• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

አያስቅም! አጭር ወግ

March 10, 2014 08:45 pm by Editor Leave a Comment

በብሄራዊ ትያትር አካባቢ አንዲት አነስተኛ ምግብ ቤት ነበረች። «ገሊላ ምግብ ቤት» ትባል ነበር።  በአዲስ አበባ «ቁምራ» ከመግባቱ በፊት በአካባቢው ያሉ የመንግስት ሰራተኞች በምሳ ሰዓት ይህችን ምግብ ቤት ያጨናንቋት ነበር። ቁምራን የማታውቁ ካላችሁ፤ ለጽድቅ የሚደረግ መንፈሳዊ ጾም እንዳይመስላችሁ። እድገትና ትራንስፎርሜሽኑ ያመጣው አዲስ ክስተት ነው – ቁርስ ምሳና ራት በአንድ ጊዜ የመመገብ ዘዴ። «ኑሮ በዘዴ፣ ጾም በኩዳዴ» ይባል ነበር። ይህ አባባል አሁን መኖ በዘዴ በሚል ተቀይሯል። መቼም ሁሉም ነገር በነበር እየቀረ ነው።

ጋዜጠኛ አቤል አለማየሁ በቅርቡ ባሳተመው “የአዲስ አበባ ጉዶች” የሚል መጽሃፉ ላይ ስለዚህች ታሪካዊ ምግብ ቤትም ትንሽ ብሏል። የምግብ ቤትዋ ባለቤት “ገሊላ ምግብ ቤት” የሚለው ጽሁፍ በከፊል አጥፍተውታል። አሁን ምግብ ቤት የሚለው ተነስቶ “ገሊላ” የሚለው ብቻ ነው የቀረው። ጉዳዩ በህግ እንዳያስጠይቃቸውም ይመስላል ጽሁፉ ላይ ነጭ ቀለም ነው የደፉበት። የምግብ ቤቷ ትራንስፎርሜሽን መሆኑ ነው። የዚህ ትራንስፎርሜሽን ትርጉም የገባቸውም ሆነ ያልገባቸው ተስተናጋጆች ወደ ገሊላ (ምግብ ቤት) ጎራ ማለታቸው አልቀረም። የዚህች ቤት አዲሶቹ ደንበኞች በአነስተኛና ጥቃቅን የተደራጁ ወጣቶች ናቸው። እዚያ ሲገቡ ሰልፍ ይጠብቃቸዋል። ይህች ስፍራ ስፋትዋ ለምግብ ቤት በቂ ነበር። ለቀን አልጋ አገልግሎት ግን ትንሽ ስለጠበበች ነው ሰልፍ ሊከሰት ያቻለው። ተራ የደረሳቸው በመጀመርያ ሜኑ ይቀርብላቸዋል። የቀድሞው የምግብ ሜኑ በወይዛዝርት ፎቶ ተቀይሯል።…

ይህ ዘርፍ አሁን ከኮብልስቶንም የበለጠ አዋጭ እየሆነ በመምጣቱ፤ ምግብ ቤቶች የአገልግሎት አይነታቸውንና የሜኑ ደብተራቸውን እየቀየሩት መሆናቸው እውነት ነው።

የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ወሬ መሰማት ከተጀመረ ትንሽ ዘገየ። ይህ አዋጅ ከተሰማ በኋላ የእርሻ፣ የኢንዱስትሪና የሃይል አቅርቦቶች በሙሉ በአስር እጥፍ ነው ያደጉት። እድገታቸው ታዲያ ወደላይ ሳይሆን እንደባህር ዛፍ ወደታች ነው። በእርግጥ የለውጥ ምልክቶች በሀገሪቱ እየታዩ ነው ከተባለ የዝሙት ኢንደስትሪው በደንብ ለመጠቀስ ይችላል። ይህ ዘርፍ በተለይ ከአረብ ሃገር የበርካታ ቱሪስቶች መስህብ ሆኗል። በዚያን ሰሞን አንድ በአዲስ አበባ የሚታተም ጋዜጣ ድንግልና በአስር ሺህ ብር እንደሚሸጥ አስነብቦን ነበር። አንዲት ደናግል ለዚህ ጸያፍ ነገር ስትዳረግ ድህነትን ብቻ አይደለም የምትሰናበተው። የማንነትዋ መግለጫ የሆነው የሞራል ጉዳይም አብሮ ይሄዳል።

የአገልግሎት ክፍያው የሚከናወነው በዶላር መሆኑ ደግሞ በዚህ ዘርፍ ላይ የግሽበት ችግር አይደርስበትም። ኢንደስትሪው ለሃገሪቱ የውጭ ምንዛሪ ምንጭም ስለሆነ ይመስላል ከመንግስት በኩል እየተበረታታ የመጣው። የውጭ ምንዛሪ በማስገኘቱም «ልማታዊ» ተግባር ተብሏል። መንግስት ከዚህ ሴክተር ምን ያህል እንደሚጠቀም በውል ባይታወቅም አገልግሎት ሰጭዎቹ (ደላሎቹ) ግን ሃብታም እንደሆኑ ይነገራል።

ወደ ጎተራ አካባቢ በተሰራው የኮንዶሚንየም መንደር ደግሞ ሌላ ታሪክ አለ። ይህ ኮንዶ «ፌስቡክ» የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል። ለምን ፌስቡክ እንደተባለ ለማወቅ ብዙም ግዜ አይፈጅም። የቆነጃጅት ኮረዳዎች ሁሉ መሰብሰቢያ ነው። ትምህርት አቋርጠው ወይንም ከቤተሰብ ተኮራርፈው የተሰወሩ የቤት ልጆችን ለማግኘት ወላጆች ወደ ፖሊስ ጣብያ መሄድ አቁመዋል። ወደ ጎተራው «ፌስቡክ» ብቅ ካሉ የጠፉትን ሁሉ እዚያ ያገኙዋቸዋል። ባለሃብቶች እና ባለግዜዎች ወጣት ሴቶችን እየወሰዱ እዚያ እንደ እቃ ያስቀምጧቸዋል። ይህን የሚያጫውቱኝ ወዳጆቼ እየሳቁ ነበር የነገሩኝ። ነገሩ ያሳዝናል እንጂ አያስቅም!

በዚህ ልማታዊ «ቢዝነስ» ውስጥ ጨቅላዋ ማሪቱም ገብታበታለች። የማሪቱን ነገር ማንሳቱ ብቻ ሁኔታውን በደንብ ይገልጸዋል።

ይህች ጨቅላ ጉብል በወግና በማዕረግ ያደገችበትን ቀዬ ለቃ ከወጣች አመታት አልፈዋል።  በሃገሬው ሹሩባ ተጎንጉኖ የነበረው ያ ዞማ ጸጉርዋ በፈረስ ጸጉር ተተክቷል። እንደምንጭ ውሃ ጥርት ብለው የነበሩት አይኖችዋ በህብረቀለማት ኩል ተበርዘዋል። በአረንጓዴ ካኪ የተሰፋላት ሽንሽን ቀሚሷ ካላይዋ ላይ ተጥሎ በዘመናዊ ሚኒ-ስከርት ተቀይሯል። ኮንጎ ጫማዋም በሂል ተለውጦ ምቾትዋን ወስዶባታል። ማሪቱ አሁን አዲስ ዓለም ውስጥ ናት። እንደ አሻንጉሊት ሁለመናዋ ሰው-ሰራሽ ሆናለች። ስምዋም ተቀይሯል። አሁን ሜሪ ናት። ማሪቱን ሜሪ ለማድረግ ደላሎቹ ችግር የለባቸውም። ዘመናዊ ልብስ እንጂ ዘመናዊ ስም ወጪ አያስወጣም። ለማሪቱ ከሜሪ ይልቅ ማርታ ወይንም መስከረም ይቀርብ ነበር። እነዚህን ሁለት እርከኖች ዘልሎ ፈረንጅኛው ላይ መሄዱ፣ ምን ያህል ፈጣን የእድገት ጎዳና ላይ መሆናችንን ያሳየናል።

እርግጥ ነው። ማሪቱ በትምህርቷ ገፍታ ሰዎች የደረሱበት ለመድረስ ችሎታውና ፍላጎቱ እንጂ አቅሙ አልነበራትም። እድሜዋ ለአቅመ ሄዋን እንደደረሰ እንደከተሜ እኩዮችዋ ለኮሌጅ ትምህርት አልታደለችም። ወላጆችዋ ብዙም ቅሪት የላቸውም። ለችግር ግዜ አስቀምጠዋት የነበረችውን ገንዘብ ለ«ህዳሴው ግድብ» መዋጮና ቦንድ መግዣ አውለዋት በተስፋ መኖር ጀምረዋል። አዎ ተስፋቸውን ሁሉ በህዳሴው ላይ አድርገዋል።  ግና ተስፋ የእለት ጉርስ አይሆንም።

ሜሪ ድህነትን ለማሸነፍ ስትል የማትወደውን ስራ የመስራት ውሳኔ ላይ ደርሳለች። በውሳኔዋ እንዳትጸጸት የሚያጽናናት ነገርም አለ። «ትምህርት ምን ያደርጋል? የተማረ የት ደረሰ?» የሚለው የወላጆችዋ አባባል በእምሮዋ ውስጥ ያቃጭል ነበር። ይህንን አባባል እንደ ጥቅስ እቤትዋ ላይ ሰቅላዋለች። ከህሊና ወቀሳ ለመሸሽ ስትፈልግ ቀና እያለች ይህንን ጥቅስ ታነብና ትጽናናለች። ታላቅ ወንድምዋ የኢንጅነሪንግ ምሩቅ ነው። የዩኒቨርሲቲ ትምህርቱን እንዳጠናቀቀ ከልጅነቱ ጀምሮ ይመኝ የነበረውን ስራ ሊያገኝ አልቻለም። ይህም፣ ወላጆቹ በትምህርት እና በእውቀት ላይ ተስፋ እንዲቆርጡ አድርጓቸው ነበር። የኋላ-ኋላ ግን የስራ አጡን ጎራ ለማምለጥ አዲስ ስልት ቀየሰ።  የኢህአዴግ አባልነት ፎርም ሞልቶ በጥርነፋ መያዙ ግድ ሆነበት። ከዚያም በ«አነስተኛና ጥቃቅን» ዘርፍ ተደራጅቶ ኮብልስቶን ላይ ተሰማራ። ድንጋይ ሲፈልጥና ሲሸከም ለመዋል መስፈርቱ መብዛቱ ሜሪን አማርሯታል። በመጀመሪያ የዩኒቨርሲቲ ምሩቅ መሆን፣ ከዚያ የአባልነት ፎርም መሙላት፣ ከዚያ በአነስተኛና ጥቃቅን መደራጀት፣ ከዚያ መጠርነፍ…።

በደርግ ግዜ ኑሮ መሯቸው በሱዳን ድንበር ሊጠፉ የነበሩ ወጣቶች፤ ጠረፍ ላይ ሲደርሱ አንድ መፈክር አዩ። “ትግላችን መራራ፣ ጉዟችን እሩቅ፤ ግባችን ረጅም ነው!” የሚል መፈክር። ወጣቶቹ ተስፋ ቆርጠው ጉዟቸውን አቋረጡ። ከዚያም ጫካ ገቡ ይባላል።  ያሁኑ ዘመን ጫካ «ቼቺንያ» የሚባለው መንደር ነው። ሜሪም ወንድሟ ያለፈበትን ረጅም መንገድና አስቸጋሪ መስፈርቶች ማሟላት ስለሚሳናት አጭሩን መንገድ መምረጥ ነበረባት።

በተለይ ከመካከለኛው ምስራቅር የሚመጡ ቱሪስቶች፣ አየር ባየር ነጋዴዎችና ባለስልጣናትም ጎራ እያሉ የሚዝናኑባቸው ማሳጅ ቤቶች እንደአሸን ነው የፈሉት። ከታይላንድ የዝሙት እንደስትሪ የተወረሱ “ሃፒ እንዲንግ” ተግባራት የሞራል ውድቀታችን ምን ያህል እንደወረደ ያሳየናል። እንደዚህ አይነቶቹ ነውር ነገሮች ሁሉ ገቢ እስካስገኙ ድረስ አዋጭ ስራዎች ናቸው። በልማታዊው መንግስታችንም ይበረታታሉ።

ሁሉን ነገር ተነጠቀን የቀረችን አንዲት ነገር ሞራል ብቻ ነበረች። የሞራል እሴቶቻን ግን እንዴት ነው እንዲህ የራቁን? መልካም ስነ-ምግባር፣ ጨዋነት፣ ግብረ-ገብነት እና ፈሪሃ እግዚአብሄር የጠፋበት ህብረተሰብ መጨረሻው ምን ሊሆን ይችላል?  ሃገር ማለት መሬት ብቻ አይደለም። ሃገር ማለት ሕዝብና አንድ ሉዓላዊ አካል ብቻም አይደለም። መልካም ስርዓት እና የሞራል እሴት የሌለው ሃገር ከማፍያ ጉረኖ የተሻለ አይሆንም።

ሌት ተቀን የምንደኖቅርበት እድገትና ትራንስፎርሜሽም የሚመጣው በመጀመርያ ሃገር ስትኖር መሆኑን መገንዘብ ይበጃል። …. የሃይማኖት አባቶችስ ይህንን እያዩ ለምን ዝም አሉ? ስራቸው ፍትሃት ማድረግ እና እና ግብር መሰብሰብ ብቻ መሆን ነበረበት? ወይንስ እነሱንም ይኸው ልማታዊ አስተሳሰብ ተጸናወታቸው?

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am
  • Rusted screws, metal spikes and plastic rubbish: the horrific sexual violence used against Tigray’s women July 4, 2025 01:48 am
  • በሞርሞን ቤ/ክ ዕርዳታ የኪዳነምህረት ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ማምለኪያ ሥፍራ አገኘች July 2, 2025 01:28 pm
  • የበረከት ስምዖን “አየር ላይ ትዕይንት” አየር ላይ ተበተነ July 2, 2025 01:24 am
  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am
  • ከትግራይ ሾልኮ የወጣው ምሥጢራዊው ሰነድ ምንድነው? May 20, 2025 09:18 am
  • በደቡብ ጎንደር በጸዳሉ ደሴ የተመሩት 72 ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ May 19, 2025 02:24 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule