• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

“ከወረስነው ቂም ይልቅ የምናወርሰው ፍቅር ይበልጣል”

January 26, 2014 03:00 am by Editor Leave a Comment

ፈጣሪ በየትውልዱ የራሱን ድምጽ ያወጣልፍቅር ያሸንፋል– የኔ ሳይሆን የትውልድ ድምጽ ነውእዳ አለ የምንል ከሆነም፤ እዳ የሚከፈለውና የሚሸፈነው በፍቅር ብቻ ነው

የፍቅር ጉዞ ከሚለው ሃሳብ እንጀምር፡፡

መነሻው ምንድነው? “አቦጊዳ ብዬ፣ ፊደል “ሀ”ን ቆጥሬ፤

የፍቅርን ትርጉም ለልቤ አስተምሬ፣

ይዤሽ በአኮፋዳ እንደቆሎ ተማሪ፣

አቦጊዳ ልበል የፍቅር ጀማሪ…”

እንዲህ ነው የኔ የዘፈን ህይወት የሚጀምረው። አሁን የፍቅር ጉዞ ላይ ደርሷል፡፡ ሁላችንም፣ በተለያዩ የታሪክ አጋጣሚዎች ውስጥ እናልፋለን። ብዙ ቅሬታና ብዙ ደስታ፣ ብዙ ትክክል የሆኑ ነገሮችና ብዙ ትክክል ያልሆኑ ነገሮች አሉበት – ያለፍንበት ታሪክ፡፡ ትልቁ ነጥብ፣ ካለፍንበት ታሪክ ተነስተን ለሚቀጥለው ጊዜ ምን እናድርግ የሚለው ነው፡፡ ያዘንበትን ነገር በይቅርታ ሰርዘን፣ የወደድነውን ነገር ደግሞ አሳድገን ለመጓዝ፣ ትልቁ መድሃኒት ፍቅር ነው፡፡ ይቅር ተባብሎ የቀድሞ ስህተቶችን ለማስተካከልና በህብረት ተጠራርቶ የቀድሞ ትክክለኛ ነገሮችን ለማሳደግ፣ ፍቅር ያስፈልጋል፡፡ አቡጊዳ ብለን ነው ፍቅርን የምንጀምረው፡፡ “ዳህላክ” ላይም፣ ለልጆቻችን ቂምን አናውርስ ብለናል፡፡ “ካስተማርሽው ፍቅርን በጊዜ፣ አይሻለሁ ወይ ባሱ ጊዜ…” ኢትዮጵያና ኤርትራ ተራርቀው የተፈጠረው ግጭት የሩቅ ጊዜ ታሪክ አይደለም።

የብዙዎችን ህይወት በቀጠፈው ግጭት፣ ብዙ የተበተነ ቤተሰብ፣ የደማ ስሜት አለ፡፡ ይሄ ቁስል ዘላለም እንደመረቀዘ መቀጠል አለበት? መዳን መፈወስ የለብንም? ይቅር መባባልን ነው በ“ያስተሰርያል” የዘፈንነው፡፡ ለምንወልዳቸው ልጆች፤ ለምንፈጥራቸው አዲስ ትውልዶች የምናወርሰው ቂምን ከሆነ፣ ያለፈው መቁሰል ሳይበቃ ለወደፊትም ሌላ አደጋ እንዲፈጠር እየተባበርን ነው ማለት ነው፡፡ የሚሻለው መፍትሔ፣ እኛ የወረስነው አለመግባባት ካለ፣ በቂም ሰበብ የተቋሰልነው ነገር ካለ፣ የአዲሱን ትውልድ ህይወት እንዳያውክ፣ እኛ ጋ መቆም አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡

የዘመናችን ፈተናዎች ሳያንሱ፣ የቅርብ ጊዜ የቂም ታሪክንም እየተሸከመን፣ ከዚያም አልፎ የሩቅ ጊዜ የቅሬታ ታሪኩንም እየቆሰቆስን ቂምን የምናወርስ ከሆነ፣ ለማናችንም ሕይወት የማይጠቅም፣ የልጆቻችንንም ተስፋ የሚያጨልም አደጋ እየፈጠርን እናልፋለን፡፡ ቂምን መሻር፣ ቁስልን መፈወስ፤ ከዚያም አልፎ ለሁላችንም የሚበጅና የተስፋ ብርሃንን የሚያደምቅ ነገር መስራት የምንችለው በፍቅር ነው፡፡ ከ “አቡጊዳ” እስከ “ያስተሰርያል”፣ “ዳህላክ”፣ ቀላል ይሆናል”…እና ሌሎች ዘፈኖች ይህንን መልዕክት ያስተላልፋሉ፡፡ ግን ልዩ አዋቂ ስለሆንኩ ወይም ልዩ ሃይል ስላለኝ አይደለም፡፡ በፈጣሪ ሃይል ነው። ፈጣሪ በየትውልዱ የራሱን ድምጽ ያወጣል። የትውልዱን ድምጽ በኔ አድርጐ ማውጣቱን አምናለሁ፡፡ አሁን፣ ቅን እና ጥሩ ትውልድ አለ፡፡ የዚህ ቅን ትውልድ ድምጽ የፍቅር ድምጽ ነው። ግራ የሚያጋቡ፣ የሚያስጨንቁና የተተበተቡ ችግሮች ሁሉ በፍቅር ይፈታሉ፡፡ ከቂም፣ ከቁስል በፍቅር እንዳን፣ ፍቅር ያሸንፋል የሚለው መልዕክት የኔ ሳይሆን የትውልድ ድምጽ ነው፡፡ ይህ ቅን ትውልድ ተቀራርቦ፣ ተሰባስቦ አንድ ላይ የፍቅር ድምፁን የሚያስተጋባበት እንዲሆን ታስቦ የተዘጋጀ ነው የፍቅር ጉዞ፡፡

በፖለቲካም ሆነ በሌላ ምክንያት፣ በተለያየ ችግርና አለመግባባት በአገራችን ለተከሰተው ቂምና ቁርሾም፣ እዚህ አገር ቤትም ሆነ በየአገሩ ተበታትነው የሚገኙ ወገኖቻችን፣ ቢያንስ ለልጆቻቸው ሲሉ ይቅር መባባልን እንዲቀበሉ ለመጋበዝ፤ የአዲሱ ትውልድ ስሜትም ይሄ እንደሆነ የሚገልፁ ዝግጅቶችን ለማቅረብ ነበር ያቀድነው፡፡ ዝግጅቱን በተለያዩ የኢትዮጵያ ከተሞች በስፋት ለማዳረስ ነው፤ በሄኒከን ከሚተዳደረው በደሌ ቢራ ጋር ተነጋግረን ውል የተፈራረምነው፡፡ በተፈራረምንበት እለት እንደተገለፀውም፤ የቋንቋና የብሔር ስብጥር ውስጥ ህብረትና አንድነታችንን የሚያጠናክር፣ ቂም እንዳንወርስና መልካም መንፈስን ለመጋራት አንድ ላይ የሚጮህ የፍቅር አላማ ያለው ዝግጅት ነው፡፡ ግን፣ የኢትዮጵያ ታሪክም ሆነ የኢትዮጵያውያን ሕይወት አንተ እንደምትለው፣ በፍቅርና ሰላም ብቻ የተሞላ ሳይሆን፣ በቂምና በግጭትም የተበረዘ ነው፡፡

አይደለም? ምን ጥርጥር አለው! ያሉና የነበሩ ነገሮች ናቸው፡፡ የህይወት እና የደስታ ውድነት ትርጉም የሚኖረው ከሞትና ከሀዘን ጋር ነው፡፡ የፍቅር ውበት የሚጐላው፣ ከጥላቻ ጋር ሲነፃፀር ነው። ነገር ግን ያሳዘኑን ነገሮች ላይ ብቻ ስናተኩር፣ አዲሱንና የወደፊቱን ትውልድ ያውካል፡፡ እዳ አለ የምንል ከሆነም፤ እዳ የሚከፈለውና የሚሸፈነው በፍቅር ብቻ ነው፡፡ ፍቅር መድሃኒት ነው፡፡ የነገር ሁሉ መጀመሪያና መጨረሻ ነው፡፡ ሁላችንም ህፃናትን ማቀፍና መሳም የምንወደው ለምንድነው? ገና ሲወለዱ፣ ገና ከመነሻው ሲፈጠሩ ፍፁም ፍቅር ስለሆኑ ነው፡፡ ያ የፍቅር ሃይል ነው የሚስበን፡፡ ህፃኑም እናቱ ጉያ ውስጥ የሚገባው በፍቅር ሃይል ነው፡፡

እንኳን ሰውን የመሰለ ክቡር ፍጥረት ይቅርና አውሬ የምንላቸው እንስሳት ውስጥም የምናየው የተፈጥሮ ሃይል ነው፤ ፍቅር፡፡ ነገር ግን በኑሮ ውስጥ በብዙ ውጣ ውረድ፣ ብዙ ቅሬታዎችና እንከኖች ስለሚያጋጥሙን ፍቅራችንን ሊበርዙብን ወይም ውስጣችንን መርዘው የውስጥ ህመም ሊሆኑብን ይችላሉ፡፡ ባዘንበትና በተቀየምንበት ነገር ላይ ቆመን ተውጠን ስንቀር በሽታ ይሆኑብናል፡፡ ለቅያሜ እልባት እየሰጠንና እየሰረዝን ካልሄድን፣ ይባስ ብለን ለልጅ ልጅ እያወረስን ከቀጠልን፣ በማህበረሰብ ደረጃ እንደዝገት ውስጣችንን እየበላ ይጨርሰናል ወይም እንደተዳፈነ እሳት በሆነ አቅጣጫ ተግለብልቦ ያቃጥለናል፡፡

እና ምን ይሻለናል ብለን ስናስብ፣ በቀድሞ ዘመን ወይም ባለፍንበት ጊዜ የተፈፀሙ መልካም ነገሮችን ወይም ስህተቶችን እንዳልነበሩ ማድረግ አንችልም። ወደኋላ ተመልሰን በህይወት የሌሉ ሰዎችን መሸለም ወይም እዳ ማስከፈል አንችልም፡፡ እነሱ በዘመናቸው አልፈዋል፡፡ ነገሩ ያለው የዛሬ ነዋሪዎች ላይ ነው፡፡ በቀድሞ ሰዎች ታሪክ የምንደሰትበትና የምናዝንበት፣ ትክክል የሆኑና የተሳሳቱ ስራዎች፣ የወደድነውና የተቀየምንበት ነገር ይኖራል፡፡ ቀጥለው የመጡ ትውልዶች የትኛውን ስሜት መያዝ፣ የትኛውን ስሜት ማውረስ አለባቸው? እኛስ የትኛውን ወርሰን የትኛውን ማሳደግ አለብን? ቅሬታና ቂምን ይዘው ያወርሱናል ወይስ ፍቅርንና መዋደድን? ቅያሜና ቂም ብንወርስ ምን ይበጀናል? ወደ ኋላ ተመልሰን እዳ ማስከፈል አንችል? ህይወት የሚቀጥለው፣ ካለው ነገር ላይ በመነሳት ነው፡፡ ስህተቶችን ትተን፣ ትክክል የሆኑትን ይዘን፣ ያን እያሳደግን ነው መቀጠል ያለብን፡፡

ታላላቆቻችን በተለያዩ አለመግባባቶች ውስጥ ያልፋሉ፡፡ አለመግባባትና ቅሬታ ባይፈጠር መልካም ነበር፡፡ ነገር ግን ቢያንስ ቢያንስ፣ የታላላቆችን አለመግባባት ወደ አዲሱ ትውልድ እንዳይሻገርና መጪውን ጉዞ እንዳያውክብን፣ ታላላቆቻችን ስለ አዲሱ ትውልድና ስለመጪው ትውልድ መጨነቅ ያስፈልጋቸዋል ብዬ አስባለሁ። ፍቅር ያሸንፋል የሚለው የታናናሾች የአዲሱ ትውልድ ድምጽም ጐልቶ መሰማት እንዳለበት አምናለሁ፡፡ የፍቅር ጉዞ የዚህ የአዲሱ ትውልድ መንፈስ ነው፡፡ የፍቅር ጉዞ ዝግጅት ከበደሌ ቢራ ጋር ተፈራርመህ በሳምንቱ ነው ውዝግብ የተፈጠረው። እንዴት ነበር የሰማኸው? ከጊዜ በኋላ ነው የሰማሁት፡፡

አንደኛ በድሬዳዋ አንድ ተብሎ የሚጀመረው ጉዞ፣ ትልቅ የፍቅር መልዕክት የያዘ ስለሆነ፣ ያልተበታተነ ትኩረት ይፈለጋል፡፡ ከዚህ ውጭ ባለው ጊዜ ደግሞ፣ በሚቀጥለው መስከረም ወይም ብዙ ሳይቆይ አዲስ አልበም ለማድረስ የጀመርኩት ስራ አለ፡፡ ሁለቱም ቀናተኛ ስራዎች ናቸው፡፡ አእምሮህ ሌላ ነገር እንዲያስተናግድ አይፈቅዱልህም፡፡ በዚህ ምክንያት፣ ባልደረቦቼ በኢንተርኔት በተፈጠረው ውዝግብ ዙሪያ ሊያናግሩኝ ሲሞክሩ ስራ ላይ ሆኜ ብዙም ፈቃደኛ አልነበርኩም፡፡ ሲደጋገም ግን ሰማሁ፡፡ ማኔጀሬ (ዘካሪያስ) ተጨንቆ ነው የነገረኝ። ከሥራ አስኪያጅ አንፃር ሆነህ ስታየው መጨነቁ አይገርምም፡፡ ግን ተረጋግተን ነው የተነጋገርነው፡፡ አልተረበሻችሁም? ነገሩን አቅልለን አላየነውም፡፡ የፍቅር ጉዞ ትልቅ ዝግጅት ነው፡፡

ነገር ግን፣ በብዙ ወጣ ገባ መንገድ ከማለፍ እና ብዙ ውጣ ውረድ ከማየት የተነሳ፣ ችግሮችን ማስተናገድ ትለማመዳለህ፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ የፍቅር መልእክት፣ በቴዎድሮስ ካሳሁን የተፈጠረ ሃሳብ አይደለም፡፡ የነበረ ያለና የሚኖር የእግዚአብሔር ሃሳብ ነው፡፡ ያንተ ድርሻ ያ ሃሳብ ሲሰጥህ መቀበል ነው እንጂ፤ አንተ ከምትጨነቀው በላይ ከምንም አስበልጦ፣ ፈጣሪ ስለ አላማውና ስለሃሳቡ፣ ስለ እኛ እና ስለትውልዱ ስለሚጨነቅ፣ ብዙ አልተሸበርንም፡፡ ሁሉንም ነገር ለበጐ ያደርገዋል ብዬ አምናለሁ፡፡

“ጥቁር ሰው” በሚለው ዘፈንህ በአድዋ ጦርነት ዙሪያ ምኒልክንና ሌሎች የታሪክ ሰዎችን በማንሳት ዘፍነሃል፡፡ የምኒልክ ታሪክ ላይ ያለህን አስተሳሰብ በቅርቡ ቃለ ምልልስ አድርገህ በመጽሔት ታትሟል፡፡ ከዚህ ቃለ ምልልስ ጋር ተያይዞ ነው የምኒልክ ጦርነት ቅዱስ ነው የሚል አወዛጋቢው አባባል የተሰራጨው፡፡ በመጽሔት ታትሞ በወጣው ቃለምልልስ ላይ፣ እንደዚያ አይነት አባባል የለም፡፡ “አካሄዱን ያየ አመጣጡን ያውቃል” በሚል ርዕስ በእንቁ መጽሔት ታትሞ የወጣውን ቃለምልልስ ማየት ይቻላል፡፡ በምኒልክ መቶኛ የሙት ዓመት መነሻነት የተደረገ ቃለምልልስ ነው፡፡

በዚህ ቃለምልልስ ውስጥ ማንንም የሚያስቀይም አባባል የለበትም፡፡ ነገር ግን በኢንተርኔት ሲሰራጭ የኔ ያልሆነ አባባል ታክሎበት የተከፉ ሰዎች እንዳሉ ስሰማ፣ የተሳሳተውን መረጃ ለማስተካከል ምላሽ ሰጥተናል፡፡ እኔ ብቻ ሳልሆን፣ የመጽሔቱ አዘጋጅም አወዛጋቢው አባባል እኔ የተናገርኩት እንዳልሆነ፣ በመጽሔቱ ህትመት ውስጥም እንዳልነበረ አስረድቷል፡፡ ነገር ግን ውዝግቡ በዚህ አልተቋጨም፡፡ ለምን የፍቅር ጉዞን የሚያስተጓጉል ነገር ተፈጠረ አልልም፡፡ እዚህ ምድር ከተገለጡትም ሆነ ካልተገለጡት ሃይሎች ሁሉ የሚልቀው ፍቅር ነው፡፡ ክብደቱም የዚያኑ ያህል ነው፡፡

ስለዚህ የፍቅር ጉዞ ብለህ ስትነሳ፣ ያለ እክል እና ያለ ችግር ትደርሳለህ ማለት አይደለም፡፡ እንኳን ትልቁና ከባዱ ጉዞ ላይ ይቅርና፣ እንደ ቀላል የምናያቸው ጉዞዎች ላይም፣ ወደ ናዝሬት ወይም ወደ አዋሳ ለመሄድ ስትነሳ እንኳ፣ በመኪኖች መጨናነቅ ጉዞህ ሊጓተት ይችላል። ጐማ ቢተነፍስ ወይም ሞተር ቢግል፣ ጐማ ለመቀየርና የራዲያተር ውሃ ለመለወጥ መቆምህ አይቀርም፡፡ ከሁሉም የከበደው የፍቅር ጉዞ ላይማ፣ ለምን ፈተና ይፈጠራል ማለት አይቻልም። ከምንም በላይ ይቅር መባባልን የሚያበዛ የእርቅ መንፈስን ይዘህ ስትጓዝ፣ እንዲያውም ከተቻለ ታላላቆችህም እንዲግባቡልህና መግባባትን እንዲያወርሱ ስትጮህ፣ በዚህ ምክንያት ካንተ ጋር የማይግባባ ነገር ሲፈጠር፣ ነገሩን ንቀህ የምታልፈው አይሆንም፡፡ ምንም እንኳ፣ በተሳሳተ መረጃ ምክንያት የተፈጠረ ቅሬታ ቢሆንም፣ አንተም በተራህ የቅሬታ ባለቤት መሆን የለብህም፡፡ ፍቅር ሁሉንም ያቅፋል፡፡ በተሳሳተ መረጃ የተነሳ ያልወደደህንም ሰው ማቀፍ አለበት። የቃለምልልሱ ሁለተኛ ክፍል በሚቀጥለው ሳምንት ይጠብቁን፡፡ (አዲስ አድማስ)

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Literature Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am
  • Rusted screws, metal spikes and plastic rubbish: the horrific sexual violence used against Tigray’s women July 4, 2025 01:48 am
  • በሞርሞን ቤ/ክ ዕርዳታ የኪዳነምህረት ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ማምለኪያ ሥፍራ አገኘች July 2, 2025 01:28 pm
  • የበረከት ስምዖን “አየር ላይ ትዕይንት” አየር ላይ ተበተነ July 2, 2025 01:24 am
  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am
  • ከትግራይ ሾልኮ የወጣው ምሥጢራዊው ሰነድ ምንድነው? May 20, 2025 09:18 am
  • በደቡብ ጎንደር በጸዳሉ ደሴ የተመሩት 72 ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ May 19, 2025 02:24 pm
  • የተመሠረተው የፋኖ አደረጃጀት ዋነኛ ዓላማው ድርድር መሆኑ ተነገረ May 14, 2025 11:07 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule