• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

እነ “ሻኪራ” በአሞራ ገደል

August 19, 2013 07:20 pm by Editor Leave a Comment

የዛሬ ሳምንት ሀዋሳ ነበርኩኝ፡፡ የወትሮዋ ሳቂታዋ ሀዋሳ አልነበረችም፡፡ አኩርፋለች፡፡ ሌላ ችግር ገጥሟት ግን አይደለም፡፡ ክረምቱ ነው ያስኮረፋት፡፡

ዝናቡ፣ ቅዝቃዜውና ደመና የሸፈነው ሰማይ ተጫጭነዋት ነበር፡፡ እንደኔ እንደኔ ሀዋሳ ደርሶ አሞራ ገደልን ሳይጐበኙ መመለስ ካለመሄድ እኩል ነው፡፡ እዚህ ስፍራ ዓሳ እንደጉድ ይበላል፡፡ ያውም ቁጥር – ልክ እንደ ስጋ፡፡ የአሳ ቁርጥ ተመጋቢዎች በእንጨት ግድግዳ በተከበበው ዳስ መሳይ ቤት ውስጥ ግፊያውና መረጋገጡን ተያይዘውታል፡፡ በሀዋሳ ሀይቅ ዳር ባለው በዚህ ስፍራ ሰው ከአንድ ቦታ አሳውን ይገዛና እዛው ዳስ ቤት ውስጥ የአሳውን እሾክ እያስወጣ ቁርጡን በሳህን እየያዘ ማባያውን ለማግኘት ሁለት ጐን ለጐን የተቀመጡ ማባያ አቅራቢዎች ጋር መገናኘት ይጠበቅበታል፡፡ አንዱ “ዳጣ” የተባለው እና ከሚጥሚጣ እንዲሁም ከሌሎች ቅመሞች የተሰራ የሚያቃጥል ማባያ ሲሆን (እኔ በጣም ከማቃጠሉ የተነሳ “እንላቀስ” ብየዋለሁ) ሁለተኛው ትንንሽ ክብ የበቆሎ ቂጣዎች ናቸው፡፡ ሁለት ወጣቶች የአሳ ቁርጥ ከግፊያው ውስጥ ይዘው ወጥተው አንዱ ሌላውን፣ “ሂድና ሲዲ ይዘህ ና፣ ታዲያ ስክራች እንዳይኖረው” ሲል አስጠነቀቀው፡፡ ሲዲ ምንድነው ስል ጠየቅሁት አንዱን ወጣት፡፡ “ሲመጣ ታይዋለሽ” አለና ዳጣ ሊያስጨምር መስከረም ወደ ተባለች ዳጣ ሻጭ አመራ፡፡ እኔም “ስክራች እንዳይኖረው” የተባለውን ሲዲ በጉጉት መጠበቅ ጀመርኩ፡፡ ለካስ ሲዲ የሚሉት የበቆሎውን ቂጣ ነው፡፡ “ስክራች” የተባለው ደግሞ ያረረ እና የተሰነጣጠቀ እንዳይሆን ለማለት የተጠቀሙበት አገላለፅ ነው፡፡

ከወጣቶቹ የእንብላ ግብዣ ቀረበልኝ፡፡ የአሳ ቁርጥ በልቼ ስለማላውቅ ብፈራም “ሲዲ”ውን በዳጣ ግን አልማርኩትም፡፡ ወጣቶቹ ቁርጡን እየበሉ ሳሉ አንዱ “ሲዲውን በርን (burn) አድርገው” ሲል ሰማሁ፡፡ ደሞ ምን ማለት ይሆን አልኩኝ – ለራሴ፡፡ ለካ ቂጣው ስለላቀ ጨምር እና ግዛ ለማለት ነው፡፡ በሳቅ ታጅቤ አብሬያቸው ቆየሁ፡፡ በአሞራ ገደል ከአሳ ቁርጥ ባልተናነሰ የአቮካዶ ቁርጥም እንደ ጉድ ይበላል፡፡ ታዲያ የአቮካዶም ማባያ ዳጣ ነው፡፡ የሲዲ ሻጮቹ ሴቶች ቁጥር በርካታ ነው፡፡ ተደርድረው “ከእኔ ግዛ፣ ከእኔ ግዛ” ይላሉ፡፡ ከሁሉም ዳጣ በመሸጥ ፋታ አጥታ የምትተጋው ግን መስከረም ናት፡፡

መስከረም ላለፉት አራት አመታት በዚህ ስፍራ ዳጣ በመሸጥ ስራ ላይ መቆየቷን አጫውታኛለች፡፡ በዚህ ስፍራ ጠዋት ጠዋት ዳጣ በጅምላም በችርቻሮም ትሸጣለች፡፡ በአካባቢው ከልጅ እስከ አዋቂ ሁሉም የአሳ ቁርጥ በሊታ ነው፡፡ እርግጥ የተጠበሰ አሳም በስፍራው ይገኛል፡፡ ግን ቁርጥ ተመጋቢው በቁጥር ይልቃል፡፡ የተጠበሰ አሳ ከአሞራ ገደል ይልቅ በፍቅር ሀይቅ በኩል ኦሲስ አሳ መሸጫ ውስጥ ይገኛል፡፡ በዚህ ቦታ የአሳ ሾርባው ተጠጥቶ አይጠገብም፡፡

እነሆ ሌላ ትዕይንት፡፡ የአሳ ቁርጥ ሲሰራ የሚጣለውና ትርፍራፊውን የአሳ ስጋ በፌስታል በመያዝ እና በአካባቢው አባ ኮዳ ተብሎ ለሚጠራው ግዙፍ የወፍ አይነት እየወረወሩ በመስጠት ሌላ ስራ የሚሰሩም ታዳጊዎች አስደምመውኛል፡፡ እንግዳ ሆነው ከሄዱ ይህ ወፍ በረጃጅም ማንቁርቱ ስጋውን ለመያዝና ከተቀናቃኙ ሌላው ጓደኛው ለመቅደም የሚያደርገው ዝላይ አይን ያፈዛል፡፡ ብልጣብልጦቹም ታዳጊዎች “ሂዱና ፎቶ ተነሱ” ብለው ወፉ አካባቢ እንዲቆሙ ይነግሩዎታል፡፡ እርስዎም በዚህ ትዕይንት መሀል አንድ ታሪካዊ ፎቶ ልነሳ ብለው ወፉ ስጋ ለመቅለብ የሚያደርገውን ዝላይ እየተመለከቱ ፎቶ ሲነሱ ይቆዩና እግዜር ይስጥልኝ ብለው ሊሄዱ ሲሉ “እንዴ ጋሼ (እትዬ) አስር ብር ይክፈሉ፤ ይህንንም ስራ የምንሰራው እኮ በማህበር ነው” ብለው እርፍ ይላሉ፡፡ እየሳቁም እየተገረሙም ከፍለው ይሄዳሉ፡፡ ሌሎች በርካታ ትዕይንቶችም በዚህ ስፍራ ይገኛሉ፡፡

እነ ሻኪራ በአሞራ ገደል አሁን ደግሞ ወደነሻኪራ ልውሰዳችሁ፡፡ በዚህ ስፍራ ካስደነቁኝ ነገሮች ሁሉ የእነ ሻኪራ ጉዳይ ነው፡፡ በ2010 የአለም ዋንጫ በደቡብ አፍሪካ በተካሄደ ጊዜ ሻኪራ በስፍራው ተገኝታ “ዋካ ዋካ ዚስ ኢዝ ታይም ፎር አፍሪካ” የሚል ዘፈን ማቀንቀኗ ይታወሳል፡፡እነሻኪራ ይህን ዘፈን ከነዳንሱ በዚህ ስፍራ አሳምረው ያቀልጡታል፡፡

የቡድን መጠሪያቸው “እነ ሻኪራ” ይሰኛል፡፡ ሂሩት አሸናፊ፣ ሀይማኖት ቶሳ እና መሰረት ኦሳ፡፡ ሂሩትና ሀይማኖት የ7 ዓመት ህፃናት ሲሆኑ የአንደኛ ክፍል ተማሪዎች መሆናቸውን ነግረውኛል፡፡መሰረት ደግሞ ዕድሜዋ ስምንት አመት ሲሆን የሁለተኛ ክፍል ተማሪ ናት፡፡ እነዚህ ህፃናት ጐስቋላ ኑሮ እንደሚኖሩ በማየት ማረጋገጥ ይቻላል፡፡ አለባበሳቸው፣ ፀጉራቸው አጠቃላይ ሁኔታቸው ኑሯቸው ምቾት የራቀው መሆኑን ይመሰክራል፡፡ ከሁለቱ አንዷ ጫማ አልተጫማችም፡፡ ሂሩት ከላይ የለበሰችው አዳፋ ሹራብ ከጠዋቱ ብርድ ሊከልላት አልቻለም፡፡ ሀይማኖት ደግሞ ፀጉሯ ክፉኛ ቆሽሿል፡፡ ጉብኝቴን ጨርሼ ወዳረፍኩበት ለመመለስ ባጃጅ ኮንትራት ስይዝ አጠገቤ ያለ አንድ ወጣት “እነ ሻኪራ ፈረንጆቹ መጡላችሁ” ብሎ ሲነግራቸው ብን ብለው ወደ ፈረንጆቹ ሮጡ፡፡ ፈረንጆቹ የህፃናቱ ፍላጐት የገባቸው አይመስሉም፤ አልፈዋቸው ሄዱ፡፡ እኔ ጠርቼ አናገርኳቸው፡፡ ባለ ባጃጁም እስካናግራቸው እንደሚጠብቀኝ ነግሮኝ፣ የሻኪራን ዘፈን እየዘፈኑ ብር እንደሚቀበሉ ጠቆመኝ፡፡ እነዚህ ህፃናት አማርኛ በደንብ አይችሉም፡፡ ነገር ግን እየተኮላተፉም ቢሆን መግባባት ችለናል፡፡ “የሻኪራን ዘፈን ከነዳንሱ እንበልልሽ” አሉኝ፡፡
“ቀጥሉ” አልኳቸው፡፡

“በወላይትኛ ዳንስ ይሻልሻል ወይስ በራሷ በሻኪራ?” አማረጡኝ፡፡

“በወላይትኛም በሻኪራም እፈልጋለሁ” አልኳቸው፡፡

“ዋካ ዋካ” ተጀመረ፡፡ ዘፈኑ ወዲያው “ዱርሳ ዱርሳ” ወደተሰኘ ሌላ የአካባቢው ዘፈን ተቀየረ፡፡ አከታትለው የትዕግስት ወይሶን “ገደ ገዳ” ቀጠሉ፡፡ ልጆቹ ነገረ ስራቸው አይን ያፈዛል፤ አንጀትም ይበላሉ፡፡ የሚገርመው እኔ ደንሱልኝ ብያቸው እየደነሱ አይናቸውና ልባቸው ሌላ ጋ ነው፡፡ ሌላ የሚያስደንሳቸው ሰው ፍለጋ በሀሳብ ይባዝናሉ፡፡ መቼ ስራውን እንደጀመሩ ስጠይቃቸው በአንድ ቃል “ዱሮ ነው የጀመርነው” ሲሉ መለሱ፡፡

“አሁን ስንት ታስከፍሉኛላችሁ?”

“የፈለግሽውን ስጭን፤ እኛ ይህን ያህል እያልን አንጠይቅም፡፡”

“እዚህ ስትሠሩ፣ ትምህርታችሁስ?” አልኳቸው፡፡

“አሁን ትምህርት ቤት ዝግ ነው፤ ሲከፈት ግን ከትምህርት ቤት በኋላ እየመጣን እንሰራለን” አሉኝ፡፡

እነዚህን ህፃናት በቀን ስንት ብር እንደሚያገኙና ብሩን ምን እንደሚያደርጉት ጠይቄያቸው ነበር፡፡ በቀን እያንዳንዳቸው ከ10 እስከ 40 ብር እንደሚያገኙና ለእናታቸው እንደሚሰጡ ነገሩኝ፡፡ በዚህ የልጅነት እድሜ ወላጆቻቸውን ይደግፋሉ ማለት ነው፡፡ ከእኔ ጋር እያወራን ዕድሜዋ ገፋ ያለ አንዲት ፈረንጅ ስትመጣ አዩና እሷ ጋ ሄደው ለመደነስ ልባቸው ቆመ፡፡ 10 ብር ሰጥቼ ልሸኛቸው ስል የወደፊት ምኞታቸውን ጠየቅኋቸው፡፡ እንደ ሻኪራ ታዋቂ ዘፋኝና ዳንሰኛ መሆን እንደሚፈልጉ ነገሩኝ፡፡ በት/ቤታቸው እንዲህ አይነት እንቅስቃሴ ያደርጉ እንደሆነም ጠይቄያቸው ነበር፡፡ “ት/ቤት እኛ መደነስ እንፈልጋለን ስንል አይፈቀድልንም፤ እዚህ እየመጣን ነው የምንደንሰው” አሉኝና አመስግነውኝ ወደ ፈረንጇ በቀጫጭን እግሮቻቸው ተፈተለኩ፡፡ ፈረንጇም እግዜር ይስጣት ቆማ በተመስጦ ዳንሳቸውን እየተመለከተች፣ ፎቶግራፍ ስታነሳቸው ነበር፡፡ እቺ ፈረንጅ ከእኔ የተሻለ ጉርሻ እንደምትሸጉጥላቸው በልቤ ተስፋ አደረግሁኝ፡፡ ከሁሌም ያሳሰበኝ ግን የወደፊት ዕጣ ፈንታቸው ነው፡፡ እንደምኞታቸው ይሳካላቸው ይሆን? ብዙ ፈተና ይጠብቃቸዋል፡፡ አንድዬ ይርዳቸው፡፡ (ምንጭ፤ አዲስ አድማስ)

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Social Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ከፍተኛ የፋኖ አመራሮች መገደላቸው ተነገረ May 6, 2025 10:40 pm
  • ሃይማኖትን ለተራ የፖለቲካ ሸቀጥ ማዋል ውርደት ነው April 24, 2025 12:43 am
  •  የኬሪያ ኢብራሒም ኑዛዜ “ብትንትናችን ወጥቷል” April 22, 2025 12:08 am
  • ለወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞን አመራሮች ወታደራዊ ሥልጠና ተሰጠ April 16, 2025 11:44 pm
  • ዓቅም እንደሌለው የገመገመው ሻዕቢያ ፊቱን ከጦርነት ወደ ዲፕሎማሲ እያዞረ ነው   April 15, 2025 12:32 am
  • “አንድ የፋኖ ተቋም (የእስክንድር) ተመሥርቷል፤ ሌሎቹ ደግሞ እንዲሁ አንድ ተቋም መሥርተው ወደዚህ ይመጡ” አበበ ጢሞ April 11, 2025 12:07 am
  • መለስ (ለገሰ) ዜናዊ – ተዋርዶ ያዋረደን! April 9, 2025 10:28 pm
  • የተከዜ ዘብ: የሉዓላዊነት መጠበቂያ April 8, 2025 11:49 pm
  • አዲስ አበባ አስተዳደር የሪፖርተርን የተዛባ መረጃ ኮነነ፤ ሕጋዊ እርምጃ እወስዳለሁ አለ April 8, 2025 10:06 pm
  • ሀሰተኛውን የሪፖርተር ዘገባ ንግድ ባንክ በጽኑ ተቃወመ፤ እርማትም ጠየቀ April 8, 2025 09:48 pm
  • “ኦሮሚያ ላይ ወይም ሌላ ቦታ ላይ ስታደርገው ከነበረ ትግራይ ወስጥም የማታደርግበት ምንም ምክንያት አይኖርህም” ነው ጌታቸው ረዳ April 7, 2025 10:22 pm
  • “TPLF’s belief in a strong federal government was always tied to its own dominance in Addis Ababa” April 7, 2025 10:15 pm
  • Counter-Video by EBC Challenges EBS Broadcast, Sparks Public Outcry Over Alleged Misinformation March 31, 2025 02:36 am
  • የኤሊያስ መሠረትን ፌክ መረጃ ማን ያጋልጥ? February 19, 2025 06:00 pm
  • አዘርባጃን፡ የሻዕቢያን ሸምቀቆ ማጥበቂያ?! February 19, 2025 12:29 am
  • የአሜሪካ ድምፅ/ቪኦኤ ይዘጋ ተባለ  February 12, 2025 03:37 am
  • የብልፅግና ፓርቲ ሹመኛ ካድሬዎች February 3, 2025 11:07 am
  • ትግሉን የጎዳው የእስክንድር ነጋ አካሄድ February 3, 2025 10:29 am
  • ኤሊያስ መሠረት “ጭምብሉ ዛሬ ወለቀ”፤ ተከፋይ ነው! February 2, 2025 05:32 pm
  • የፋሲል ግንብ እድሳት እንዴት ተካሄደ? የመንጣቱ ምክንያት? January 23, 2025 03:41 pm
  • ታሪካዊዉ የፋሲል ቤተመንግሥት ለምን ነጣ? January 23, 2025 03:04 pm
  • የኢትዮጵያ አየር መንገድ በተወልደ አስተዳደር ዘመን ለተሠራ ስህተት 425ሺ ዶላር ተቀጣ December 14, 2024 01:44 am
  • በትግራይ ከሞትና ከአካላዊ ጉዳት የተረፉት ለስደት ተዳርገዋል November 27, 2024 12:09 pm
  • የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት አሠራሩን እንዲያርም ጥብቅ መመሪያ ተሰጠው November 27, 2024 11:31 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule