• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

መስከረም፣ መስከረም

September 16, 2017 01:57 am by Editor 2 Comments

ኢዮሃ አበባዬ / መስከረም ጠባዬ
ኢዮሃ አበባዬ / መስከረም ጠባዬ …

የወራት ሁሉ ቁንጮ መስከረም። ግንቦት እሳት፣ ሰኔ ውኃ ነው። የኢትዮጵያ ምድር በእሳትና በውኃ ሳትጠመቅ እረፍት እና ልምላሜዋን አታጋራም። ከግንቦት ማብቂያ እስከ መስከረም መጀመሪያ ሦስት ወር ብቻ ቢሆንም፣ እስኪጠባ መጠበቁ ሦስት ዓመት ያስመስለዋል። የመከራ አንዱ ቀን እንደ ዘላለም ነው፤ እግሮቹም በብረት ሰንሰለት ከብደዋል። ደስታ ግን ክንፍ እንጂ እግር የለው።meskerem1

ግንቦት ድርቅና ብክነት ነው። መስከረም እረፍትና ልምላሜ። ወራት መኳንንት ቢሆኑ መስከረም ንጉሥ ነው። መስከረም ደጅ ያስጠናል። ደጁን ካልከፈተ፣ ፊት ከነሳ ጥቅምትን ማየት አይቻል። አስራ ሁለቱን ወር እንደ ምን ተንፏቆ የደረሰ፣ አምስት እና ስድስት ቀን ጨምሮ ደጅ ይጠናል፤ ራሱንና ጓዳውን እንዲያዘገጃጅ ይገደዳል።

ይህን ያህል ርቀት ተጕዘው ለጥቂት ከደጅ የሚቀሩ አሉ። የሰኔ ጎርፍ ጠርጎ ወሰዳቸው የተባሉ ነፍስና ሥጋቸውን በጥርሳቸው አንጠልጥለው የሐምሌና የነሐሴን ሙላት ተሻገሩ። ሌላው ዳር ቆሞ የደረሱለትንና ያልደረሱለትን ምኞቶቹን ይከልሳል፤ ያመላልሳል። ሆያ ሆዬ ይላል። ሙልሙል ይጎረድማል።

እንደ ሞት ብቅ ይላል፤ መስከረም ሳይታሰብ ብቅ ይላል፤ እንዳላስጠበቀ ሌቱን ገስግሶ ከተፍ ይላል። ያለፈውን ዘመን አስረጅቶ ቀብሮ፣ አዲስ ሕይወት አዲስ ተስፋ ደግሶ ይቀበላል። “ሕይወት እነሆ!” ይላል።

መስከረም፣ እንቁጣጣሽ እንቁጣጣሽ ይላል፤ ጉዝጓዝ ሣር ትኵስ ቡና ይሸታል። እንኳን ደህና መጣሽ። ዓመት ዓመት ያምጣሽ፣
ኢዮሃ አበባዬ / መስከረም ጠባዬ
ኢዮሃ አበባዬ / መስከረም ጠባዬ
መስከረም ሲጠባ
ወደ አገሬ ልግባ …

የግንቦት ሕጻናት ቢይና አፈር ያቦናሉ፣ አፈር ያፍሳሉ፤ ንፍሮና ቆሎ ያፍሳሉ፤ ጠግበው ቁቅ ይላሉ። የመስከረም ሕጻናት እሸት እሸት ይሸታሉ፤ ያስገሳሉ። ቄኪያቸውን ሰው አፍ ላይ ይስላሉ። አበባ ይስላሉ። አደይ አበባ ይለቅማሉ። ወረቀት ያቀልማሉ፤ ለክርስትና አባታቸው ለክርስትና እናታቸው ለሚወዱት አያታቸው ለሚያቀብጣቸው አጎታቸው ለአክስታቸው ለጎረቤታቸው ያበረክታሉ። ስሙኒ ይለቅማሉ። ሜንታ ከረሜላ ይመጠምጣሉ፤ በደስታ ከረሜላ ይደሰታሉ። ቼሬአሊያ ይኮረሽማሉ፤ ጮርናቄ ያላምጣሉ። ይሳሳቃሉ። እንደ ተርብ ይሯሯጣሉ። ግንባር ለግንባር ተላትመው ይላቀሳሉ። ይንከባለላሉ። ይንቦጫረቃሉ። ስሙኒአቸውን ደጋግመው ይቆጥራሉ። ከሸመቱበት ወዲህ ፍራንኩ ማቃጨሉ ለምን እንደ ቀነሰ በጥርጣሬ ያሰላሉ።

ከሐምሌና ከነሐሴ ጎርፍ የተረፉ ይሰባሰባሉ። በየቤቱ በየቤተክርስቲያኑ ይሰባሰባሉ። በየአደባባዩ ይጨፍራሉ። አክ እንትፍ ያበዛሉ። ይገባበዛሉ። ይጎራረሳሉ። በሞቅታ ይንገዳገዳሉ። ይደጋገፋሉ። ሰላምታ ይሰጣጣሉ። ተስፋ ይቀባበላሉ፤ ተስፋ እንደ ማይጉም ይቀባባሉ። መስከረም ደስታ ነው፤ ልምላሜ ነው፤ ንጹሕ አየር ነው፤ ጤና ነው፤ ንቁ እርጥብ ፀሐይ ነው፤ ሰማያዊ ሰማይ ነው፤ የተባዘተ ጥሩ ጥጥ ብሩህ ደመና ነው። ብርሃንም እንደ ዝናብ፣ በታጨደ መስክ ላይ፥ በምድርም ላይ እንደሚንጠባጠብ ጠብታ ነው። የሚካበድ የአድማሳት ጥቁር ቡልኮ ወልቆ፣ እንቅልፍ የሚያስይዝ የሰላምና የሲሳይ ዝናብ ነው። ሰማይ የሚሰነጥቅ ጋራ የሚንድ የነጎድጓድ ድምጽ በወፎች ዝማሬ ሲተካ ነው። የደስታ ጅራፍ የሚያስያነጭ፣ የገደል ማሚቶ ኵልል ብሎ የወጣበት ጤዛ የሚያስመርቅ። መስከረም፣ ዳዊት የሚያስደግም ወር ነው፣

ምድርን ጎበኘሃት፣ አጠጣሃትም / ብልጥግናዋንም እጅግ አበዛህ
የእግዚአብሔር ወንዝ ውኃን የተመላ ነው / ምግባቸውን አዘጋጀህ፣ እንዲሁ ታሰናዳለህና
ትልምዋን ታረካለህ / ቦይዋንም ታስተካክላለህ
በነጠብጣብ ታለሰልሳታለህ / ቡቃያዋንም ትባርካለህ
በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ / ምድረ በዳውም ስብን ይጠግባል
የምድረ በዳ ተራሮች ይረካሉ / ኮረብቶችም በደስታ ይታጠቃሉ
ማሰማርያዎች መንጎችን ለበሱ / ሸለቆችም በእህል ተሸፈኑ
በደስታ ይጮኻሉ፣ ይዘምራሉም። [ዳዊት 65፡9-13]

meskerem2ደጁን አንኳኵተው ለከፈተላቸው መስከረም ግብዣው ብዙ ነው፤ ድግሱ የጦፈ። የጋመ በቆሎ እሸት ጥብስ። ቅቤ ልውስ አንጮቴና ቡና ቀላ። ትኵስ አቦል ቡና ቅቤ በረካ። በአስራ ሁለት የጉራጌ መስቀል፣ በአስራ ስድስት ደመራ፣ በአስራ ሰባት ለተቀረነው መስቀል። ጠፍቶ የከረመው የሚገኝበት፣ እሳትና ዐመድ የተስማማበት። ግንቦት በፀሐይ እሳት ያቦነነውን፣ መስከረም በደመና እሳት አብርዶ ያሳርገዋል።

በአስራ ስምንት፣ ተማሪ ልብሱን አጥቦ ተስፋ ፍለጋ፣ እውቀት ፍለጋ ደብተሩን ይዞ ይራመዳል። ከጳጉሜ [ጳጉሜን፣ ቋቍሜ] መስከረም እስኪሸኝ፣ የአገር ሰላምታ እንደ በረቅ እንደ ነጎድጓድ ከቅርብና ከርቀት ይንጎደጎዳል፤ እንደ ምንጭ ውኃ እንደ ጅረት ይዥጎደጎዳል፦
እንኳን አደረሰህ … እንኳን አደረሰሽ
እንኳን አደረሰሽ … አሜን እንኳን አደረስዎ
እንኳን አደረሰዎ … እንኳን አደረሰሽ
እንኳን አደረሳችሁ … እንኳን አደረስዎ አባባ
ሃፒ ኒው ይር ማዘር … ሃቢኑር ያርግሽ እቴ፣ እንኳን አደረሰሽ በዪልኝ እናትሽን
አደረሳችሁ … ይመስገነው … ክብሩ ይስፋ…

meskerem3መስከረም የወሮች ሁሉ ንጉሥ ነው። የኢትዮጵያ ክልሎች፣ ወረዳዎች፣ አደባባዮች፣ ቀዬዎች እና ጓዳዎች ይዘጋጁ፤ ከሩቅ እጅ ይንሱ፣ ከቅርብ እጅ ይንሱ። የሰላም እሳት ያጋዩ፣ ያደፈውን እና ያረጀውን ያቃጥሉ። የመስቀሉ እሳት ተውሳኩን ያጋይ! የአጋንንትን መንጋ ያክስም። የተስፋ ችቦ ይብራ። በአንድነት ሆ! ይበሉ። የደስታ ሆታቸውን ሸለቆ ሸንተረሩ ጋራና ፈፋው ተቀብሎ ያስተጋባ። “ምነው ተሽኮረመምሽ? እንደ መስቀል ወፍ የት ጠፍተሽ ከረምሽ?” ይባባሉ።

ኢዮሃ አበባዬ / መስከረም ጠባዬ
መስከረም ሲጠባ / አደይ ሲፈነዳ
እንኳን ሰው ዘመዱን / ይጠይቃል ባዳ

ለተቀረው ዓለም፣ አዲስ ዓመት ጥር ነው። ለኛ አዲስ፣ መስከረም ነው።

የሰላምና የምህረት ዓመት ይሁንልን!

© ምትኩ አዲሱ፣ 2010 ዓ.ም

Image credit: skyscrapercity.com; googleimages.com


“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Comments

  1. Mulugeta Andargie says

    September 20, 2017 04:02 am at 4:02 am

    መስከረም!! መስክ አረም!! መስከረም!
    ያዲስ ዓመት ለምለም ወራት! ለምለም!
    ክረምት አላፊ ሃምሌ ነሃሴ!
    ዓዲስ ዓመቱ መጣ ፈሰሴ
    መስከረም ጠባ ወፎች ዘመሩ
    ቢጫው ዓደዩ ሲታይ ማማሩ!
    በየመኩ ላይ ተዘርቶ ፈክቶ
    እንደ መስከረም ማን አለ ከቶ??

    Reply
  2. Mitiku says

    October 1, 2017 12:18 am at 12:18 am

    ውድ ሙሉጌታ፣
    መስከሮምን አሳመርከው አደል? አንተም ይመርብህ!
    ምትኩ

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am
  • ከትግራይ ሾልኮ የወጣው ምሥጢራዊው ሰነድ ምንድነው? May 20, 2025 09:18 am
  • በደቡብ ጎንደር በጸዳሉ ደሴ የተመሩት 72 ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ May 19, 2025 02:24 pm
  • የተመሠረተው የፋኖ አደረጃጀት ዋነኛ ዓላማው ድርድር መሆኑ ተነገረ May 14, 2025 11:07 pm
  • ከፍተኛ የፋኖ አመራሮች መገደላቸው ተነገረ May 6, 2025 10:40 pm
  • ሃይማኖትን ለተራ የፖለቲካ ሸቀጥ ማዋል ውርደት ነው April 24, 2025 12:43 am
  •  የኬሪያ ኢብራሒም ኑዛዜ “ብትንትናችን ወጥቷል” April 22, 2025 12:08 am
  • ለወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞን አመራሮች ወታደራዊ ሥልጠና ተሰጠ April 16, 2025 11:44 pm
  • ዓቅም እንደሌለው የገመገመው ሻዕቢያ ፊቱን ከጦርነት ወደ ዲፕሎማሲ እያዞረ ነው   April 15, 2025 12:32 am
  • “አንድ የፋኖ ተቋም (የእስክንድር) ተመሥርቷል፤ ሌሎቹ ደግሞ እንዲሁ አንድ ተቋም መሥርተው ወደዚህ ይመጡ” አበበ ጢሞ April 11, 2025 12:07 am
  • መለስ (ለገሰ) ዜናዊ – ተዋርዶ ያዋረደን! April 9, 2025 10:28 pm
  • የተከዜ ዘብ: የሉዓላዊነት መጠበቂያ April 8, 2025 11:49 pm
  • አዲስ አበባ አስተዳደር የሪፖርተርን የተዛባ መረጃ ኮነነ፤ ሕጋዊ እርምጃ እወስዳለሁ አለ April 8, 2025 10:06 pm
  • ሀሰተኛውን የሪፖርተር ዘገባ ንግድ ባንክ በጽኑ ተቃወመ፤ እርማትም ጠየቀ April 8, 2025 09:48 pm
  • “ኦሮሚያ ላይ ወይም ሌላ ቦታ ላይ ስታደርገው ከነበረ ትግራይ ወስጥም የማታደርግበት ምንም ምክንያት አይኖርህም” ነው ጌታቸው ረዳ April 7, 2025 10:22 pm
  • “TPLF’s belief in a strong federal government was always tied to its own dominance in Addis Ababa” April 7, 2025 10:15 pm
  • Counter-Video by EBC Challenges EBS Broadcast, Sparks Public Outcry Over Alleged Misinformation March 31, 2025 02:36 am
  • የኤሊያስ መሠረትን ፌክ መረጃ ማን ያጋልጥ? February 19, 2025 06:00 pm
  • አዘርባጃን፡ የሻዕቢያን ሸምቀቆ ማጥበቂያ?! February 19, 2025 12:29 am
  • የአሜሪካ ድምፅ/ቪኦኤ ይዘጋ ተባለ  February 12, 2025 03:37 am
  • የብልፅግና ፓርቲ ሹመኛ ካድሬዎች February 3, 2025 11:07 am
  • ትግሉን የጎዳው የእስክንድር ነጋ አካሄድ February 3, 2025 10:29 am
  • ኤሊያስ መሠረት “ጭምብሉ ዛሬ ወለቀ”፤ ተከፋይ ነው! February 2, 2025 05:32 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule