• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

የጎልጉል ቅምሻ

March 6, 2013 09:29 am by Editor Leave a Comment

“ሐብቴ ቢያንስ 20ቢሊዮን ፓውንድ ነው”

የዓለማችንን ባለጠጋዎች ዝርዝር በማውጣት የሚታወቀው ፎርብስ የተሰኘው መጽሔት የሳውዲ ንጉሥ አብዱላ ወንድም ልጅ የሆኑትን ልዑል አልዋሊድ ቢን ጣላል ያላቸውን ሃብት ዝቅ አድርጎ በመናገሩ ልዑሉ እጅግ ተቆጥተዋል፡፡

የሐብታቸው መጠን ቢያንስ 20ቢሊዮን የእንግሊዝ ፓውንድ እንደሚደርስ የተናገሩት ልዑል በደንብ ከተሰላ መጠኑ 29.6ቢሊዮን ፓውንድ እንደሚደርስ አስታውቀዋል፡፡ ሮልስ ሮይስን፣ ፌራሪን እና ላምበርጊኒስን ጨምሮ ከ200 መኪናዎች በላይ ያሏቸው የ57ዓመቱ ልዑል ጣላል፤ በአውሮጳ እጅግ ውድ የሆኑ ሆቴሎችን ባለቤት ከመሆናቸው አልፎ እጅግ ትልልቅ የሆኑ ሁለት መርከቦች እና የዓለም ትልቁ የግል አውሮፕላን ጀት ባለቤትም ናቸው፡፡ በለንደኑ ሳቮይ ሆቴል፣ በአፕል ኩባንያ፣ በሲቲግሩፕ እና ኒውስ ኮርፕ ያላቸው ከፍተኛ ኢንቨስትመንት ዋጋው ዝቅ ተደርጎ እንደተገመተ ያስረዱት ልዑል ለሁኔታው ተጠያቂ ነው ያሉትን የመጽሔቱ ዋና አዘጋጅ ከሥራው እንዲባረር ጠይቀዋል፡፡ ጉዳዩንም ፎርብስ ለመካከለኛው ምስራቅ ባለሃብቶች ያለውን የተጣመመ አመለካከት የሚያሳይ ነው በማለት ወንጅለውታል፡፡

በርካታ የዓለማችን ባለጠጋዎች የሃብታቸውን መጠን በይፋ ለመናገር ፈጽሞ የማይፈልጉ መሆናቸው እየታወቀ ባለበት ሁኔታ የልዑሉ ግልጽነት በርካታዎችን አስደምሟል፡፡ እርሳቸው እንደሚሉት ሃብታቸው በትክክል ቢመዘን ኖሮ ከ26ኛ ደረጃ ወደላይ ከፍ በማለት ከሎሪዬል (የሽቶና ማስዋቢያ አምራች) ወራሽ ሊሊያን ቤተንኩር ቀጥሎ የ10ኛ ደረጃ ይጎናጸፉ ነበር፡፡

ከእስርቤት ወደ ሆቴልቤት

ቦታው ከዚህ በፊት ሰዎች የተቻላቸውን ሁሉ አድርገው ቢቻል መውጣት የሚመኙት ነው፡፡ አንድ ቀን እንኳን ማደር የማይፈልጉበት ነበር፡፡ ከፍተኛ ወንጀል የፈጸሙ እስረኞች የሚታሰሩበትና ላለፉት 150ዓመታት አገልግሎት ሲሰጥ የነበረው በኔዘርላንድ የሚገኝ እስርቤት ፍጹም ማሻሻያ ተደርጎበት ወደ ሆቴልነት ከተቀየረ ወዲህ ግን ሰዎች በርካታ ቀናት የሚያድሩበትና ቢቻላቸውም ጨምረው መቆየት የሚፈልጉበት ቦታ ሆኗል፡፡

105 የእስረኛ ክፍሎች የነበሩት ወደ 40 ሰፋፊ ያጌጡ የሆቴል ክፍሎች ተቀይረው በክፍሎቻቸው ዘመን አመጣሽ ቲቪዎች፣ ነጻ የኢንተርኔት አገልግሎት፣ … ከውብ መኝታዎቻቸው ጋር አገልግሎት ይሰጣሉ፡፡ ተጠቃሚዎችም ዳጎስ ያለ ገንዘብ በመክፈል ያድሩባቸዋል፡፡

ልማት፣ ሕዳሴ፣ … እያለ ሕዝባችንን የሚያደነቁረው ኢህአዴግ ከልማትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዱ ውስጥ የእስርቤት ግንባታውን ጉዳይ ቢሰርዘው ከሰማን እንነግረዋለን፡፡ በተለይ አሁን ደግሞ ሙስሊሞችን ጥያቄ አቀረባችሁ በማለት በገፍ እስርቤት እያስገባ ከሚያሰቃይና ተጨማሪ እስርቤቶችን ከሚሠራ ጥያቄያቸውን ቢመልስና ሁሉንም የፖለቲካ እስረኞች ለቅቆ የኔዘርላንድን ፈለግ መከተል ከሁሉ የላቀው ህዳሴ ነበር፡፡

“ኪርዛኪስታን” – አዲሷ የጆን ኬሪ አገር

የአሜሪካ ፖለቲከኞች ለሌላው ዓለም ስምና አጠራር እምብዛም አይጨነቁም፡፡ አጣምመው፤ አወላግደው፤ … የአገር፣ የቦታዎችን፣ የመሪዎችን ስም ሲጠሩ ይሰማሉ፡፡

በቅርቡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነው የተሾሙት ጆን ኬሪ ሥልጣን ከመያዛቸው አንድ ወር ባነሰ ጊዜ አዲስ አገር ፈጥረዋል – “ኪርዛኪስታን” የምትባል! በቅርቡ በቨርጂኒያ ዩኒቨርሲቲ ባደረጉት ንግግር የአሜሪካ ወዳጅ የሆነችውን ኪርጊስታንን እና የሰሜን ጎረቤቷ የሆነችው ካዛኪስታንን በመቀላቀል ኪርጊስታንን የጠሩ መስሏቸው ኪርዛኪስታን በማለት ለዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች አዲስ አገር አስተዋውቀዋል፡፡ እንደዚህ አይነት ስህተቶችን በመስራት የሚታወቁት ጆን ኬሪ ከስድስት ዓመት በፊት በኢራቅ የሚገኙትን የአሜሪካ ወታደሮችን ዝቅ የሚያደርግ ቃል ተናግረው አያሌ ሕዝብ ተከፍቶባቸው ነበር፡፡ “ትምህርታችሁን በደንብ ከተከታተላችሁ፤ እንደሚገባው ካጠናችሁ፤ የቤት ስራችሁን ከሰራችሁ ጎበዝ ተማሪ ትሆናላችሁ፤ አለበለዚያ ግን ኢራቅ ተቀርቅራችሁ ነው የምትቀሩት” በማለት ነበር በወቅቱ ለመቀለድ የሞከሩት፡፡ በመጪዎቹ አራት ዓመታት ብዙ ሲሉ እንሰማቸዋለን፡፡

1.6 ሜትር የጾታ ግድግዳ በየሱቁ

ሳውዲአረቢያ በምትከተለው ጥብቅ ሃይማኖታዊ ሕግ ምክንያት የቅርበት ዝምድና የሌላቸው ወንድና ሴት በሙሉ ተለያይተው ሥራቸውን እንዲያከናውኑ ሰፋፊ ሱቆች 1.6ሜትር (5ጫማ ከ3ኢንች) ከፍታ ያለው ግድግዳ እንዲያቆሙ ታዝዘዋል፡፡ ወንድና ሴት ሠራተኞችን የሚቀጥሩ ሱቆች ይህንን ትዕዛዝ እንዲተገብሩና ሁኔታውንም ሃይማኖታዊ ፖሊሶች (ሙታዋ) እንዲያስፈጽሙ ተነግሯቸዋል፡፡

ሆኖም ጉዳዩ አሉባልታ ነው በማለት ምላሽ የሰጡት የመንግሥት ባለሥልጣን ወንድና ሴት ሠራተኞች የሚቀጥሩ ሱቆች ሁኔታው እንዳመቻቸው የፈለጉትን ማድረግ ይችላሉ በማለት ጉዳዩን አጥላልተውታል፡፡ እስላማዊው ግዛተአጼ በሚከተለው ዋሃባዊ የሻሪያ ሕግ ምክንያት በሳውዲአረቢያ ሴቶች መኪና መንዳት የማይፈቀድላቸው ሲሆን በባንኮችና ቢሮዎች የራሳቸው የመግቢያ በር የሚጠቀሙ እንዲሁም በአለባበስ በኩል ጥብቅ ሥርዓት መከተል ይጠበቅባቸዋል፡፡

በሰሜን አፍሪካ የአረብ ጸደይ የለውጥ ማዕበል ለዘመናት በሥልጣን የቆዩ መሪዎች ከሥልጣን ካስወገደ በኋላ የአሜሪካ ጥብቅ ወዳጅ በሆነችው ሳውዲአረቢያ እጅግ መጠነኛ ለውጦች እየተካሄዱ ይገኛል፡፡ ባለፈው ወር ንጉሥ አብዱላ በምክርቤታቸው አወቃቀር ላይ ማሻሻያ ካደረጉ በኋላ 150 አባላት ከሚገኙበት የሹራ ምክርቤት 30 የሚሆኑት ሴቶች መቀላቀል ችለዋል፡፡

“ሒትለር በአመጋገቡ እጅግ ጠንቃቃ ነበር” ምግብ ቀማሹ

የአዶልፍ ሒትለርን ምግብ ለዓመታ ሲቀምሱ የነበሩ የ95ዓመቷ ጀርመናዊት ሒትለር በአመጋገቡ በኩል እንዴት ጠንቃቃና አትክልትና ፍራፍሬን በታማኝነት ይመገብ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ሒትለር በምግብ መርዝ እንዳይሞት ከፍተኛ ጥበቃ እንዲካሄድ በማስፈለጉ ይህንኑ የምግብ መቅመስ ጉዳይ እንዲያከናውኑ ከተመደቡት 12ሴቶች መካከል አንዷ የነበሩት አዛውንት ሲናገሩ “ከእኩለቀን በፊት ከ5 እስከ 6ሰዓት ባለው ጊዜ ውስጥ ሁላችንም ምግቡን እንቀምሳለን፤ ከዚያም ምግቡ ወደኤስ ኤስ ጠቅላይ ጽ/ቤት ይወሰዳል” ብለዋል፡፡ ምግቡ በሙሉ አትክልት እንደነበረና የሥጋ ምግብና አሣ ሲቀርብ እንደማያስታውሱም ገልጸዋል፡፡ ባሳለፏቸው ዓመታት ከባድ ፍርሃት ላይ ወድቀው እንደነበር የተናገሩት ሴት በሆነ አጋጣሚ ምግቡ ተመርዞ ቢሆን ኖሮ እንኳን የመቅመስ ግዴታ ስለነበረባቸው ቀምሰው ሊሞቱ ይችሉ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡

የጀርመን ሕዝብ የአትክልት ተመጋቢ እንዲሆን ከፍተኛ ምኞት የነበረው ሒትለር ጦርነቱ ከተጠናቀቀ በኋላ ዓላማውን ተግባራዊ ለማድረግ ዕቅድ ነድፎ እንደነበር ይነገርለታል፡፡ የአትክልትን ብቻ ምግብነት የሚደግፉ ቡድኖች በተለይ በአሁኑ ጊዜ የሥጋ ውጤቶች በኬሚካልና በሌሎች ሆርሞኖች እየተበላሸ በመምጣቱ የእንስሳትንም ሆነ የዶሮ ሥጋ ለምግብነት መጠቀም ለበርካታ በሽታዎች እንደሚያጋልጥ ይመክራሉ፡፡

“ስለ እናት”

ከዚህ በታች ያለውን ጽሁፍ ያገኘነው ከዮሐንስ ሞላ ፌስቡክ (Yohanes Molla) ነው፡፡ ስለእናቱ የጻፈውን አጭርና እጅግ መሳጭ ጽሁፍ እንዳለ አቅርበነዋል፡፡ ዮሐንስ ለጽሁፉ ርዕስ ባለመስጠቱ “ስለ እናት” ብለን ሳናስፈቅድ ርዕስ በመስጠታችን እንደማይቀየመን ተስፋ እናደርጋለን፡፡ ምስጋናችንም የላቀ ነው፡፡

“… በልጅነቴ ተድሬ ልጅነቴን ሳላውቀው አለፈኝ። ከዚያ በኋላ ግን ከጓደኞቼ ጋር… አሻሮ እየቆላን፣ እንኩሮ እያነኮርን እንጫወት ነበር። ስራችንን ከጨረስን ዝም ብለን እየተቀላለድን እንጫወታለን። እንዘፍናለን። እንጨፍራለን። ልጆች ነን፥ ዝም ብሎ መሳቅ መቀለድ ነው። ግን የግድ ማስተዋልም አለ።… ታዲያ ሁሉም ነገር መሽቶ ባሎቻችን ቤት እስኪመጡ ነው።… ከመሬት ተነስተው ስለሚመቱን እንፈራለን።

ያኔ ሳንቲም እንዳያጥረኝ መሸታ እጠምቅ ነበር። … መጥመቁን ከእናቴ የተማርኩት ነው። እናቴ ትነግዳለች፤ መሸታ ስለምትጠምቅ ብር አይቸግራትም ነበር። እኔም አንድ ልጇ ስለሆንኩ አይከብዳትም መሰለኝ በጣም ትንከባከበኝ ነበር። በልጅነቴ – 9 ዓመት ሲሆነኝ – ሞተች። ታዲያ ግን እርሷ የምትለውን ያምታደርገውን ሁሉንም አስታውሳለሁ። እንደሷ መሆን እፈልግ ነበር።…

ባለቤቴ የቀን ወጪ 30 ሳንቲም ይሰጠኛል። 30 ሳንቲም ብዙ ነው። ቡናውን፣ የቡና ቁርሱን፣ ወጡን፣ እንጀራውን፣ እንጨቱን፣ ሁሉንም በዚያው በ30 ሳንቲም ነው። እርሱን አብቃቅተን እንበላበትና ያልቃል።… ከሆድ አያልፍም ነበር። እንግዳ ቢመጣብኝ እንኳን አንድ ጣሳ ጠላ ገዝቼ ላስተናግድ ብል ስለማልችል ተጨማሪ ፍራንክ እፈልግ ነበር። ለዚያ ነው ጠላ የምጠምቀው። እንደዛ ስለማደርግ ሳንቲም አይቸግረኝም።

የብር ከሃምሳ ጠላ ብጠምቅ፣ ብር ከሃምሳ ትርፍ ያመጣልኝ ነበር። እንግዳ ቢመጣ አላፍርም፤ በደንብ ነው የማስተናግደው። ከጓደኞቼም ጋር አምስት አምስት ሳንቲም እናዋጣና እንጀራ፣ ጠላ ቆሎ ሁሉን ነገር ገዝተን እየበላን እየጠጣን እንጫወታለን። ጨዋታ ሳንጨርስ ስላገባን ዝም ብሎ መጫወት ያምረን ነበር። በየቀኑ ጨዋታ ነው።… እንደዚያም ሆኖ ግን ቤት አለ። የቤት ስራው አለ። ባል ይማታል። ልጅ ማሳደግ አለ።…

በ21 ዓመቴ 3 ልጆች ወልጃለሁ። ራሴ ግን ልጅ ነበርኩኝ። (ትስቃለች) እንኳን ልጅ ላሳድግ ጨዋታም ያምረኝ ነበር። መጀመሪያም ሳልፈልግ ስላገባሁ ሁሌ መፋታት እፈልግ ነበር። አባቴን በመጡ ቁጥር እጨቀጭቃቸው ነበር። ዛሬም አስፈቱኝ። ነገም አስፈቱኝ ነው። እርሳቸውም ‘ልጅነት ነው። ልጅ ስትወልድ ትተወዋለች።’ እያሉ በቀጠሮ ያራዝሙብኛል።

ብልህ ነበሩ፥ ቆይ ለፋሲካ፣ ቆይ ለመስቀል ይሉኛል። እኔም አልረሳም። እውነት መስሎኝ አስታውሼ እጠይቃቸዋለሁ። ለመስቀል ስጠይቃቸው – ‘ቆይ ለፋሲካ’ ይሉኛል። ለፋሲካ ሳስታውስ – ‘ቆይ ለገና’ ይሉኛል። እኔም ሳልረሳ እጠይቃለሁ። ታዲያ ሁለት ልጅ ተከታታይ ሞቶብኝ ሶስተኛውን ልጄ ሳይ የትም መሄድ አስጠላኝ። እንኳን አፋቱኝ ልል ከዚያ ቤት ሞት ይንቀለኝ አልኩኝ። ብማረርም መፋታቱን ማሰብ ተውኩኝ።

ታዲያ ተፋትቼ ቢሆን ኖሮ ይፀፅተኝ ነበር። ይሄን ሁሉ አላይም ነበር። ሳልፈልግ አግብቼ ከእግዚአብሄር ጋር ቤት ሙሉ ልጅ አሳደግሁኝ። … ፀጋው አይጓደል። ምን አጣሁ? ባጣም የማላውቀውን ነው።… ” ~ My Mom ♥


ዘገባውን ለማጠናቀር በየጽሁፉ ከጠቀስናቸው ምንጮች በተጨማሪ ሌሎችንም የሚዲያ ውጤቶች መጠቀማችንን ለመግለፅ እንወዳለን፡፡ ከዜናዎቹ ማነስ አኳያ በየጸሁፉ ለመግለጽ ባለመቻላችን ይቅርታ እንጠይቃለን፡፡

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: News Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የተንጋደደው የገዱ መልስ February 6, 2026 03:05 pm
  • ሻዕቢያ “አክሱም ገብቶ ወጣቶች በጅምላ ሲረሽን ጸብ ተፋፍሟል …” February 4, 2026 01:15 pm
  • አደራ ጠባቂው የኢሉአባቦር ሕዝብ February 4, 2026 12:14 pm
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን January 28, 2026 09:56 am
  • በአሜሪካ ጥምር ዜግነት እንዲቀር ጥያቄ ቀረበ January 27, 2026 03:05 pm
  • “ከህወሓት፣ ከሻዕቢያ፣ ከግብፅ ሰዎች ጋር ሆኖ እንዴት የአማራን ጥያቄ ማስመለስ ይቻላል?” ኮሎኔል ፈንታው January 25, 2026 04:23 am
  • የኢትዮጵያ አየር ኃይል: ለአፍሪካ ሀገራት የመጀመሪያዎቹን የአየር ኃይል አብራሪዎች ያሰለጠነ ተቋም January 25, 2026 03:50 am
  • የአማረ ሪፖርተር እያደረሰ ያለው የብሔራዊ ደኅንነት አደጋ January 22, 2026 01:56 am
  • የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የማርያምን ማዕረግ ዝቅ አደረገች December 12, 2025 09:27 pm
  • ኢህአፓ: ከነጭ ሽብር ወደ “አዲስ አበባ ትናገር” የጎዳና ሽብር? December 12, 2025 09:11 pm
  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule