
Nile River, Arabic Baḥr Al-Nīl or Nahr Al-Nīl river, the father of African rivers and the longest river in the world. It rises south of the Equator and flows northward through northeastern Africa to drain into the Mediterranean Sea. Encyclopedia Britannica.
በዓለማችን በግዙፍነታቸው ከሚወደሱትና አንቱ ከተባለላቸው ወንዞች መሃል የአባይ ወንዝ /Blue Nile/ግንባር ቀደሙ ነው።ከ6ሺ ኪሎሜትር በላይ ርዝማኔ ያለው የኣለማችን ግዙፉ ወንዝ በርካታ አገሮችን እያቋረጠ የሜዲትሪያንያን ባህርን ይቀላቀላል።
አባይ የሚያቋርጥባቸው አገሮች ደም ስር ሆኖ በማገልገልም ላይ ይገኛል።ምንም እንኳን የአባይ ወንዝ ምንጭና የ80 በመቶ ባለድርሻ አገራችን ኢትዮጵያ ብትሆንም እስከ ዛሬ ከአባይ ያተረፈችው ነገር ቢኖር ግጥምና ዜማ በድምሩ ዘፈን ብቻ ሆኖ እናገኘዋለን።
የእኛው አባይ በተለይ ለሱዳንና ለግብፅ ነፍሳቸው ነው ብል ማጋነን አይሆንብኝም።አባይን ግብፆችና ሱዳኖች ይበሉታል ይጠጡታል ይለብሱታል ያጌጡበታል ይታጠቡበታል ይሞቁበታል ይንቦራጨቁበታል ይነግዱበታል ወዘተረፈ።
ኢትዮጵያውያን ግን የወንዙን አውራ ባለቤትነታችንን ለሱዳንና ለግብፅ አሳልፈን ሰጥተን እነሱ በአባይ ነፍስ ሲዘሩ እኛ ቅኔ እንቀኝላቸዋለን።
አሁንም ቅኔ ድርደራው ቢቀጥልም እስቲ የሆነ ነገር በወንዙ እንስራ በሚል ኢህአዴግ መራሹ የኢትዮጵያ መንግስት ከግድቡ ርዝማኔ ጋር የሚመጣጠን 6ሺ ሜጋዋት ሃይል ማመንጨት የሚያስችል ፕሮጀክት ነድፎ በኢትዮጵያውያን ቦንድ ግዢ ግድቡን መገንባቱን ተያይዞታል።80 ቢሊዮን ብርም ወጪ ይደረግበታል ተብሎ ይገመታል።
አባይ በመገደቡ ላይ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ “ባንዳም ቢሆን ነጭ ለባሽም“ ቢሆን ተቃውሞ የለውም!አራት ነጥብ።
ችግሩ ያለው አባይን የመገደብ ስራ ላይ የሆነ የተለየ አስተያየት የሚሰጥ ወይም ከሌላ አቅጣጫ ነገሮችን አጥንቶ የሚያቀርብ ሰው ወይም ድርጅት እንደ ፀረ-አባይና ኢትዮጵያ ተደርጎ መታየቱ ላይ ነው።በተጨማሪም የአባይ ግድብ ጉዳይ የፖለቲካ ትርፍም ታስቦበት መገባቱ ነው።
የኢህአዴግ አመራር ከፍተኛ ችግር ለኢትዮጵያ ከእኛ በላይ የሚያስብላት የሚጨነቅላት ከእኛ ውጭም የሚመራት የለም ብሎ መታወሩ ነው።እንዲሁም ከሌሎች ምሁራንና ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ለሚመጡት ሃሳቦች ክብደት ያለመስጠትና ገና ከጅምሩ ጭብጦዬን ሊቃመሱኝ ነው በሚል እንደ ጥርኟ በደንብ ሃሳቦችን ሳያላምጥና ሳይቀበል ወደ ማር ጋገራው መሯሯጡም ተጠቃሾች ናቸው።
የጥርኟን ታሪክ የማያውቀው አለ ብዬ ባላምንም ሃሳቡን ግን እንዲህ በአጭሩ እገልጸዋለሁ።“ በአንድ ዘመን ነው አሉ።ጥርኝ ከንብ ማር አሰራር ለመማር ወስና ወደ ንብ ዘንድ ጎራ ትላለች።ጥርኝ አንድ ሃሳብ ከንቧ ሲዘነዘር ይህንንማ አውቃለሁ በሚል ስሜት ስለማር አሰራር ከልቧ ሳታደምጥ ላይ ላዩን እሺ እሺ ብላ ገና መጨረሻውን ንቦ ሳትነግራት በቃ በቃ ከዚህ በላይ ማወቅ አልፈልግም ቻው ገብቶኛል ለዚህ ነው እንዴ ብላ ጥላት ትሄዳለች ።ከዛም ጥርኝ ይኸው እስከዛሬ ማር ትሰራለች ግን ማሯ አይጣፍጥም!“
አዎ ኢህአዴግም ጥርኝ መሆን የለበትም።ረጋ ብሎ ከግራም ከቀኝም ለሚሰነዘሩ ሃሳቦች ጉልህ ቦታ ሊሰጥ ይገባዋል።የሚሰነዘሩት ሃሳቦች ሁሉ ትክክል ላይሆኑ ይችላሉ ግን ሁሉም ሃሳቦች እጅግ በጣም ጠቃሚ ናቸው።
ማንኛውም ኢትዮጵያዊ አስተሳሰቡ ሰይጣናዊም ቢሆን በአገሩ ጉዳይ ላይ እኩል የመደመጥ መብት አለው።ኢህአዴግ ማሩ እንዲጣፍጥለት ከፈለገ ያልተሰሙ ድምፆችንም በንቡ አድምጦ ማስተካከል የሚገባውን ማስተካከል አለበት።
እንዲያውም በሌሎችም አገሮች እንደሚካሄደው ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ያማከለ “ አገራዊ የአባይ ግድብ አማካሪ ቦርድ“ መቋቋም አለበት።ቦርዱ የምሁራን ስብስብ ሆኖ ደጋፊውንም ተቃዋሚውንም ገለልተኛውንም የፖለቲካ ሃይል፤ሌላውንም አስተሳሰብ ያለውን ኢትዮጵያዊ ማካተት አለበት። ምሁራኑ የትም ሊኖሩ ይችላሉ።የቦርዱ አባል በማድረግ የዘመኑን ቴክኖሎጂ በመጠቀም ጭምር ሃሳባቸውን እንዲገልፁ ማድረግ ይገባል።
ከግንባታው በፊት ብንወያይ መልካም ነበር።አሁንም ግን ለውይይት ምንም የረፈደ ነገር የለም።በግንባታና ድህረ-ግንባታ ዙሪያ በርካታና ግራ የሚያጋቡ ሁኔታዎች ሊኖሩ ስለሚችሉ ከወዲሁ ማሰብና በጋራ ጉዳይ ላይ መደማመጥ መከባበር አለብን።
በልማት ምክንያትም ቢሆን ህዝብና መንግስት ገዢ ፓርቲና ተቃዋሚ ላይስማሙ እንደሚችሉም ኢህአዴጎች ማመን አለባችሁ።ይሄ ደግሞ ከዴሞክራሲያዊ አስተሳሰብ መርህ የሚመነጭ በመሆኑ ሊገርም አይገባም።እንደ ተዓምርም ኢህአዴጎች ልታዩት አይገባም።
እዚህ እኔ በምኖርበት ጀርመን የቅርቡን ምሳሌ እንኳን ማንሳት ይቻላል።በጀርመን አገር ሽቱትጋርት 21 የሚባል ግዙፍ የባቡር መስመርና የከተማ ልማት ፕሮጀክት ተነድፎ የአገሪቱ መንግስት 6ነጥብ 5 ቢሊዮን ዩሮ/ከ150 ቢሊዮን ብር በላይ/በጀት መድቦ ስራ ለመጀመር ይፋ ያደረገው ከ20 ዓመት በፊት ነው ስራው ግን ወዲያው እንዳይጀመር ህዝቡና ተቃዋሚዎች የገዢው ፓርቲ /CDU/ ደጋፊዎችም ሳይቀሩ በጉዳዩ ላይ መክረው የከተማዋን ጥንታዊ ታሪክ ያበላሻል በማለት ሲመክሩበት ኖረው ምንም እንኳን ግንባታው የዛሬ ሦስት ዓመት አካባቢ ቢጀመርም በሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞ ፕሮጀክቱ ተቋርጦ ነበር።
ጥቁር ቢጫ በመባል የሚታወቀው የዶክተር አንጌላ ሜርክል ጥምር መንግስት ስለፕሮጀክቱ ለማሳመን ከሶስት አሰርት ዓመታት በላይ በአካባቢው የነበረውን የበላይነት በተቃዋሚዎች የፓርላማ መቀመጫው እስኪነጠቅ ድረስ ጠንክሮ ሰራ እንጂ ጎረቤት አገሮችን እየጠራ የህዝቡን ተቃውሞ ከአሸባሪነት ጋር አልፈረጀም። በመጨረሻ ከግራም ከቀኝም ነገሮችን ካብላላና ህዝቡምንም ካወያየ በሁዋላ በስምምነት በፕሮጀክቱ ላይ ህዝበ-ውሳኔ እንዲሰጥበት በማድረግ ጉዳዩን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ቋጨው።
ኢህአዴግ ይሄን ለማድረግ አቅም ባይኖረውም የመላውን ህዝብ ይሁንታ ባያገኝ እንኳን በድምፅ ብልጫ ህዝቡ በዘመቻ ገንዘብ ስላዋጣ ብቻ የመላው ህዝብ ሃሳብ ነው ተብሎ ሊወሰድ አይችልም።አባይ ሊገደብ ነው ሲባል ማንም ኢትዮጵያዊ የሆነ ሁሉ ልቡ ትርክክ ብሎ ድህነት ደህና ሰንብች ሊባል ነው በሚል ስሜት አይደለም ገንዘቡን ህይወቱንም ይሰጣል። የተያዘው ፕሮፓጋንዳም ትንሽ መስመሩን የሳተ ይመስላል።ልክ የኢትዮጵያዊነት መለኪያ ይመስል ለአባይ ያዋጣና ያላዋጣ የሚል ስሜትም መንፀባረቅ ጀምሯል።ስለዚህ ኢህአዴግ ፓርቲ ብቻ ሳይሆን ዲፋክቶ መንግስትም በመሆኑ የሌሎችንም ሃሳብ ሊያደምጥ ይገባዋል።
በአንፃሩ እየሆነ ያለው ግን ሌላ ነው።ኢህአዴግ በዘመኑ/በአገዛዙ ለተፈጠሩት መልካም ነገሮችም ይሁን ጥፋቶች ተጠያቂው ራሱ ነው።አባይን ለመገደብ ተነሳስቷል።በጥሩ ታሪክነቱ በዘመኑ ይነገርለታል።ችግር የለውም።የአባይን ወንዝ አቅጣጫ ለማስቀየር ግንቦት 20ን መጠበቅ አያስፈልግም።በጣም የገረመኝ ነገር ቢኖር በዕለቱ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩ አቶ አለማየሁ ተገኑ የአባይ ወንዝን ተፈጥሯዊ አቅጣጫ የማስቀየሩ ተግባር ከግንቦት 20 በዓል ጋር መገጣጠሙ ታሪካዊ ያደርገዋል በማለት ሆን ተብሎ የተሰራን ስራ በቀሽም ንግግር በአደባባይ ሊሸውዱን መሞከራቸው ነው።መቼም ሼም የለም እነሱ ጋር!
በሌላ በኩል ኢትዮጵያዊነት መለኪያው ኢህአዴግነት ነው ብሎ መነሳትም ታሪካዊ ስህተት በመሆኑ ገዝፎ በጥቁር ቀለም መፃፉ አይቀርም።
በየትኛውም ወገን ያለነው ሰዎች በኢትዮጵያዊነታችን የአገሪቱ ጉዳይ ያገባናል።ስለዚህ አንድን ተግባር መደገፍም ይሁን መቃወም ተፈጥሯዊ መብታችን ነው።
ኢህአዴግ የአባይን ግድብ እንደ ኤች አይ ቪ ኤድስ እድሜ ማራዘሚያ /Anti Retroviral Therapy-ART/እየተጠቀመበት ይገኛል።ይሄ አይነቱ ዘዴ ደግሞ እድሜ ያራዝማል እንጂ ለዘላለም አያኖርም ወይም ከሞት አያድንም።
ስለዚህ በልማትም በዴሞክራሲም በሰብዓዊ መብትም ዙሪያ ተቃውሞ ሲነሳ ስም ለመለጠፍ አሸባሪ ድርጅቶችን ማሰስ አያስፈልግም።የተለየ ሃሳብን በማድመጥ ማስረዳት ካልሆነም መቀበል የበታችነት አያሰኝም ይሄ የዴሞክራሲ ሀሁ ነው የታላቅነት መለኪያም ጭምር።
አሁን አሁን ደግሞ በተለይ ከወደ ግብፅ የሚሰሙት የአንዳንድ ሃላፊነት የጎደላቸው ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ፎካሪ ምሁራን አምባጓሮ ጉንጭ አልፋ ንግግር በእኔ እምነት የሚያመጣው ችግር የለም።ምክንያቱም ኢትዮጵያ ለግብፅ የሚጠቅማትን ነገር ነው እየሰራችላት ያለውና።ጦርነት እናድርግ ቢሉም የበለጠ የሚጎዱት እነሱ በመሆናቸው ለጦርነት ጊዜው ረፍዷል። ኢትዮጵያ እንደሆነ ግድቡን ለመስኖ አትጠቀምበትም።ብትጠቀምበት ኖሮ ጦርነቱ አይቀሬ ነው ብሎ መገመት ይቻል ነበር።የኢህአዴግ ስህተት ነው የምንለውም ፕሮጀክቱን ሁሉን አቀፍ አለማድረጉ ነው።
አሁን የወንዙን አቅጣጫ ማስቀየር ከተቻለ ወደፊትም የወንዙን ተፈጥሯዊ አቅጣጫ በማስቀየር ግብፅ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ማድረስ እንደሚቻል የግብፅ የውሃ ባለሙያዎች ሳይቀሩ በልብ ያምኑታል።የሱዳንም አቋም ከኢትዮጵያ ጋር መስማማቱ ለግብፆች ለራሳቸው ሌላ ራስ ምታት ይሆንባቸዋል።ስለዚህ የእንቶኔን ጠባሳ ያየ በእሳት አይጫወትም ነውና ነገሩ ጦርነት ለጊዜው ስጋት አይደለም።
ሁለቱም መንግስታት በውስጥ ችግሮቻቸው የተተበተቡ በመሆናቸውም ደፍረው ወደ ጦርነቱ አይገቡም።
በመሆኑም ግብፅ እብድ መንግስት ቢኖራትም ጦርነቱን አትጀምርም።የሚደርስባት ኪሳራ ቀላል አይሆንምና በእኛ ጦር ሃይል ሳይሆን ወንዙን ወደ ግብፅ ከማፍሰስ ወደ ኢትዮጵያ የተለያዩ ክልሎች በማፍሰስ የግብፅን ጉሮሮ ማንጣጣት ይቻላልና።
ስለዚህ የግብፅ ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ፎካሪ ምሁራን አካኪ ዘራፍ ለኢህአዴግ የዕድሜ ማራዘሚያ ግብዓትነት ከመዋል ያለፈ ጥቅም የላቸውም።
ኢህአዴግም ሆነ የሚመራው መንግስት ይህን በአባይ ላይ እየተቀዳጀ ያለውን የበላይነት ያጎናፀፈው መላው ኢትዮጵያዊ መሆኑን አምኖ ለመላው ኢትዮጵያዊ ጆሮውን ከፍቶ ሊያደምጠው ይገባል። ለአገራዊ የጋራ ህዝባዊ አንድነትም ሊጠቀምበት ይገባል።ፓርቲ ሌላ አገር ሌላ ነውና።ቸር እንሰንብት! (ፎቶ፡ በጸሃፊው የተላከ)
ጋዜጠኛ መስፍን ኣብርሃ/ጀርመን
የጥላ መፅሔት መስራችና ዋና ስራ አስኪያጅ
በጽሑፉ ላይ ግብረ-መልስ ለመስጠት ከፈለጉ በተከታዩ አድራሻ ጸሓፊውን ማግኘት ይችላሉ። tilamagazine@yahoo.de
Leave a Reply