢትዮጵያዊነት !!
አህጉሪቱ አፍሪካም የመልከኞች ቤት ናት!።
^^^^^^^^^^^^^^^^^^^
“መልካም የክርስቶስ ልደት በዓል ለጋዜጣው ባለቤቶች አዘጋጆች ባለሙያዎችና ለተሳታፎዎች ለሁሉም የኢትዮጵያ ልጆች ሁሉ ሰላም ለእናንተ ይሁን ከምስጋና ጋር በቸር ይግጠመን !” ከሀገረ ካናዳ
የኔ የዋህ ገላ ግብግቡ አድክሞሽ
ቀለምሽን ለመሸሽ አልሸሽ ሲልሽ
ያለሺን መለወጥ ስትቸጋገሪ
ነጩን እንዳትጎጂው ፤ ከራስሽ እደሪ
ባለነጩ ቆዳ እንዴት እንዳጠላው ጠጉሩን ሲያከረድድ በጄል ሲለውሰው
የሽንብራ ማሳ መስሎ ሲያጋጊጠው?
አላየሽም እንዴ …..አፍሪካዬ ድንግል
የሌለን መናፈቅ የሁሉ ስራ ነው
ነጩ ራሱን ጠልቶ
ጸኃይ ላይ ተሰጥቶ
ጆሮውን በሳስቶ
ፊቱን ቀረዳዶ
በአዲስ ሞዴል ሂሳብ ሲንጎራደድልሽ?
የተፈጥሮሽ ውበት እርሱን አስክሮታል
ለመዘረፍ እሺ
ለመገደል እሺ
ለመታለብ እሺ ባልሽበት ቀን ሁሉ
ፍቅርሽ ፈገግታሽ ሰላምሽ ደንቆታል
የንቺን ነገር ወስዶ ባለው የመሰለው ተኮንኖበታል
እሱ የሸሸውን ፈልገሽ ስትሄጂ ፊትሽን ስታነጪ ተስፋው ይጨልማል
ራሱን እንዳጠላ መሄጂያ በማጣት በሃዘን ይሞታል፡፡
አደራ አፍሪካዬ ለሱ ብለሽ እንኩዋን ነጩን አትምሰይ
በነጭ ቆዳውስጥ ለመሸገው ሰይጣን
በጥቁር ቆዳውስጥ ያለው ውብ ብርሃን ይገለጥለታል
እየተጎተተ ከግርሽ ስር ይወድቃል
በጥቁር ቆዳ ውስጥ ነጭ ልብ እያየ ይሰለፍልሻል
እውነቱን ላስታውሺሽ ተጎጂ መርታቱን አለም ቀድሞም ያውቃል
Ethiochristian.net
ቀለም ቀቢዎቹ
ወሬ አቀባዮቹ
ጆሮና ዓይን ናቸው፤ ልብ ምን አጠፋ
ከጓዳ ሳይወጣ፤ሌት ከቀን በለፋ
አጭሩን ረጅም፤ጥቁሩን ነጭ ብለው
ለቅሶን በሙዚቃ ዘፈን አስመስለው
ከክተው፤ አቡክተው ካላቀረቡለት
ልብ ‘ልብ’ የለውም የሚመዝንበት
እንደዛሬ ዳኞች፤ነው የልብ ነገር
ጥላ ሲሉት መጥላት
አፍቅር ሲሉት ማፍቀር
ባይገባን ነው እንጂ ሁሉም ይወደዳል
ባመት በአል በደስታ ነጭ ይለበሳል
አንዳንዱም ሲፈልግ በጥቁር ይዋባል
ባግባብ ከተያዘ ሁሉም ቀለም ያምራል::
አናመሳስላቸው ጥቁርና ክፉን ስራ
ነጭም ጥላሸት ነው አጥፊ እንደ ኖራ
መታ መታ አርገው ሚያቦኑት እንደ አቧራ
ነጭ ሰው አያደምቅም በራሱ ካልኮራ
ውስጠ ባዶ ሆኖ መነፋት በጉራ
ያጋልጣልና ለባሰ መከራ::
ልክ እንደፊታችን
ቢነበብ ልባችን
ጨለማው ጓዳችን
የውስጡ ጥቀርሻ
የሌለው ማበሻ::
ይፋ ቢወጣማ!
ድብቁ ከተማ
ሽፍኑ ጉራንጉር
ሰው ያቆመው ነበር
ጠፈርን መመርመር
መሄድ እግዜር ሰፈር::
ጦርነት አቁሞ የዓለም ወታደር
ሃሳቡን ጊዜውን
ገንዘብና ዓቅሙን
ባዋለው ነበረ እዚህ ላይ ዕውቀቱን
ማንጣት በታገለ የጠቆረ ልቡን!