
በተለምዶ ሰይጣን ቤት ወይም ፒራሚድ አዲስ እና ባስ አዲስ ክለብ ታሸጉ፤ 68 ሰዎችም በቁጥጥር ስር ውለዋል።
በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 3 አስነዋሪ ድርጊት እና ትውልድን በሚጎዳ ስራ ላይ የተሰማሩና ሲጠቀሙ የተገኙ 68 ሰዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የከተማው አስተዳደር አሳውቋል።
ከህብረተሰቡ በደረሰ ጥቆማ በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻ በተለምዶ ሰይጣን ቤት ወይም ፒራሚድ አዲስ እና ባስ አዲስ ክለብ በማህበረሰቡ ተቀባይነት የሌላቸው አፀያፊ ድርጊቶች ሌሎች ህገወጥ ተግባራት ሲፈፅሙ በመገኘታቸው ቤቶቹ መታቸጋቸው ተገልጿል።
የአዲስ አበባ ከተማ ደንብ ማስከበር፣ የአዲስ አበባ ከተማ ፖሊስ እና የሠላምና ፀጥታ ቢሮ በጋራ በመሆን ትላንት ከምሽቱ 4:00 ሰዓት እስከ 8:00 ሰዓት ባደረጉት ድንገተኛ ፍተሻ ነው ህገወጥ ተግባራት ሲፈጸምባቸው የተገኙት የምሽት ቤቶች እንዲታሸጉ የተደረገው።
በተደረገው ድንገተኛ ፍተሻ ፦
– ከ100 በላይ የሺሻ ዕቃዎች ፣
– በርካታ መዋሰሎች፣
– ከ6 በላይ ሀሺሽ የያዙ እቃዎች እንዲሁም በወቅቱ በቦታው የነበሩ ከ68 በላይ የሚሆኑ ተጠቃሚዎችን እና ወጣቱን በዚህ እኩይ ድርጊት ላይ እንዲሳተፍ ሲያደርጉ የቆዩ ግለሰቦች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የከተማው አስተዳደር ገልጿል።
ነዋሪዎች በየአከባቢያቸው አዋኪና ከማህበረሰቡ ወግና ባሕል ያፈነገጡ አስነዋሪ ድርጊቶች ላይ ወጣቱ እንዲሳተፍ የሚያደርጉ ምሽት ቤቶችንና ግለሰቦችን በማጋለጥ ሀላፊነቱን እንዲወጣ ጥሪ ማቅረቡን የአዲስ አበባ ከንቲባ ጽቤት አስታውቋል።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply