• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ከእሁድ እስከ እሁድ

January 14, 2013 06:41 am by Editor Leave a Comment

የላሊበላ ቅርስ አደጋ ላይ ነው

ታሪካዊና የኢትዮጵያ የጥንት የስልጣኔ አሻራ ምስክር የሆኑት ውድ የላሊበላ ውቅር አቢያተክርስቲያናትና ቅርሶች በመፈራረስ  ላይ መሆናቸው በተደጋጋሚ መጠቀሱ ይታወቃል። መንግስትም በተደጋጋሚ ቅርሶቹን ለማደስ እንደሚሰራ ማስታወቁም አይዘነጋም። በሳምንቱ መጨረሻ በስፍራው የተገኙ የተወካዮች ምክር ቤት አባላት “ስጋት አለን። ቅርሶቹ በመፈራረስ ላይ ናቸው” ሲሉ በመንግስት ቴሌቪዥን ተናግረዋል።

በተደጋጋሚ የላሊበላ ውቅር አቢያተ ክርስቲያናትና ውድ ቅርሶች የመፍረስ አደጋ እንደከበባቸው ቢገለጽም ምላሽ አለማግኘቱ አነጋጋሪ ሆኗል። መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ከሆነና የመንግስት ቴሌቪዥን ይፋ እንዳደረገው ታሪካዊዎቹ የኢትዮጵያ ልዩ መገለጫዎች የሚፈለጉት ለቱሪዝም ገቢ ብቻ ነው። በዓመት እስከ 40 ሺህ የሚደርሱ ቱሪስቶች ይጎበኟቸዋል። ከመቶ ሃያ ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ያስገባሉ።  ይህ ገንዘብ ብቻ በያመቱ ለቅርሶቹ እድሳት ቢውል እንደዚህ ላለ ታሪክን ሊያሳጣ የሚያደርስ አሳሳቢ አደጋ ላይ አይደረስም ነበር። የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ጉዳዩን አስመልክቶ ያለው ነገር የለም።

ለብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች የዲፕሎማሲ ስልጠና ተሰጠ   

ለአፍሪካ ዋንጫ ያለፈው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከቴክኒክ ስልጠና በተጨማሪ የፐብሊክ ዲፕሎማሲ ስልጠና እንደተጠተው በሸራተን አዲስ የሽልማት ስነስርዓት ላይ ተጠቁሟል። የመንግስት መገናኛዎች ተቀባብለው እንደዘገቡት የአባይ ግድብ የብሄራዊ ተሳትፎ አስተባባሪ በስልጠናው ላይ ተጨዋቾቹ ስለ አባይ ግድብ በማስተዋወቅና በመናገር የአገራቸው አምባሳደሮች እንዲሆኑ የሚያስችላቸውን “ግንዛቤ አስጨብጠዋል”፡፡

ተጨዋቾቹ በሚያገኙት አጋጣሚ በአገራቸው እየተካሄደ ስላለው ልማትና ስለ አባይ ግድብ ለሌሎች በማስተዋወቅ ከመጫወት በተጨማሪ የህዝብ ግንኙነት ስራ እንዲሰሩ አደራ ተሰጥቷቸዋል። አንድ ቀልደኛ የጎልጉል ሰው ኢትዮጵያ ሁለት ለባዶ ስትመራ ቆይታ ሁለት ለሁለት ጨዋታው ተጠናቆ ጎሎቹን ያገባው ተጨዋች ጋዜጣዊ መግለጫ ስጥ ቢባል “በምሳሌ አስረዳለሁ። አንድ ሁለት መቶ ብር የነበረው ሰው አንድ መቶብር ለአባይ ግድብ፣ አንድ መቶ ብር ለአዲስ ራዕይ ግዢ ቢያውል ምን ይተርፈዋል? ምንም። ስለዚህ ውጤቱ እንዲሁ ይመስላል” በማለት ልማቱንና ውጤቱን በማያያዝ ሊመልስ እንደሚችል ተናግሯል። በነገራችን ላይ የተለያዩ የኢንሹራንስ ኩባንያዎች 20 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ የጉዞ ኢንሹራንስ ገዝተዋል።

በጣና ሃይቅ ግድያ የፈጸሙ ተያዙ

ፖሊስ ተራ ሌቦች ናቸው ብሏል

ባለፈው ሳምንት በመዝናናት ላይ ከነበሩ ቱሪስቶች መካከል አንዱን ተኩሰው ገድለዋል የተባሉት ሶስት ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የአማራ ክልል ፖሊስ አስታውቋል። ኮማንደር እርቅ ይሁን ለኢቲቪ በሰጡት መግለጫ እንዳመለከቱት ወንጀሉን ፈጽመዋል የተባሉት ተጠርጣሪዎች የተያዙት በ48 ሰዓታት ውስጥ ነው። ለጊዜው ያመለጡት ሁለት ተፈላጊዎች ህዝብና የጸጥታ ሃይሉ በረሃ ገብተው እያሰሱዋቸው ስለሆነ በርግጠኛነት በቁጥጥር ስር እንደሚውሉ ኮማንደሩ ተናግረዋል።

የክልሉ ፖሊስ ምክትል ኮሚሽነር በበኩላቸው ድርጊቱን ለጊዜያዊ ጥቅም የተፈጸመ እንደሆነ ተናግረዋል። የክልሉን ገጽታ እንደማያበላሽ የጠቆሙት ኮሚሽነሩ፣ የተቀሩትን ባስቸኳይ በቁጥጥር ስር በማዋል አስፈላጊው የህግ ውሳኔ ተሰጥቶበት ለህዝብ ይፋ እንደሚሆን አስታውቀዋል። ተጠርጣሪዎቹ ሲያዙ በጃቸው ላይ 5,700 የኢትዮጵያ ብር፣ 150 ዩሮና ፓስፖርትና ተይዞባቸዋል።

አበበ ገላው ማለት “እኛ ነን”

አበበ ገላውና ሲሳይ አጌና

በጋዜጠኛ አበበ ገላውን ለመግደል በዝግጅት ላይ የነበሩ ቅጥረኞች የተሰጣቸውን የቤት ስራ ሳያከናውኑ እንደተደረሰባቸው መገለጹን ተከትሎ ጉዳዩ የበርካቶችን ቀልብ ስቦ ሰንብቷል። ኢሳት በሰበር ዜና በአሜሪካ ሀገር የፖለቲካ ጥገኝነት ጠይቆ የሚኖረውና የህወሃት ሰላይ ይሆናል ተብሎ እንደሚታመን በስም ጠቅሶ እንደዘገበው፣ ይኽው ግለሰብ ጋዜጠኛ አበበን ለመግደል ሶስት የወንጀሉ ተባባሪ የሚሆኑ ግለሰቦችን መመልመሉ ተደርሶበታል። የግድያውን ሴራ የFBI መሪማሪዎች ደርሰውበት እንዳከሸፉት የተነገረለት ይህ ከፍተኛ የወንጀል ድራማ በአገርቤትና በውጪ አገር የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንን አስቆጥቷል።

ጋዜጠኛ አበበ ገላውን በመደገፍና በማበረታታት በተለያዩ ማህበራዊ ገጾች በርካታ ጽሁፎች የተበተኑ ሲሆን “አበበ ማለት እኛ ነን” የሚል ይገኝበታል። የግድያ ሙከራውን በማውገዝ ሞረሽ የሚባለው የአማራ ተቆርቋሪ ነኝ የሚለው ማህበር  ድርጊቱ “በአማራ ነገድ ላይ ያነጣጠረ ነው” በማለት ያወጣውን መግለጫ አበበ እንዳልወደደው አስታውቋል። አበበ ኢትዮጵያዊነት እንጂ ወደ አንድ ብሔር የመጠጋጋት ጉዳይ አጀንዳው እንዳልሆነ በይፋ የገለጸበት ጽሁፍ በተለያዩ ድረገጾች ተላልፏል። FBI ደርሶበት አከሸፈው ስለተባለው የግድያ ሙከራ ከህወሃትም ሆነ፣ ህወሃት ከሚመራው ኢህአዴግ በኩል እስካሁን የተባለ ነገር የለም።

ከጅቡቲና ከጎዴ ቅድሚያ ለማን

በሶማሌ ክልል የጎዴ ከተማ የመብራት አገልግሎት የምታገኘው ከጄኔሬተር መሆኑን የከተማዋ ከንቲባ አስታውቀዋል። ከንቲባው እንዳሉት በከተማዋ ያለው የኤሌትሪክ ችግር እንዲቀረፍ ባለሃብቶችና ነዋሪዎች እየጠየቁ ነው። ስለከተማዋ ልማት በኢቲቪ የዜና እወጃ ላይ ቀርበው የተናገሩት ከንቲባው የመስመር ዝርጋታው በቅርቡ ጎዴ ይደርሳል የሚል እምነት እንዳላቸው አመልክተዋል። ኢትዮጵያ ወደ ጅቡቲና ሱዳን የኤሌክትሪክ ሃይል መሸጥ መጀመሯ ይታወሳል።

በሌላ በኩል በክልሉ በተከሰተ ረሃብ ከብቶቻቸው የሞቱባቸው፣ ግመሎቻቸውን ያጡና በከፍተኛ ደረጃ የተጎዱት አርብቶአደር የጎዴ ነዋሪዎች ራሳቸውን እንዲችሉ በተደረገው ጥረት የኮብል ድንጋይ ማዘጋጀት ጀምረዋል። በኮብል ድንጋይ የሚሰራ መንገድ በመስራት ገቢያቸውን አሳድገዋል። ይህ ጅምር ወደፊትም ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ከንቲባው አስታውቀዋል።

ዓለም ባንክ ቴሌን ዳር ዳር እያለው ነው!

የዓለም ባንክ ባለፈው ዓርብ ይፋ ባደረገው ጥናት የቴሌኮም ዘርፉ ለከፍተኛ ሙስና አደጋ የተጋለጠ መሆኑን ሲያረጋግጥ፣ በተለይ በግዥና በአቅርቦት ሒደቶች የሚታዩት ክፍተቶች ለሙስና አደጋ በመጋለጥ ከፍተኛውን ድርሻ ይዘዋል ተብሏል፡፡

መንግሥት ከባንኩ ጋር ባደረገው ስምምነት መሠረት የባንኩ አጥኚ ቡድን የአገሪቱን የሙስና መጠን ለስድስት ወራት ያህል ሲያጠና ቆይቷል፡፡ ጥናቱ የተካሄደባቸው ስምንት ዋና ዋና ዘርፎች ሲሆኑ፣ በአብዛኞቹ ዘርፎች ላይ የሙስና መንሰራፋት ያን ያህል አሳሳቢ በሚባል ደረጃ ላይ አይደለም ብሏል፡፡ ሆኖም ጥናቱ “አዳዲስ የኢንቨስትመንት ዘርፎች” ብሎ በመደባቸው ንዑሳን ክፍሎች ውስጥ የተካተቱት ቴሌኮም፣ የኤችአይቪ/ኤድስ መከላከልና ሕክምና እንዲሁም የመድኃኒት ዘርፉ በሙስና ቀለበት ውስጥ የወደቁ መሆናቸውን አመላክቷል፡፡

ጥናቱ በአጠቃላይ የአገሪቱን ስምንት ዋና ዋና ዘርፎች በሦስት ክፍሎች መድቧቸዋል፡፡ “የመሠረታዊ አገልግሎት ሰጭ ዘርፎች”፣ “አሮጌዎቹ ዘርፎች”፣ እንዲሁም “አዳዲስ የኢንቨስትመንት ዘርፎች” በማለት የመደባቸው ሲሆን፣ አዳዲስ ኢንቨስትመንት ዘርፎች ውስጥ የተካተቱት፣ ከፍተኛ ፈንድ የሚጎርፍላቸው ከመሆናቸው ባሻገር ከሌሎቹ ዘርፎች አኳያ በአገሪቱ ያላቸው ተሞክሮ አነስተኛ ሆኖ የሚገኙ ናቸው፡፡

በመሠረታዊ የአገልግሎት ሰጭ ዘርፍ ውስጥ የተካተቱት እንደጤና፣ ትምህርት፣ ፍትሕና የመሳሰሉት ናቸው፡፡ በአሮጌው ዘርፍ ውስጥ ደግሞ እንደ ማዕድን፣ ኮንስትራክሽን፣ መሬትና ሌሎችም ተደልድለዋል፡፡

የባንኩ የጥናት ውጤቶች እንደሚያመለክቱት፣ በመሠረታዊ አገልግሎት ሰጭ ተቋማቱም ሆነ በአሮጌዎቹ ዘንድ የሚታየው የሙስና ደረጃ ያን ያህል አደገኛ ሁኔታ ውስጥ የሚገኝ አይደለም፡፡ ምንም እንኳ በዘርፎቹ የሚታየው የሙስና መጠን እያደገ ቢመጣም፣ ህልውናቸውን እንደማይፈታተነው ጥናቱ አመላክቷል፡፡ በተለይ የመሠረታዊ አገልግሎት ዘርፉ ከሌሎቹ አኳያ ለሙስና ያለው ተጋላጭነት አነስተኛ ሆኖ ይታያል፡፡

ከዚህ ይልቅ አሮጌዎቹ ዘርፎች ለሙስና ያላቸው አስተዋጽኦ ከአዳዲሶቹ ቀጥሎ ያስቀምጣቸዋል፡፡ በተለይ የቴሌኮም ዘርፉን በመከተል መሬትና ኮንስትራክሽን በሙስና አደጋ ውስጥ ቢገኙም፣ የትኞቹም የቴሌኮም ዘርፉን ያህል ግን አይደሉም፡፡

ከጥቂት ቀናት በፊት “ቴሌን ደህና ሰንብት?” በሚል ርዕስ ባወጣነው ዜና ላይ ቴሌ የአውሮጳውያንን ኩባንያዎች ማግለሉና በሙስና የተዘፈቀ ድርጅት መሆኑ ጠቅሰን መዘገባችን ይታወሳል፡፡ (ከላይ የተጠናቀረውን ዜና በቀጥታ የወሰድነው ከሪፖርተር ነው)

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: News Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • አዲሱ የቴድሮስ ካሳሁን 888 ኮድ፤ እንደ 666?! April 15, 2026 05:53 am
  • ምኑ ነው ያሳቃችሁ፤ ያስደሰታችሁ? April 2, 2026 10:52 am
  • የጀዋር መሃመድ የፖለቲካ ማንነት እና የባዕዳን ተልዕኮ April 2, 2026 10:16 am
  • ከግብፅ በዳያስፖራ ትርምስ ጠማቂዎች በኩል ፋኖ ወደ አዲስ አበባ የላከው “ስጦታ” March 27, 2026 09:14 am
  • “ሰላማዊ ታጋዮቹ” እነ ልደቱ ከአራጁ ሸኔ ጋር ተጣምረዋል March 25, 2026 01:04 pm
  • ጸረ-ኢትዮጵያዊ የሆነው የሪፖርተር አዘጋገብ March 19, 2026 11:54 am
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ የኦሮሚያ የልማት ድርጅቶች March 18, 2026 10:48 am
  • የጃኖ ስጦታና የዶሮ ፖለቲካ በጎንደር March 10, 2026 09:24 am
  • “አዲሷ” ኢህአፓ፤ ከንፈሯን ቀለም የተቀባች አሳማ February 25, 2026 11:24 am
  • የተንጋደደው የገዱ መልስ February 6, 2026 03:05 pm
  • ሻዕቢያ “አክሱም ገብቶ ወጣቶች በጅምላ ሲረሽን ጸብ ተፋፍሟል …” February 4, 2026 01:15 pm
  • አደራ ጠባቂው የኢሉአባቦር ሕዝብ February 4, 2026 12:14 pm
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን January 28, 2026 09:56 am
  • በአሜሪካ ጥምር ዜግነት እንዲቀር ጥያቄ ቀረበ January 27, 2026 03:05 pm
  • “ከህወሓት፣ ከሻዕቢያ፣ ከግብፅ ሰዎች ጋር ሆኖ እንዴት የአማራን ጥያቄ ማስመለስ ይቻላል?” ኮሎኔል ፈንታው January 25, 2026 04:23 am
  • የኢትዮጵያ አየር ኃይል: ለአፍሪካ ሀገራት የመጀመሪያዎቹን የአየር ኃይል አብራሪዎች ያሰለጠነ ተቋም January 25, 2026 03:50 am
  • የአማረ ሪፖርተር እያደረሰ ያለው የብሔራዊ ደኅንነት አደጋ January 22, 2026 01:56 am
  • የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የማርያምን ማዕረግ ዝቅ አደረገች December 12, 2025 09:27 pm
  • ኢህአፓ: ከነጭ ሽብር ወደ “አዲስ አበባ ትናገር” የጎዳና ሽብር? December 12, 2025 09:11 pm
  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule