• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

አባይ የኢህአዴግ ኤአርቲ!

June 9, 2013 02:53 am by Editor Leave a Comment

Nile River, Arabic Baḥr Al-Nīl or Nahr Al-Nīl river, the father of African rivers and the longest river in the world. It rises south of the Equator and flows northward through northeastern Africa to drain into the Mediterranean Sea. Encyclopedia Britannica.

በዓለማችን በግዙፍነታቸው ከሚወደሱትና አንቱ ከተባለላቸው ወንዞች መሃል የአባይ ወንዝ /Blue Nile/ግንባር ቀደሙ ነው።ከ6ሺ ኪሎሜትር በላይ ርዝማኔ ያለው የኣለማችን ግዙፉ ወንዝ በርካታ አገሮችን እያቋረጠ የሜዲትሪያንያን ባህርን ይቀላቀላል።

አባይ የሚያቋርጥባቸው አገሮች ደም ስር ሆኖ በማገልገልም ላይ ይገኛል።ምንም እንኳን የአባይ ወንዝ ምንጭና የ80 በመቶ ባለድርሻ አገራችን ኢትዮጵያ ብትሆንም እስከ ዛሬ ከአባይ ያተረፈችው ነገር ቢኖር ግጥምና ዜማ በድምሩ ዘፈን ብቻ ሆኖ እናገኘዋለን።

የእኛው አባይ በተለይ ለሱዳንና ለግብፅ ነፍሳቸው ነው ብል ማጋነን አይሆንብኝም።አባይን ግብፆችና ሱዳኖች ይበሉታል ይጠጡታል ይለብሱታል ያጌጡበታል ይታጠቡበታል ይሞቁበታል ይንቦራጨቁበታል ይነግዱበታል ወዘተረፈ።

ኢትዮጵያውያን ግን የወንዙን አውራ ባለቤትነታችንን ለሱዳንና ለግብፅ አሳልፈን ሰጥተን እነሱ በአባይ ነፍስ ሲዘሩ እኛ ቅኔ እንቀኝላቸዋለን።

አሁንም ቅኔ ድርደራው ቢቀጥልም እስቲ የሆነ ነገር በወንዙ እንስራ በሚል ኢህአዴግ መራሹ የኢትዮጵያ መንግስት ከግድቡ ርዝማኔ ጋር የሚመጣጠን 6ሺ ሜጋዋት ሃይል ማመንጨት የሚያስችል ፕሮጀክት ነድፎ በኢትዮጵያውያን ቦንድ ግዢ ግድቡን መገንባቱን ተያይዞታል።80 ቢሊዮን ብርም ወጪ ይደረግበታል ተብሎ ይገመታል።

አባይ በመገደቡ ላይ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ “ባንዳም ቢሆን ነጭ ለባሽም“ ቢሆን ተቃውሞ የለውም!አራት ነጥብ።

ችግሩ ያለው አባይን የመገደብ ስራ ላይ የሆነ የተለየ አስተያየት የሚሰጥ ወይም ከሌላ አቅጣጫ ነገሮችን አጥንቶ የሚያቀርብ ሰው ወይም ድርጅት እንደ ፀረ-አባይና ኢትዮጵያ ተደርጎ መታየቱ ላይ ነው።በተጨማሪም የአባይ ግድብ ጉዳይ የፖለቲካ ትርፍም ታስቦበት መገባቱ ነው።

የኢህአዴግ አመራር ከፍተኛ ችግር ለኢትዮጵያ ከእኛ በላይ የሚያስብላት የሚጨነቅላት ከእኛ ውጭም የሚመራት የለም ብሎ መታወሩ ነው።እንዲሁም ከሌሎች ምሁራንና ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ለሚመጡት ሃሳቦች ክብደት ያለመስጠትና ገና ከጅምሩ ጭብጦዬን ሊቃመሱኝ ነው በሚል እንደ ጥርኟ በደንብ ሃሳቦችን ሳያላምጥና ሳይቀበል ወደ ማር ጋገራው መሯሯጡም ተጠቃሾች ናቸው።

የጥርኟን ታሪክ የማያውቀው አለ ብዬ ባላምንም ሃሳቡን ግን እንዲህ በአጭሩ እገልጸዋለሁ።“ በአንድ ዘመን ነው አሉ።ጥርኝ ከንብ ማር አሰራር ለመማር ወስና ወደ ንብ ዘንድ ጎራ ትላለች።ጥርኝ አንድ ሃሳብ ከንቧ ሲዘነዘር ይህንንማ አውቃለሁ በሚል ስሜት ስለማር አሰራር ከልቧ ሳታደምጥ ላይ ላዩን እሺ እሺ ብላ ገና መጨረሻውን ንቦ ሳትነግራት በቃ በቃ ከዚህ በላይ ማወቅ አልፈልግም ቻው ገብቶኛል ለዚህ ነው እንዴ ብላ ጥላት ትሄዳለች ።ከዛም ጥርኝ ይኸው እስከዛሬ ማር ትሰራለች ግን ማሯ አይጣፍጥም!“

አዎ ኢህአዴግም ጥርኝ መሆን የለበትም።ረጋ ብሎ ከግራም ከቀኝም ለሚሰነዘሩ ሃሳቦች ጉልህ ቦታ ሊሰጥ ይገባዋል።የሚሰነዘሩት ሃሳቦች ሁሉ ትክክል ላይሆኑ ይችላሉ ግን ሁሉም ሃሳቦች እጅግ በጣም ጠቃሚ ናቸው።

ማንኛውም ኢትዮጵያዊ አስተሳሰቡ ሰይጣናዊም ቢሆን በአገሩ ጉዳይ ላይ እኩል የመደመጥ መብት አለው።ኢህአዴግ ማሩ እንዲጣፍጥለት ከፈለገ ያልተሰሙ ድምፆችንም በንቡ አድምጦ ማስተካከል የሚገባውን ማስተካከል አለበት።

እንዲያውም በሌሎችም አገሮች እንደሚካሄደው ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ያማከለ “ አገራዊ የአባይ ግድብ አማካሪ ቦርድ“ መቋቋም አለበት።ቦርዱ የምሁራን ስብስብ ሆኖ ደጋፊውንም ተቃዋሚውንም ገለልተኛውንም የፖለቲካ ሃይል፤ሌላውንም አስተሳሰብ ያለውን ኢትዮጵያዊ ማካተት አለበት። ምሁራኑ የትም ሊኖሩ ይችላሉ።የቦርዱ አባል በማድረግ የዘመኑን ቴክኖሎጂ በመጠቀም ጭምር ሃሳባቸውን እንዲገልፁ ማድረግ ይገባል።

ከግንባታው በፊት ብንወያይ መልካም ነበር።አሁንም ግን ለውይይት ምንም የረፈደ ነገር የለም።በግንባታና ድህረ-ግንባታ ዙሪያ በርካታና ግራ የሚያጋቡ ሁኔታዎች ሊኖሩ ስለሚችሉ ከወዲሁ ማሰብና በጋራ ጉዳይ ላይ መደማመጥ መከባበር አለብን።

በልማት ምክንያትም ቢሆን ህዝብና መንግስት ገዢ ፓርቲና ተቃዋሚ ላይስማሙ እንደሚችሉም ኢህአዴጎች ማመን አለባችሁ።ይሄ ደግሞ ከዴሞክራሲያዊ አስተሳሰብ መርህ የሚመነጭ በመሆኑ ሊገርም አይገባም።እንደ ተዓምርም ኢህአዴጎች ልታዩት አይገባም።

እዚህ እኔ በምኖርበት ጀርመን የቅርቡን ምሳሌ እንኳን ማንሳት ይቻላል።በጀርመን አገር ሽቱትጋርት 21 የሚባል ግዙፍ የባቡር መስመርና የከተማ ልማት ፕሮጀክት ተነድፎ የአገሪቱ መንግስት 6ነጥብ 5 ቢሊዮን ዩሮ/ከ150 ቢሊዮን ብር በላይ/በጀት መድቦ ስራ ለመጀመር ይፋ ያደረገው ከ20 ዓመት በፊት ነው ስራው ግን ወዲያው እንዳይጀመር ህዝቡና ተቃዋሚዎች የገዢው ፓርቲ /CDU/ ደጋፊዎችም ሳይቀሩ በጉዳዩ ላይ መክረው የከተማዋን ጥንታዊ ታሪክ ያበላሻል በማለት ሲመክሩበት ኖረው ምንም እንኳን ግንባታው የዛሬ ሦስት ዓመት አካባቢ ቢጀመርም በሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞ ፕሮጀክቱ ተቋርጦ ነበር።

ጥቁር ቢጫ በመባል የሚታወቀው የዶክተር አንጌላ ሜርክል ጥምር መንግስት ስለፕሮጀክቱ ለማሳመን ከሶስት አሰርት ዓመታት በላይ በአካባቢው የነበረውን የበላይነት በተቃዋሚዎች የፓርላማ መቀመጫው እስኪነጠቅ ድረስ ጠንክሮ ሰራ እንጂ ጎረቤት አገሮችን እየጠራ የህዝቡን ተቃውሞ ከአሸባሪነት ጋር አልፈረጀም።  በመጨረሻ ከግራም ከቀኝም ነገሮችን ካብላላና ህዝቡምንም ካወያየ በሁዋላ በስምምነት በፕሮጀክቱ ላይ ህዝበ-ውሳኔ እንዲሰጥበት በማድረግ ጉዳዩን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ቋጨው።

ኢህአዴግ ይሄን ለማድረግ አቅም ባይኖረውም የመላውን ህዝብ ይሁንታ ባያገኝ እንኳን በድምፅ ብልጫ ህዝቡ በዘመቻ ገንዘብ ስላዋጣ ብቻ የመላው ህዝብ ሃሳብ ነው ተብሎ ሊወሰድ አይችልም።አባይ ሊገደብ ነው ሲባል ማንም ኢትዮጵያዊ የሆነ ሁሉ ልቡ ትርክክ ብሎ ድህነት ደህና ሰንብች ሊባል ነው በሚል ስሜት አይደለም ገንዘቡን ህይወቱንም ይሰጣል። የተያዘው ፕሮፓጋንዳም ትንሽ መስመሩን የሳተ ይመስላል።ልክ የኢትዮጵያዊነት መለኪያ ይመስል ለአባይ ያዋጣና ያላዋጣ የሚል ስሜትም መንፀባረቅ ጀምሯል።ስለዚህ ኢህአዴግ ፓርቲ ብቻ ሳይሆን ዲፋክቶ መንግስትም በመሆኑ የሌሎችንም ሃሳብ ሊያደምጥ ይገባዋል።

በአንፃሩ እየሆነ ያለው ግን ሌላ ነው።ኢህአዴግ በዘመኑ/በአገዛዙ ለተፈጠሩት መልካም ነገሮችም ይሁን ጥፋቶች ተጠያቂው ራሱ ነው።አባይን ለመገደብ ተነሳስቷል።በጥሩ ታሪክነቱ በዘመኑ ይነገርለታል።ችግር የለውም።የአባይን ወንዝ አቅጣጫ ለማስቀየር ግንቦት 20ን መጠበቅ አያስፈልግም።በጣም የገረመኝ ነገር ቢኖር በዕለቱ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩ አቶ አለማየሁ ተገኑ የአባይ ወንዝን ተፈጥሯዊ አቅጣጫ የማስቀየሩ ተግባር ከግንቦት 20 በዓል ጋር መገጣጠሙ ታሪካዊ ያደርገዋል በማለት ሆን ተብሎ የተሰራን ስራ በቀሽም ንግግር በአደባባይ ሊሸውዱን መሞከራቸው ነው።መቼም ሼም የለም እነሱ ጋር!

በሌላ በኩል ኢትዮጵያዊነት መለኪያው ኢህአዴግነት ነው ብሎ መነሳትም ታሪካዊ ስህተት በመሆኑ ገዝፎ በጥቁር ቀለም መፃፉ አይቀርም።

በየትኛውም ወገን ያለነው ሰዎች በኢትዮጵያዊነታችን የአገሪቱ ጉዳይ ያገባናል።ስለዚህ አንድን ተግባር መደገፍም ይሁን መቃወም ተፈጥሯዊ መብታችን ነው።

ኢህአዴግ የአባይን ግድብ እንደ ኤች አይ ቪ ኤድስ እድሜ ማራዘሚያ /Anti Retroviral Therapy-ART/እየተጠቀመበት ይገኛል።ይሄ አይነቱ ዘዴ ደግሞ እድሜ ያራዝማል እንጂ ለዘላለም አያኖርም ወይም ከሞት አያድንም።

ስለዚህ በልማትም በዴሞክራሲም በሰብዓዊ መብትም ዙሪያ ተቃውሞ ሲነሳ ስም ለመለጠፍ አሸባሪ ድርጅቶችን ማሰስ አያስፈልግም።የተለየ ሃሳብን በማድመጥ ማስረዳት ካልሆነም መቀበል የበታችነት አያሰኝም ይሄ የዴሞክራሲ ሀሁ ነው የታላቅነት መለኪያም ጭምር።

አሁን አሁን ደግሞ በተለይ ከወደ ግብፅ የሚሰሙት የአንዳንድ ሃላፊነት የጎደላቸው ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ፎካሪ ምሁራን አምባጓሮ ጉንጭ አልፋ ንግግር በእኔ እምነት የሚያመጣው ችግር የለም።ምክንያቱም ኢትዮጵያ ለግብፅ የሚጠቅማትን ነገር ነው እየሰራችላት ያለውና።ጦርነት እናድርግ ቢሉም የበለጠ የሚጎዱት እነሱ በመሆናቸው ለጦርነት ጊዜው ረፍዷል። ኢትዮጵያ እንደሆነ ግድቡን ለመስኖ አትጠቀምበትም።ብትጠቀምበት ኖሮ ጦርነቱ አይቀሬ ነው ብሎ መገመት ይቻል ነበር።የኢህአዴግ ስህተት ነው የምንለውም ፕሮጀክቱን ሁሉን አቀፍ አለማድረጉ ነው።

አሁን የወንዙን አቅጣጫ ማስቀየር ከተቻለ ወደፊትም የወንዙን ተፈጥሯዊ አቅጣጫ በማስቀየር ግብፅ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ማድረስ እንደሚቻል የግብፅ የውሃ ባለሙያዎች ሳይቀሩ በልብ ያምኑታል።የሱዳንም አቋም ከኢትዮጵያ ጋር መስማማቱ ለግብፆች ለራሳቸው ሌላ ራስ ምታት ይሆንባቸዋል።ስለዚህ የእንቶኔን ጠባሳ ያየ በእሳት አይጫወትም ነውና ነገሩ ጦርነት ለጊዜው ስጋት አይደለም።

ሁለቱም መንግስታት በውስጥ ችግሮቻቸው የተተበተቡ በመሆናቸውም ደፍረው ወደ ጦርነቱ አይገቡም።

በመሆኑም ግብፅ እብድ መንግስት ቢኖራትም ጦርነቱን አትጀምርም።የሚደርስባት ኪሳራ ቀላል አይሆንምና በእኛ ጦር ሃይል ሳይሆን ወንዙን ወደ ግብፅ ከማፍሰስ ወደ ኢትዮጵያ የተለያዩ ክልሎች በማፍሰስ የግብፅን ጉሮሮ ማንጣጣት ይቻላልና።

ስለዚህ የግብፅ ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ፎካሪ ምሁራን አካኪ ዘራፍ ለኢህአዴግ የዕድሜ ማራዘሚያ ግብዓትነት ከመዋል ያለፈ ጥቅም የላቸውም።

ኢህአዴግም ሆነ የሚመራው መንግስት ይህን በአባይ ላይ እየተቀዳጀ ያለውን የበላይነት ያጎናፀፈው መላው ኢትዮጵያዊ መሆኑን አምኖ ለመላው ኢትዮጵያዊ ጆሮውን ከፍቶ ሊያደምጠው ይገባል። ለአገራዊ የጋራ ህዝባዊ አንድነትም ሊጠቀምበት ይገባል።ፓርቲ ሌላ አገር ሌላ ነውና።ቸር እንሰንብት! (ፎቶ፡ በጸሃፊው የተላከ)

ጋዜጠኛ መስፍን ኣብርሃ/ጀርመን

የጥላ መፅሔት መስራችና ዋና ስራ አስኪያጅ

በጽሑፉ ላይ ግብረ-መልስ ለመስጠት ከፈለጉ በተከታዩ አድራሻ ጸሓፊውን ማግኘት ይችላሉ። tilamagazine@yahoo.de

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የጃኖ ስጦታና የዶሮ ፖለቲካ በጎንደር March 10, 2026 09:24 am
  • “አዲሷ” ኢህአፓ፤ ከንፈሯን ቀለም የተቀባች አሳማ February 25, 2026 11:24 am
  • የተንጋደደው የገዱ መልስ February 6, 2026 03:05 pm
  • ሻዕቢያ “አክሱም ገብቶ ወጣቶች በጅምላ ሲረሽን ጸብ ተፋፍሟል …” February 4, 2026 01:15 pm
  • አደራ ጠባቂው የኢሉአባቦር ሕዝብ February 4, 2026 12:14 pm
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን January 28, 2026 09:56 am
  • በአሜሪካ ጥምር ዜግነት እንዲቀር ጥያቄ ቀረበ January 27, 2026 03:05 pm
  • “ከህወሓት፣ ከሻዕቢያ፣ ከግብፅ ሰዎች ጋር ሆኖ እንዴት የአማራን ጥያቄ ማስመለስ ይቻላል?” ኮሎኔል ፈንታው January 25, 2026 04:23 am
  • የኢትዮጵያ አየር ኃይል: ለአፍሪካ ሀገራት የመጀመሪያዎቹን የአየር ኃይል አብራሪዎች ያሰለጠነ ተቋም January 25, 2026 03:50 am
  • የአማረ ሪፖርተር እያደረሰ ያለው የብሔራዊ ደኅንነት አደጋ January 22, 2026 01:56 am
  • የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የማርያምን ማዕረግ ዝቅ አደረገች December 12, 2025 09:27 pm
  • ኢህአፓ: ከነጭ ሽብር ወደ “አዲስ አበባ ትናገር” የጎዳና ሽብር? December 12, 2025 09:11 pm
  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule