![](https://www.goolgule.com/wp-content/uploads/2016/08/selfd.jpg)
ይድረስ ለእኛ-ከእኛ! – ከላይ ልጀምር ካ’ናቱ፣
በብረት ኃይል ተከቦ – ከተኮፈሰው በከንቱ፣
ይድረስልኝማ ለወያኔ – ለጊዜያዊው ባለጉልበቱ፤
… “ለሕዝባዊነት መጣሁ” ብሎ – ሕዝብን በጥይት መቁላት የለምና፣
አቆልቁለህ እየውማ – የምትሄድበትን ጎዳና!
የጭካኔ መጠንህ ጫፍ ደረሰ – የውሸት ቋትህ ሞላ፣
የ’እውቀት‘ ገደብህ አበቃ – ከእንግዲህ ላይኖርህ የቀረ ‘መላ’፣
ከወደቁ ወዲያ መንፈራገጥ.. እንዳይሆን ለመላላጥ፣
ሳሩንም ላለመጋጥ.. መሬቱንም ላለመናጥ…፣
ከአውሬነት ባህል ተላቆ – ሰውነትን ይሻልና፣
ይድረስ! ይድረስ! እልሃለሁ፤ ይድረስ! እንደገና፤
ዛሬ እንኳን እንደማመጥ – ይቅርብህማ ወንድሜ፣
በግፍ ተሞልተህ ጉዞ – ላይሆንህ መልካም ዕድሜ፣
“አበቅቴ ውሉን ሳይስት” – የአመሻሽ ጀንበር ሳትጠልቅብህ፣
ቆም ብለህ ማሰብ ጀምር – እንደ “ጆቤ”ህ፣ እንደ “ፃድቃን”ህ!
ይድረስ ለወንድማችን! የወገንህን ስቃይ ለምታራዝም፣
አውቀህም ሆነ፣ ሳታውቅ – ለጥቃቅን ጥቅማ-ጥቅም፣
ለሀላፊና ጠፊ – አብሮህ ለማይኖር ቁስ፣
ህሊናህን ለምትዳርግ – ለማይድን የጸጸት ውርስ፣
ለዘር ማንዘርህ ‘ለሚተርፍ‘ የስም ስብራት “ቅርስ”፤
ይድረስ ለእህታችን! የወገንሽን ጭንቅ ለምታበዢ፣
አውቀሽ እንደዘበት፣ ሳታውቂ በስህተት ለምትናውዢ፣
በልጦ ለመገኘት፣ በምትከውኚው ድርጊት-ሃላፊ፣
የማያልፍ ክፉ ስም ተክለሽ – ሳትጠቀሚ ለምታልፊ፣
የትውልድ እናት ሆነሽ – የስምሽን ክብር ለምታጎድፊ፤
ይድረስ ለእኛ-ከእኛ!
ሕዝብ በመዶሻ ሲቀጠቀጥ፣ ምስማር ለምናቀብል ከንቱ፣
የዘረኝነት አጥሩን ሲያጥር፣ ማገር ለሆንን ለስርዓቱ፣
የጭቆና መረቡን ሲዘረጋ፣ እየተጋገዝን ለምንተበትብ፣
አስተዋጽዖ ለምናደርግ፣ ለከፋፍለህ ስልቱ ግብ፤
ለ”ልማታዊ መንግስት” ፌዝ፣ ለዘረኝነት “ፌዴራሊዝም”፤
ኃይል፣ ጉልበት ሆነን፣ እድሜውን ለምናራዝም፤
በ”ላም አለኝ በሰማይ..ቤት”፣ በአፓርትመንት ተስፋ፣
ዶላር ለምናፈስለት፣ ጨቋኝ እንዲደልብ፣ እንዲፋፋ፣
ይድረስ ለእኛ!
በመሃላ፣ በጩኸት..፣ ባደባባይ፣
“ክርስቲያን” ነኝ፣ “ሙስሊም” ነኝ ባይ፣
በማዕረግና ቅጽል ብዛት አይደለም እምነቱ፣
በቂምና በሸፍጥ አይደለም ስግደት፣ ጸሎቱ፤
መስጂድ፣ ቤተ-ክርስቲያን.. እምናምስ፣
የመለኮት ጸጋ ማደሪያውን እምናረክስ፣
በኢ-አማኝ መሰሪዎች ሴራ፣ ጽላተ-ታቦቱን እምንከስ፣
የእምነት መሰረተ-ስርዓቱን፣ ዶግማ-ቀኖና እምናፈርስ፣
መቅሰፍት መጥራት ነው በራስ፣ ቅስፈት መመኘት ነው ለሀገር፣
የዘላለም ዓለም እሳት፣ እማይበርድ የሲዖል ጣር፤
ይድረስ ለእኛ!
“መሬት እሰጣችኋለሁ..” ሲል፣ በካሬ ሜትር መትሮ፣
ከየት አምጥቶ? ብለን ብንጠይቅ፣ ባለቤቱን በግፍ አባሮ፤
ከጉልበተኞች ተጠግቶ — ተገን የሌለውን ደሀ ገፍቶ፣
የሚያለቅሱ ህጻናትን እምባ — በግፍ ረግጦ የተገነባ፣
በሞራል፣ በህግም፣ በኃይማኖት — ከቀማኛ ሌባ ተሻርኮ መብላት፣
ያስጠይቃል ጊዜው ሲደርስ — ሀገር ለባለሀገሩ ሲመለስ፤
ከስማችንም፣ ከገንዘባችንም ሳንሆን በከንቱ እንዳንቀር፣
እናም ጎበዝ! እናስብበት፣ ጊዜው ሳያልፍ እንምከር።
ይድረስ ለእኛ!
ሳይማር ላስተማረን — ወርቅ፣ አልማዝ ላበደረን፣
ምላሻችን አይሁን ጠጠር — የበላንበትን ወጭት አንስበር፤
ለፍትህ፣..ለነጻነቱ፣ ሕዝብ የሚያደርገውን ወሳኝ ትግል፣
በአእምሮ ድህነት ተጠፍረን፣ ማገዝ እንኳን ባንችል፣
እኛ ከዋናው ጠላቱ ብሰን፣ ጉሮሮው ላይ አጥንት አንሰንቅር፤
የፈሪ ዱላችንን እንደታቀፍን፣ ባይሆን “መሃል እንስፈር”፤
የ”እሱ” ክፋት መች አነሰና፣ ሀገር እሚያቃጥል በሰበብ-አስባብ፣
ለእሳት ቤንዚን ከማቀበል፣ ከእኩይ ተግባር እንታቀብ፤
ማስጣል እንኳ ቢያቅተን፣ የጊዜ ምስጢር ዘማ፣
በ”ያባትህ ቤት ሲዘረፍ..” ብሂል፣ አገራችንን አናድማ!
ይድረስ ለእኛ!
አመንዣጊ ለሆንን እንደ ጌኛ፣
በሆዳችን ለምናስብ፣
ለማይመስለን በልተን እምንጠግብ፤
ከረሃብተኛ ጉሮሮ ነጥቀን፣ በጠኔ ከደከመ ጨቅላ፣
ህሊናችንን ሸፍነን፣ ሆዳችንን ለምንሞላ፣
በዛሬ ብቻ “አስረሽ-ምችው”፣ የትውልዱን ነገ ለምናጨልም፣
ትርፍራፊያችን እንኳ እንዳይቀር፣ በክፋት ለውሰን ለምናወድም፤
ይድረስ ለእኛ!
ውጭም ሆነ-ውስጥም ላለን፣
ለቅንጥብጣቢ ስጋ፣ እንደውሻ ለሚጣልልን፣
ከደሀ አፍ ተነጥቆ፣ ዳረጎት ለሚሰፈርልን፣
ለደረቅ ፍርፋሪ እንጀራ፣ ተበልቶም ለማያጠረቃ፣
በወገን ቁስል ላይ፣ እንጨት መስደድ ያብቃ!
ይድረስ ለእኛ – ከእኛ! – “እኛና -እናንተ” ሳንባባል፣
ይልቁንስ በጋራ እናፍልቅ ላገራችን መድኅን ፀበል!!
ነሐሴ 2008 ዓ/ም
(ኦገስት 2016)
(ይህ ግጥም ከሁለት ዓመታት በፊት የተሰራጨ ሲሆን፣ ጥቂት ስንኞች ተጨምረውበት ዳግም የቀረበ ነው።)
Dear Getch
i am very proud to know you and to call you my friend.
i read it and it is true!!!
we have to comeback to our senses and join the struggle to get rid of the Woyane Junta!!