
ላለፉት ሁለት ቀናት መቀሌ መሽጋ ስትንጫጫ የቆየችው ህወሓት እነ ዓቢይ አህመድን ለመገምገም ስብሰባ ይጠራልኝ ብላ መግለጫ አውጥታለች። የዛሬውን አያድርገውና ዱሮ በፈለገችው ጊዜና ሰዓት ስብሰባ ስትጠራ የኖረችው ህወሓት ለዚህ መብቃቷ ክስረቷን ማሳያ ተደርጎ ተወስዷል።
ህወሓት ይህንን ስትጠይቅ የሚከተሉትን መሠረታዊ ውሳኔዎች በመቀበል ነው፤
ኢትዮጵያ ህዝብታት ወያናይ ዴሞክራሲ ግንባር (ኢህወዴግ) ወይም በአማርኛ ኢህአዴግ፤
- “የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ሙሉ በሙሉ ወይንም በከፊል ለመሸጥ ያስተላለፋቸውን ውሳኔዎች” እንደምትቀበል፤
- “የኢትዮ ኤርትራን የድንበር ኮሚሽን ውሳኔና የአልጄርሱ ውይይት በሚመለከት የተላለፈውም ውሳኔ ከአገሪቱ የሰላም ፖሊሲ ጋር የተጣጣመ በመሆኑ ተገቢና ወቅታዊ ነው”
ካለች በኋላ ነው ህወሓት እነ ዓቢይ ይገምገሙልኝ ስትልት ስብሰባ እንዲጠራላት በአክብሮት የጠየቀችው። ከዚህም ሌላ ህወሓት በኢህወዴግም ውስጥ ይሁን በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ውስጥ የነበረኝ ሥልጣኔ ተሸርሽሯል፤ ከፍቶኛል ብላለች። የሪፖርተሩ ብሩክ አብዱ የዘገበው እንዲህ ይነበባል፤
የሕዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) ማዕከላዊ ኮሚቴ ረቡዕ ሰኔ 6 ቀን 2010 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴን ለመሠረታዊ የኢኮኖሚ ችግር ጊዜያዊ መፍትሔ ላይ ከማተኮር ይልቅ ዘላቂ መፍትሔ ሊሰጥ ይገባ ነበር ሲል ወቀሰ።
ሕወሓት በመግለጫው፣ “የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ማየት የነበረበት መሠረታዊ ጉዳይ አሁን ገጥሞን ላለው የኢኮኖሚ ችግር ዘላቂ መፍትሔ ማፈላለግ መሆን ሲገባዉ፣ ችግሩ ባስከተላቸው ውጤቶችና ለጊዚያዊ መፍትሔዎች ቅድሚያ መስጠቱ አንድ ጉድለት እንደሆነና፣ ዘላቂው መፍትሔ ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ መስመራችን በግልጽ የለያቸውን የልማት አቅሞቻችን፣ ማለትም መላው ሕዝባችን፣ መንግሥትና የግል ባለሀብቱን በማደራጀት ርብርብ እንዲያደርጉ ትኩረት መስጠት አልቻለም፤” ብሏል።
ድርጅቱ ለሁለት ቀናት ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባም የኢሕአዴግ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ትላልቅ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ሙሉ በሙሉ ወይንም በከፊል ለመሸጥ ያስተላለፋቸውን ውሳኔዎች እንደሚቀበል፣ ነገር ግን አፈጻጸሙ ላይ ውይይትና ጥንቃቄ መደረግ እንዳለበት አስታውቋል።
የኢትዮ ኤርትራን የድንበር ኮሚሽን ውሳኔና የአልጄርሱ ውይይት በሚመለከት የተላለፈውም ውሳኔ ከአገሪቱ የሰላም ፖሊሲ ጋር የተጣጣመ በመሆኑ ተገቢና ወቅታዊ ነው ብሏል። “አፈጻጸሙን በሚመለከት ግን አገራችን ከሌሎች ጎረቤት አገሮች ጋር ካሏት የአዋሳኝ ድንበር ጉዳዮች አንፃር ጭምር እጅግ ከፍ ያለ ትርጉም ያለዉ በመሆኑ፣ በከፍተኛ ጥንቃቄ ሊታይ እንደሚገባዉ አፅንኦት ሰጥቶ ተወያይቷል፤” ሲል አስታውቋል።
ይሁንና ማዕከላዊ ኮሚቴው፣ “በኢትዮ ኤርትራ ዘላቂ ሰላም ጉዳይም ሆነ ከመንግሥት የልማት ድርጅቶች ጋር በተያያዘ የተወሰኑ ውሳኔዎች ወደ ኢሕአዴግ ምክር ቤት ሳይቀርቡ፣ አጋር ድርጅቶች ሳይሳተፉበትና የሚመልከታቸው አካላት በዝርዝር ሳይወያዩበት እንደመጨረሻ ውሳኔ ተወስዶ ለሕዝብ ይፋ መደረጉ አንድ ጉድለት እንደሆነ ማዕከላዊ ኮሚቴዉ ደምድሟ፤” ሲል በመግለጫው አትቷል።
ድርጅቱ አክሎም፣ “በአሁኑ ወቅት በኢሕአዴግ ደረጃ እየተደረጉ ያሉ የኢሕአዴግን ሕገ ደንብና ተቋማዊ አሠራር ያልተከተሉ የአመራር ምደባዎች እንዲታረሙ የሕወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ይጠይቃል፤” በማለት፣ “ወቅታዊ ሁኔታውን በፍጥነት ለማየትና ለመገምገም የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴና ምክር ቤት አስቸኳይ ሰብሰባ እንዲጠራ የሕወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ይጠይቃል፤” ብሏል።
****
የህወሓት ውሳኔ ይህ ቢሆንም ባድመን ለኤርትራ ተላልፋ እንድሠጥ ያደረገውን እና ሕዝብን የዋሸውን ስዩም መስፍንን፤ ስምምነቱን በፈቃዱ ሄዶ የፈረመውን መለስ ዜናዊን እንዲሁም ይህንን በማስፈጸም እነዚህንና መሰል የአገር ክህደት ከፍተኛ ወንጀል የፈጸሙ ግለሰቦችን ከነድርጅቱ ለፍርድ ማቅረብ የትግራይ ሕዝብ ቀዳሚ ኃላፊነት እንደሆነ አስተያየት ሰጪዎች ይናገራሉ።
ጎልጉል፤ የድረገጽ ጋዜጣ
ውነት ነው! በመጀመሪያ አገር የሸጠውና የለወጠው የትግሬ ወያኔ ለፍርድ ይቅረብ። አገር ሻጭና ለዋጭ ምን የሞራል ብቃት አለው ዶ/ር አብይን ሰበሰባ እንዲጥራ የሚጠይቀው …? መጀመሪያ ትግሬ ወያኔ የሸጥውን ባድመን ከእነ ወለዱ ክፈል።
ኢትዮጵያ እንደ አንድ ሉዓላዊ አገር ድንበር የላትም!
እንደ ሕገ መንግሥቱ ባድመም ጾረናም የትግራይ ክልል ጉዳይ ብቻ ነው፡፡
(ውብሸት ሙላት)
የፌደራሉ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ ሁለት ላይ እንደተገለጸው የአገሪቱ የግዛት ወሰን (ድንበር) የክልሎቹ ወሰን ነው፡፡ ሕገ-መንግሥቱ ሲረቀቅ ይሄም አንቀጽ በዚህ መልኩ መደንገግ እንደሌለበት፣ኢትዮጵያም እንደሌሎች ሉዓላዊ አገራት ሁሉ፣ የራሷ የሆነ ዳር ድንበርና አዋሳኞች ሊኖሯት እንደሚገባ ክርክር እንደነበር ከተለያዩ ሰነዶች መረዳት ይቻላል፡፡
የኢትዮጵያ ድንበር ሳይቀር የሚወሰነው በክልሎች ሕግጋተ መንግሥት ነው እንደማለት ነው፡፡ በዚህ መሠረት ሁሉም ክልሎች አዋሳኞቻቸውን ብሎም ድንበራቸውን የደነገጉ ቢሆንም የደቡብ ብሔሮች፣ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ሕገ መንግሥት ግን የክልሉ ወሰን የዞኖቹ እና የወረዳዎቹ ነው በማለት ደንግጓል፡፡
ይሁን እንጂ እንኳንስ ወረዳ እና ዞን ይቅርና ከልሎችም ከሌሎች ሉዓላዊ አገራት ጋር ዓለም አቀፍ ስምምነቶችን መዋዋል ስለማይችሉ ይህ ዓይነቱ በክልል፣በዞን እና በወረዳ የኢትዮጵያን የግዛት ወሰን በተለይም ከሌሎች ሉዓላዊ አገራት ጋር የምትዋሰንባቸውን ድንበሮች መለየት ለአፈጻጸምም አስቸጋሪ ነው፡፡
ክልሎቹ ከሉዓላዊ አገራት እና ከሌሎች ክልሎች ጋር ይዋሰናሉ፡፡ ከሌሎች አገራት ጋር በሚዋሰኑበት ጊዜ ጉዳዩ ዓለማ አቀፍ ሲሆን፣ ከሌላ ክልል ጋር በሚዋሰኑበት ድንበር ምክንያት የሚነሱት ጉዳዮች ደግሞ የፌደራል ይሆናሉ፡፡ ከዚህ በተቃራኒው፣ ድንበርን በተመለከተ ጥቅልል አድርጎ የክልል ማድረግ ተጠየቃዊ አይደለም፡፡
ኢትዮጵያ እንደ ፌደሬሽን ግዛቷ (territory) የክልሎቹ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ነገር ግን፣ የግዛት ወሰኗ ደግሞ በጥቅሉ የክልሎቹ ሳይሆን ክልሎቹ ከሌሎች ሉዓላዊ አገራት ጋር ያላቸው ድንበር (border or boundary) ነው፡፡ ስለሆነም፣ ክልሎቹ ከሌሎች አገራት ጋር የሚዋሰኑበትን የድንበር አከላለል እና ተያያዥ ጉዳዮች በፌደራሉ መንግሥት ሥልጣን ሥር እስካልሆኑ ድረስ ሁኔታዎቹን የበለጠ ውስብስብ ያደርጋቸዋል፡፡
የፌደራሉ ሕገ መንግሥቱ ላይም ይሁን የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ላይ እንደተገለጸው ከሆነ የባድመም ይሁን በጾረናና ሌሎች የትግራይ ክልል ከኤርትራ ጋር የሚዋሰኑባቸው አካባቢዎችን የሚመለከተው ክልሉንና ኤርትራን ብቻ ነው እንደማለት ነው፡፡ ወለፈንድ (absurd) የድንበር ሕግ!!!!
እንደዚህ ዓይነቶቹ የሕገመንግሥት አንቀጾች ካልተሻሻሉ ወደፊት በርካታ ውስብስ መዘዝ ሊያስከትል ይችላል፡፡ ሊያስከትል የሚችላቸውን መዘዞች ለጊዜው እንተወው፡፡ ቢያንስ ግን ለአገራዊ ግንባታ ደንቀራ ነው፡፡ መሻሻል ይገባዋል፡፡