• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ሰሚ ያጣ ሕዝብ

October 24, 2016 06:31 am by Editor Leave a Comment

ሕዝብ ተነሳ። ይህ ከወትሮው የተለየ አነሳስ ይመስላል። ከአንዴም ሁለት ጊዜ ይህ ሕዝብ ተነስቶ ሲያበቃ እድሉን ለልጆቹ በአደራነት ሰጥቶ ሲቀመጥ፥ መሪዎቻችን የስልጣን ርክክብ አካሄደው ሕዝቡን በዜሮ እየሰደዱት ስልችቶታል። ቁጭ ብድግ ማለቱ በቃኝ ያለ ይመስላል። አሁን ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ መነሳቱ፥ የስልጣን ርክክብ ለማካሄድ ሳይሆን፥ ዳግም እንደገና መነሳት በማያስፈልገው ሁኔታ ስልጣኑን ራሱ ወስዶ ተረጋግቶ ለመቀመጥ ነው።

ቀድሞ ነገር ባለጉዳዩ ሕዝብ ቁጭ ብሎ መሪዎቻችን ሲተራመሱና ሕዝቡን ራሱን ሲያተራምሱት ምንም ያለማድረጉ በውጭ ለተመልካች ሲታይ ምንም እንደማያውቅ ያስመስለው ይሆናል። እውነቱን ብንመረምር ግን የምናስተውለው ሁሉን አዋቂ እንደሆነና፥ ዝም ያሰኘው ትዕግስቱ መሆኑ በገባን ነበር። የኢትዮጵያ ሕዝብ ሲታገስ መሬት ነው። ይሸከማል፥ ይችላል። ረዥም ጊዜ ይሰጣል። ፅዋ ሲሞላና ጊዜው ሲደርስ ይህ ሕዝብ ጠያቂ ነው። በውጭ ሲታይ ሕዝቡ ጉዳይ ፈፅሙልኝ ብሎ አቤቱታ የሚያቀርብ ይመስላል። ግን አሁን እንደዚያ አይደለም። ቀረብ ብለን፥ አጥልቀን ብናይ ይህ ህዝብ በመልካም አስተዳድሩኝ እያለ መንግስትን እየተማፀነ አይደለም። ደግሞም ስም ጠርቶ እከሌ ይግዛኝ ብሎም እየተሟገተ አይደለም። ሕዝቡ እያለ ያለው ስልጣን የሕዝብ ነውና ለሕዝቡ የስልጣን ባለቤትነቱን የሚያረጋግጥ ድምፁ እንዲሰማ ነው።

መንግስት የሕዝብ ጥያቄ መልስ እሰጣለው ብሎ ጥልቅ ተሃድሶ ላካሂድ ብሎ ተነስቷል። ተቃዋሚ የሕዝብ ጥያቄ እመልሳለው ብሎ ሕገ መንግስት ለማርቀቅ ተነስቷል። በፊት ለፊት የማይታየውን እውነት ለማየት ብንጥር ግን ሕዝብ እያለ ያለው፥ ጊዜው የሁለቱም ተፎካካሪዎች የመምራት ጉዳይ ሳይሆን ሕዝቡ ራሱ የሚመራበት ወቅት መሆኑ ነው። ጊዜው መሪዎቻችን ስፍራቸውን ለሕዝቡ ምሪት የሚለቁበት እንጂ በየፊናቸው በነፍስ ወከፍ ለመምራት ሽር ጉድ የሚሉበት ጊዜ አይደለም። ይልቁንስ ሕዝብ መሪዎቹን ለመምረጥ የስልጣን ባለቤት ሆኖ፥ ድምፁ የሚሰማበትና የሚከበርበትን መድረክ ለማመቻቸት እንወያይና እንግባባ። መንግስትም ሰምቶ ይታዘዝ፥ ተቃዋሚም ሰምቶ ይቀናጅ።

የሕዝቡ ቆራጥነት የትዕግስቱ ውጤት ነው። ጊዜው እስኪደርስ ትዕግስቱ ሲገርም፥ ጊዜው ሲደርስ ደግሞ ቁርጠኝነቱ የሚደንቅ ነው። ውሎ እንዲያድር ፋታ አይሰጥም። በውጭ ሲታይ ለብዙ ጊዜ የታየው ትዕግስቱ አሁንም አለ ብለን እንታለል ይሆናል። ሕዝቡ ከዝምታውና ከመቀመጫው ሲነሳ ቶሎ ብሎ መታዘዝ ማስተዋል ነው። የለመደች ጦጣ ሁልጊዜ ሽምጠጣ ብለን እንደለመድነው እንቀጥል ብንል፥ መሬት የሆነው ሕዝብ እሳት ሆኖ ይበላናል። ስልጣኑን የያዘው የሙጥኝ ማለቱን ትቶ፥ ተቃዋሚዉም ስልጣኑን መቋመጡን ትቶ፥ ሕዝቡ ልምራ ሲል በእሽታ ሁሉም የየግል ምኞቱን ለቆ ይመራ። ለዚህም ዓላማ ይህ ሕዝብ በእውነት የስልጣኑ እውነተኛ ባለቤት የሚሆንበትን መፍትኤ በአስቸኳይ ይመከርበት።

አሁን ልተርክ የተነሳሁት ፊት ለፊት ያለውንና ሁላችንም ያሰለቸንን፥ ግን እውነት ስለሆነው ታሪካችንና ተጨባጭ ሁኔታዎቻችን አይደለም። ደግሞም እውነቱ አድክሞኝ የሌለ ነገር ፈጥሬ አፈታሪክ ለማውራትም አይደለም። ዓላማዬ ፊት ለፊት ከሚታየው እውነት ጀርባ ያለውን ግዙፉን የማይታየውን እውነት አስተውለን፥ የሚገርመውን ነገር እንድናውቅ ነው። እንዴት ማለት ጥሩ ነው።  እንግዲህ ከስር መሰረቱ እንጀምር።

1ኛ/ ሕዝቡ የሚገርም ነው።

የሕዝቡ ማንነት የሚገርም ነው። በመሪዎቻችን ማንነት ሕዝቡ ማንነቱን ተጠልፎ መነጋገሪያ የሆነው የመሪዎቻችን ማንነት ነው። ማን ያውራ ስለ ደጉ ሕዝብ? ማን ያውራ በፍቅር ስለሚተሳሰበው ሕዝብ። ሲራብ አብልቶ፥ ሲጠማ አጠጥቶ፥ አብሮ ተቻችሎና ተጋብቶ ለዘመናት የሚኖረውና የሚያኖረው ሕዝብ ማን ማንነቱን ያራግብለት? ያደከመን በመሪዎቻችን ማንነት ላይ የተመሰረተ የፊት ለፊት እውነት እያወራን ስጋታችን መብዛቱ ነው። ሁሉም ዓላማውን የሚያራምደው ኢትዮጵያን የመሪዎቻችን ነፀብራቅ አድርጎ በመውሰድ ነው። ከላይ ላይ ከሚታየው እውነት ጀርባ የተደበቀውና በጊዜ ተፈትኖ ያለፈው ትልቁ ጥልቅ እውነት ግን የኢትዮጵያ ሕዝብ ቤተሰብነት ነው።

2ኛ/ የሀገር ልጅ የሚገርም ነው።

መሪዎቻችን ሁሉ ሲታዩ ለየቅል ናቸው፦ ኢአዴግ፥ ግንቦት ሰባት፥ መድረክ፥ ሰማያዊ፥ ኦነግ፥ ወዘተረፈ። እንደገና ግልፅ ከሆነውና ከምናውቀው እውነት ጀርባ ያለውን የማይታየውን እውነት ለማየት ብንጥር ሁሉም የሀገር ልጆች ናቸው። ይህም በራሱ ክብር ነው፥ ምክንያቱም ከታላቁ ሕዝብ አብራክ የወጡ የሕዝቡ ልጆች ስለሆኑ ነው። የሀገር ልጆች ስለሆኑም በውስጣቸው ያለው እስከ ዛሬ ያልታየው ችሎታቸው ታሪክ ለመስራት አቅም አለው።

እነዚህ የሀገር ልጆች ድንቅ የሆነው ችሎታቸውና እምቅ አቅማቸው እስካልተገለጠ ድረስ አንዱ ሌላኛውን ለማጥፋት መሮጣቸውን አያቆሙም። ይህ ያልተገለጠው አቅም በውስጥ የሀገር ልጅነት እውን እንደሆነ ሁሉ በገሀዱ ዓለም እውን ሆኖ እንዲወጣ ተአምር ይጠይቃል። ተአምር ማለት ሲደረግ ታይቶ የማይታወቅና፥ ይሆናልም ተብሎ ሊታሰብ የማይችል ነገር ሲሆን ነው።

3ኛ/ ውይይትና መግባባት የሚገርም ነው።

በሀገር ልጆች ያለው እምቅ አቅም የሚገለጠው፥ በሕዝቡ ቆራጥ ግፊት መሪዎቻችን ውይይትና መግባባትን የችግራችን መፍቻ አድርገው መጠቀም ሲችሉ ነው። ይህ ተአምር የአገር ልጆችን እርስ በርሳቸው ተጨፍልቀው አንድ ወጥ እንዲሆኑ የሚያደርግ ሳይሆን፥ እያንዳንዳቸው ውይይትና መግባባትን ተክነውበት፥ ስልጣኑን ባለቤት ለሆነው ሕዝብ ማስረከብ የሚችሉበት መድረክ የሚፈጥር ነው። ተአምሩ ዲሞክራሲና እኩልነት አይደለም። እነዚህ እሴቶች ተአምራት ከሆነው ውይይትና መግባባት የሚገኙ ውጤቶች ናቸው። ይህም እንደ ድሮ በጠጉረ ልውጥ አሳላፊነት የሚካሄድ ሳይሆን በሀገር ልጆች ሽማግሌነት እውነትን ብቻ ዋና መሰረት አድርገው የሚተገብሩት ጉዳይ ነው።

ፊት ለፊት ያለውን የውጭውን ብቻ ለሚያይ ሰው፥ ውይይትና መግባባት መንግስትን በስልጣን የሚያስቀጥል ጊዜ መግዣ እኩይ ተግባር፥ ወይም ተቃዋሚን በአቋራጭ ስልጣን ላይ የሚያስቀምጥ መሰሪ ድርጊት አድርጎ ይወስዳል። የማይታየውን እውነታ ጠጋ ብሎ ለማየት የታደለ ግን፥ ውይይትና መግባባት እስከ ዛሬ ያልተፈተነ ተግባር ሆኖ፥ የሀገር ልጅነትን ውበት ከመሪዎቻችን ውስጥ አውጥቶ እንደ ብሩህ ብርሃን የሚያስፈነጥቅና፥ ለሕዝብ የስልጣን በላይነት ተገዥዎች እንዲሆኑ የሚያደርግ ነው።

4ኛ/ የሚጠበቀው ነገር የሚገርም ነው።

ከእንግዲህ ውሃ ቅዳ ውሃ መልስ የለም። ማንም ላይታመን፥ ሕዝቡ ራሱን ብቻ ሊያምን ተነስቷል። ስልጣን የሕዝብ ነው እያሉ በስሙ የሚነግዱ ከእንግዲህ በቃችሁ ተብለዋል። ስልጣን የሕዝብ መሆኑን የሚናገር ሳይሆን በሕዝቡ ለመመራት ራሱን የሕዝቡ ተከታይ የሚያደርግ ብቻ ይፈለጋል። ከትልቅ ትዕግስት በዋላ ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ሕዝቡ የተነሳው፥ ለመንግስት ስልጣኑን የሚያስረዝምበትን መላ ለማፈላለግ፥ ወይም ለተቃዋሚ የስልጣን ውርስ እንዲያደርጉ ለማመቻቸት ሳይሆን፤ መሪዎቻችን የሕዝቡን ድምፅ እንዲሰሙ እና ስልጣንን ለባለቤቱ (ሕዝብ) ማስረከቢያውን መንገድ እንዲፈጥሩ ነው። ፈሪሃ ፈጣሪ ያለው ይህ ሕዝብ አምላክ እንዳለለት ይታወቅለት።

ኢሜል አድራሻ፦ ethioFamily@outlook.com


“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Left Column

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ከፍተኛ የፋኖ አመራሮች መገደላቸው ተነገረ May 6, 2025 10:40 pm
  • ሃይማኖትን ለተራ የፖለቲካ ሸቀጥ ማዋል ውርደት ነው April 24, 2025 12:43 am
  •  የኬሪያ ኢብራሒም ኑዛዜ “ብትንትናችን ወጥቷል” April 22, 2025 12:08 am
  • ለወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞን አመራሮች ወታደራዊ ሥልጠና ተሰጠ April 16, 2025 11:44 pm
  • ዓቅም እንደሌለው የገመገመው ሻዕቢያ ፊቱን ከጦርነት ወደ ዲፕሎማሲ እያዞረ ነው   April 15, 2025 12:32 am
  • “አንድ የፋኖ ተቋም (የእስክንድር) ተመሥርቷል፤ ሌሎቹ ደግሞ እንዲሁ አንድ ተቋም መሥርተው ወደዚህ ይመጡ” አበበ ጢሞ April 11, 2025 12:07 am
  • መለስ (ለገሰ) ዜናዊ – ተዋርዶ ያዋረደን! April 9, 2025 10:28 pm
  • የተከዜ ዘብ: የሉዓላዊነት መጠበቂያ April 8, 2025 11:49 pm
  • አዲስ አበባ አስተዳደር የሪፖርተርን የተዛባ መረጃ ኮነነ፤ ሕጋዊ እርምጃ እወስዳለሁ አለ April 8, 2025 10:06 pm
  • ሀሰተኛውን የሪፖርተር ዘገባ ንግድ ባንክ በጽኑ ተቃወመ፤ እርማትም ጠየቀ April 8, 2025 09:48 pm
  • “ኦሮሚያ ላይ ወይም ሌላ ቦታ ላይ ስታደርገው ከነበረ ትግራይ ወስጥም የማታደርግበት ምንም ምክንያት አይኖርህም” ነው ጌታቸው ረዳ April 7, 2025 10:22 pm
  • “TPLF’s belief in a strong federal government was always tied to its own dominance in Addis Ababa” April 7, 2025 10:15 pm
  • Counter-Video by EBC Challenges EBS Broadcast, Sparks Public Outcry Over Alleged Misinformation March 31, 2025 02:36 am
  • የኤሊያስ መሠረትን ፌክ መረጃ ማን ያጋልጥ? February 19, 2025 06:00 pm
  • አዘርባጃን፡ የሻዕቢያን ሸምቀቆ ማጥበቂያ?! February 19, 2025 12:29 am
  • የአሜሪካ ድምፅ/ቪኦኤ ይዘጋ ተባለ  February 12, 2025 03:37 am
  • የብልፅግና ፓርቲ ሹመኛ ካድሬዎች February 3, 2025 11:07 am
  • ትግሉን የጎዳው የእስክንድር ነጋ አካሄድ February 3, 2025 10:29 am
  • ኤሊያስ መሠረት “ጭምብሉ ዛሬ ወለቀ”፤ ተከፋይ ነው! February 2, 2025 05:32 pm
  • የፋሲል ግንብ እድሳት እንዴት ተካሄደ? የመንጣቱ ምክንያት? January 23, 2025 03:41 pm
  • ታሪካዊዉ የፋሲል ቤተመንግሥት ለምን ነጣ? January 23, 2025 03:04 pm
  • የኢትዮጵያ አየር መንገድ በተወልደ አስተዳደር ዘመን ለተሠራ ስህተት 425ሺ ዶላር ተቀጣ December 14, 2024 01:44 am
  • በትግራይ ከሞትና ከአካላዊ ጉዳት የተረፉት ለስደት ተዳርገዋል November 27, 2024 12:09 pm
  • የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት አሠራሩን እንዲያርም ጥብቅ መመሪያ ተሰጠው November 27, 2024 11:31 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule