
• ከአዲስ አበባ ወደ ጎጃም ለሌላ ለቅሶ በመሄድ ላይ የነበሩ ዜጎች ተደብድበው ተመልሰዋል
የሰማያዊ ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮችና አባላት ሰኔ 8/2007 ዓ.ም ደብረማርቆስ ከተማ የተገደለው የሳሙኤል አወቀ ለቅሶ እንዳይደርሱ ታገዱ፡፡ አመራሮቹና አባላቱ ሰኔ 13/2007 ዓ.ም በጠዋት ከአዲስ አበባ ተነስተው የሳሙኤል አወቀ ቤተሰቦች ወደሚገኙበት ምስራቅ ጎጃም ዞን ግንደወይን እያቀኑ በነበረበት ወቅት አባይ ድልድይ ላይ በፌደራል ፖሊስ ታፍነው ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ ጎሃ ፂዮን ከተማ ውስጥ እስከ ምሽቱ 2 ተኩል ድረስ ታግተው ውለዋል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላትን ወደ ለቅሶ እንዳይሄዱ ያገዱት ከአዲስ አበባ የሄዱና ከቦታው ተዘጋጅተው ሲጠብቁ የነበሩ የፌደራል ፖሊሶች እንደሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡
አመራሮቹና አባላቱ ለፖሊስ ቃል ሲሰጡ ከሳሙኤል አወቀ ጋር የነበራቸውን ግንኙነት፣ በፓርቲው ውስጥ ያላቸውን ኃላፊነት፣ ሳሙኤልን ማን እንደገደለው የሚመለከቱ ጥያቄዎች ቀርበውላቸዋል፡፡ ለቅሶ እንዳይደርሱ ከተከለከሉትና ታተው የዋሉት:-
1. ኢ/ር ይልቃል ጌትነት/ የፓርቲው ሊቀመንበር
2. ይድነቃቸው ከበደ/ የፓርቲው የህግ ጉዳይ ኃላፊ
3. ወሮታው ዋሴ /የፓርቲው የፋይናንስ ጉዳይ ኃላፊ
4. ሀብታሙ ደመቀ/ የኦዲትና ኢንስፔክሺን አባል
5. ጌታቸው ሺፈራው/ የነገረ ኢትዮጵያ ዋና አዘጋጅ
6. ጋሻው መርሻ/ የብሄራዊ ምክር ቤት አባል
7. እምላሉ ፍስሃ/ የብሄራዊ ምክር ቤት አባል
8. ሜሮን አለማየሁ/ አባል
9. ጥላሁን አበጀ/ አባል
10. ጠና ይታየው/ አባል
11. እስጢፋኖስ በኩረጽዮን /አባል
12. ኃይለማሪያም ተክለ ጊዮርጊስ/ አባል
13. ጋሻነህ ላቀ/ አባል
14. ግርማ ቢተው አባልና
15. የመኪናው ሾፌር ናቸው
ከምሽቱ 2 ሰዓት ተኩል ከአዲስ አበባ በመንገድ ትራንስፖርት ሰራተኞችና ትራፊክ ፖሊሶች ህጋዊ መሆኑ ተረጋግጦ ያለፈው እንዲሁም ለአራት ቀን ከፓርቲው ጋር ውል የያዘው መኪና እንዳይንቀሳቀስ ተከልክሎ ከፍተኛ አመራሮቹና አባላቱ ከእስር ተለቀዋል፡፡ በተጨማሪም የሰማያዊ ፓርቲ ልዑካን ይዘዋቸው የነበሩ ቁሳቁሶች ለምርመራ በሚል በፖሊስ ተይዘዋል፡፡
በሌላ ዜና ከአዲስ አበባ ተነስተው ምስራቅ ጎጃም ዞን ደብረ ኤልያስ ወደ ሌላ ለቅሶ ሲሄዱ የነበሩ ዜጎች የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ከታፈኑ በኋላ ደጀን ላይ ተይዘው ከፍተኛ ድብደባ ተፈፅሞባቸው በግዳጅ ወደ አዲስ አበባ እንዲመለሱ ተደርገዋል፡፡ ተመልሰው ወደ ለቅሶው ቢሄዱ እስከ 10 ሺህ ብር ሊቀጡ እንደሚችሉ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸዋል፡፡ እነዚህ ዜጎች በተያዙበት ወቅት ሰማያዊ ፓርቲ ደብረማርቆስና ባህርዳር ላይ ሰላማዊ ሰልፍ ሊያደርግ እንደሆነ እንደተገለጸላቸው እነሱም የሰማያዊ ፓርቲ ሰልፍ ላይ ትገኛላችሁ ተብለው ተጠርጥረው እንደሆነ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ይህ ዜና እየተሰራ ባለበት ወቅት ማረፊያ ክፍል እየፈለጉ የሚገኙት የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት በፌደራል ፖሊስና በደህንነቶች ከፍተኛ ክትትል እየደረሰባቸው መሆኑ ታውቋል፡፡
ተጨማሪ መረጃ
የሰማያዊ ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች አሁንም ወደ ሳሙኤል ቤተሰቦች እንዳይሄዱ እንደታገዱ ናቸው
ሰኔ 8/2007 ዓ.ም የተገደለውን የሳሙኤል አወቀን ቤተሰቦች ለማስተዛዘን ከአዲስ አበባ ወደ ግንደወይን በሚሄዱበት ወቅት አባይ ድልድይ ላይ ከአዲስ አበባ በመጡ የፌደራል ፖሊሶችና ደህንነቶች ታፍነው ወደ ግንደወይን እንዳይሄዱ የተከለከሉት የሰማያዊ ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮችና አባላት አሁንም እንዳይንቀሳቀሱ እንደታገዱ ናቸው፡፡ ትናንት ከስምንት ሰዓት ጀምሮ ታስረው የዋሉት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ምሽቱ 2 ሰዓት ተኩል ላይ ቢለቀቁም መኪናውን ጨምሮ ቁሳቁሶቻቸው በሰሜን ሸዋ ዞን ወረጃርሶ ወረዳ ፖሊስ ጣቢያ በመያዙ መንቀሳቀስ አልቻሉም፡፡
የፖሊስ ጣቢያው ኃላፊ ኢንስፔክተር ወጋየሁ ጎንፋ መሬ “ወደ ገጠር ወጥቻለሁ” በሚል እንዲሁም ሌሎች አመራሮች ቢሮ ዘግተው በመውጣታቸው ቁሰቁሶቹን መቀበል አልተቻለም፡፡ ይሁንና ኢንስፔክተር ወጋየሁን ጨምሮ ሌሎች አመራሮችም ከተማ ውስጥ እንደሚገኙ ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ከእስር ሲለቀቁ ደህንነትና ፖሊሶቹ ነጻ እንደሆኑና እንዳጉላሉዋቸው በመግለጽ ይቅርታ ጠይቀው የነበር ቢሆንም ቁሳቁሶቻቸው ግን “ለምርመራ” በሚል ይዘዋቸዋል፡፡ አመራሮቹና አባላቱ “ነጻ ከሆንን ቁሳቁሶቻችንም የሚያዙበት መንገድ መኖር የለበትም፡፡ ቁሳቁሶቻችን ካልሰጣችሁን አንወጣም” ቢሉም ፖሊስ መብራቱን በማጥፋት ከግቢ አስወጥቷቸዋል፡፡ (በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር)
Leave a Reply