• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

የማፍረስ አባዜ

January 1, 2013 11:24 am by Editor 3 Comments

በአለፉት ሃያ አንድ ዓመታት፣ በተለይም ከ1997 ዓ.ም. ወዲህ፣ የወያኔ/ኢሕአዴግ አገዛዝ ልዩ መታወቂያው ያደረገው  እያፈረሱ መገንባትን ነው፤ ማፍረስ ቀላል ሥራ ነው፤ ጭንቅላትም፣ ማሰብም አይጠይቅም፤ ልብም፣ ስሜትም አይጠይቅም፤ የሚጠይቀው የዝሆን አካልና ጉልበት ብቻ ነው፤ አንድ ቤተሰብ ስንት ዓመት በዚያ ቤት ውስጥ ኖረ? ጎረቤቶች ምን ዓይነት ትስስር አላቸው? በማኅበር፣ በእድር፣ በዝምድና በቤተ ክርስቲያን ወይም በቤተ መስጊድ፣ በመቃብር፣ በሥራ፣ በአጠቃላይ የእያንዳንዱ ሰው ኑሮ ከልደት ጀምሮ የተፈተለበትና የተደራበት ውስብስብ የኅብረተሰብ አካል መኖሪያ ነው፤ ይህንን አካል ለማፍረስ ትንሽ ጭንቅላትና ግዙፍ ጡንቻ ያለው አይቸግረውም፡፡

መኖሪያ ቤቶችን ማፍረስ፣ መቃብሮችን ማፍረስ፣ የንግድ ድርጅቶችን ማፍረስ፣ ትምህርት ቤቶችን ማፍረስ፣ … ማፍረስ… ማፍረስ… ማፍረስ! ሳያለቅሱ እያስለቀሱ ማፍረስ፤ መሬቱን ማራቆት፣ ሰዎቹን ማራቆት፤ እያፈረሱ ማራቆት፤ እያራቆቱ ማስለቀስ፤ እያስለቀሱ ማፈናቀል፤ እያፈናቀሉ መጣል፤ የሚፈርሰው ቤት ብቻ አይደለም፤ የሚራቆተው መሬት ብቻ አይደለም፤ የሚፈርሰው ሰው ነው፤ የሚፈርሰው ከልደት ጀምሮ የነበረ ጉርብትና ነው፤ የሚፈርሰው ለዘመናት የተገነባ ዝምድና ነው፤ የሚፈርሰው የኑሮ የመደጋገፍ ተስፋ ነው፤ የሚፈርሰው የ‹‹ቀባሪ አታሳጣኝ!›› ጸሎት ነው፤ የሚፈርሰው የአጥቢያና የእድር የቀብር ዋስትና ነው፤ የሚበጣጠሰው ለብዙ ዘመናት የቆየ፣ በደስታና በሐዘን፣ በሳቅና በለቅሶ ማኅበረሰቡን ያስተሳሰረው ገመድ ነው፤ ይህ ለዘለዓለም ጠፍቶ የሚቀር፣ ማንም በምንም የማይተካው ማኅበረሰባዊ ክስረት ነው፤ የትውልድ መቋረጥ ነው፤ የታሪክ መቋረጥ ነው፤ የማይሽር የዜግነት ቁስል ነው፤ ከዜግነት የአገር ባለቤትነት ወደባይተዋርነት፣ ከሰውነት ወደኢምንትነት፣ ወደገለባነት መውረድ ነው፤ መዋረድ ነው፤ የተወለዱበትና ያደጉበት በጉልበተኞች ሲፈርስ አቅመ-ቢስ ሆኖ መፈናቀል፣ አገሬ ነው ባሉት ቦታ ባይተዋር ሆኖ መሰደድ ነው፤ በሌላ አገር ተሰድዶ ሁለተኛ ዜጋ መሆንን የሚመርጡ ሞልተዋል፤ ያውም ከተገኘ!

ይህ ሁሉ ሀሳብ-የለሽ ማፍረስ የሚካሄደው በደሀዎች የኢትዮጵያ ዜጎች ላይ ነው፤ ይህ ሁሉ ሀሳብ-የለሽ ማፍረስ የሚካሄደው በሕገ መንግሥቱ በግልጽ የተዘረዘሩ መብቶች በአሏቸው ሰዎች ላይ ነው፤ በብዙ የዓለም-አቀፍ ሕጎችና ስምምነቶች የታወቁ መብቶች በአሏቸው ሰዎች ላይ ነው፡፡

የማፍረሱን አባዜ ክፋቱን ገልጦ የሚያሳየው አንደኛ አብዛኛውን ጊዜ በክረምት መሆኑ ነው፤ ሁለተኛ ቤታቸው ለሚፈርስባቸው ሰዎች ጊዜያዊ መጠለያ እንኳን ሳይመቻችላቸው ሴቶችና ወንዶች፣ ሕጻናትና ልጆች፣ አሮጊቶችና ሽማግሌዎች፣ ሕመምተኞችና ደካሞች ሜዳ ላይ መውደቃቸው ነው፤ በኢጣልያ ወረራ ጊዜ ያየሁትን እየመረረኝ ልናገር፤ ኢጣልያኖቹ ደህና ደህና ቤቶችን ለሹማምንት ይፈልጉ ነበር፤ ነገር ግን መጀመሪያ ለባለቤቶቹ በመርካቶ ኢንዲጂኖ (የአገሩ ሰው ገበያ) የጭቃ ቤቶች ሠርተው ያስገቧቸው ነበር፤ ባለቤቶቹን ከቤታቸው የሚያስወጡት ወደአዲሶቹ ቤቶቻቸው ካስገቡ በኋላ ነበር፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ነኝ የሚል ከወራሪ የፋሺስት ቄሳራዊ አገዛዝ እንዴት የባሰ መስሎ ይገኛል?

ለመሆኑ እነዚህ ቤቶቻቸው የሚፈርሱባቸው ሰዎች ኢሕአዴግን ከመረጡት 99.7 ከመቶ ውስጥ ያሉ ናቸው ወይስ ከዚያ ውጭ ያሉትና ያልመረጡት እየተፈለጉ ነው?

ቤት አፍራሾቹ ጊዜ የፈቀደላቸው ዘመናዮች ናቸው፤ በእነሱ ጭንቅላት ጊዜ ጸጥ ብሎ የቆመና በእነሱ ጡንቻ ብቻ የሚነጋና የሚመሽ ነው፤ ትዕቢት የሚባለው ይህ ነው፡፡

ቤቶቻቸው፣ የዘመዶቻቸው መቃብሮች፣ የንግድ ድርጅቶቻቸው የፈረሱባቸው ሰዎች ተራ የኢትዮጵያ ዜጎች ናቸው፤ ለእነሱ ዓለም ተደርምሶ ለእነሱም ጊዜ ጸጥ ብሎ ቆሞአል፤ ትናንት ያለፉበት ሁሉ በጨለማ ተውጦአል፤ ትውስታም አልተወላቸውም፤ ነገ በጥላቻና በመረረ ቂም ተጋርዶ ንጋትን አያስመኝም፤ ቢጮሁ ድምጻቸው የማይሰማ፣ አቤት ብለው የሚጮሁበት መድረክ የሌላቸው፣ የእገሌ ያለህ! ወይም በእገሌ አምላክ! የሚሉት የሌላቸው፣ ቀኑ የጨለመባቸው ሰዎች ናቸው፤ አምላካቸው ብቻ ያያቸዋል፤ እንባቸውንም ይሰፍራል፤ ቀኑ ሲደርስም ያስከፍላል፤ የብርዱን ግርፋት፣ የጸሐዩን ጥብሳት፣ ረሀቡንና ጥማቱን ጉልበተኞቹ፣ ትዕቢተኞቹ ባያዩም እግዚአብሔር ያያል፤ አይቶም ይመዘግባል፤ መዝግቦም ዋጋ ያስከፍላል፤ ታሪክም መዝግቦ ለነገው ትውልድ ያስተላልፋል፤ ያፈረሱ የሚፈርሱበትን፣ ያራቆቱ የሚራቆቱበትን፣ ያዋረዱ የሚዋረዱበትን ቀን እግዚአብሔር ያመጣዋል፤ ያኔ ሁሉም እኩል የአገሩ ባለቤት ይሆናል፤ አፍራሽ ጉልበተኛ በሕግ ይታሰራል፤ ደካማውም ደሀ በነጻነት ጉልበትን ያገኛል፡፡

++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++

በቅርቡ ደግሞ ሌላ ዓይነት የማፍረስ ተግባር መጀመሩ ይሰማል፤ ዙሪያውን እየተቆፈረ ስለሆነ የአቡነ ጴጥሮስ ሐውልት ቢፈርስስ? የአጼ ምኒልክ ሐውልት ቢፈርስስ? ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢፈርስስ? ማን ይመክትላቸዋል? እንደ እንግሊዝ፣ እንደ ቤልጂክና እንደሩስያ ኤምባሲዎች ያለ የሚመክት ኃይል በአካባቢው የለም፤ በአንዳንድ አገሮች ለምሳሌ በእንግሊዝ አገር እንኳን ብሔራዊ ታሪክንና ስሜትን ያዘለ ሐውልትና ጥሩ የእርሻ መሬትም ለመንገድ እንዲውል ሕዝቡ አይፈቅድም፤ የሕዝብ ድምጽ ዋጋ ባለው አገር፡፡

ደሞስ እንኳን ሐውልትና አርበኞችን፣ ለአገራቸው ለወገናቸው፣ ሕይወታቸውን ለአደጋ አጋልጠው የቆሰሉትንና የደሙትን፣ ስቃያቸውን ያዩትን ገድለናቸው የለም እንዴ? ሰቅለናቸው የለም እንዴ? በጥይት ደብድበናቸው የለም እንዴ? ባንዳዎቹ አርበኞቹን እየገደሉ ጨርሰው የባንዳዎቹ ልጆች የሚገድሉት አርበኛ ሲያጡ ሐውልት ቢያፈርሱ፣ ወይም የአሉላን ሐውልት ለሌላ፣ የሙሉጌታ ቡሊን መታሰቢያ ለሌላ ቢያደላድሉ አዲሱ ነገር ምንድን ነው? መካብ ሲያቅት ማፍረስ ሥራ ይሆናል፤ ወይም የማፍረስ አባዜ ከያዘ ካላፈረሱ መካብ የማይቻል ይሆናል፡፡

እግዚአብሔርም ያፈርሳል፤ ‹‹ዝናብም ወረደ፤ ጎርፍም መጣ፤ ነፋስም ነፈሰ፤ ያንም ቤት መታው፤ ወደቀም፤ አወዳደቁም ታላቅ ሆነ፡፡›› ማቴ. 7/27

(ፕ/ር መስፍን ወልደ-ማርያም)
ታኅሣሥ 2005

ምንጭ: Mesfin Woldemariam Blog

Print Friendly, PDF & Email

60

SHARES
Share on Facebook
Tweet
Follow us
Share
Share
Share
Share
Share

Filed Under: Opinions Tagged With: Full Width Top, mesfin, Middle Column

Reader Interactions

Comments

  1. በለው ! says

    January 1, 2013 08:24 pm at 8:24 pm

    የአቡነ ጴጥሮስ እና ዳማዊ ምን ልክ ሀውልት ሊፈርስ ነው
    ለመሆኑ ምን ያልፈረሰ አለ? ወደፊት እንዲፈረስ ያልታቀደው የወያኔ ‘ሞኖፖል’ ብቻ ነው። ለአንድ ሀገር ዕድገት መለኪያ የሚሆነው ቤት መሥራት እና መንገድ ማስፋት ነው ብለው የሚያምኑ አፍሪካ መሪዎች በአብዛኛዎቹ በነጭ አለቆቻቸው ሙገሳ አድናቆት ኒሻን እና የክብር ዶክትሬት ሲሸለሙ አይተናል! ዕንባም እየተናነቃቸው ዝናቸውን ሲለፉፉላቸው አይተናል ሰምተናል ተገርመናል ይህም ለእኛ ቤት ሰውዬ ብቻ ሳይሆኑ ሌሎችም ተንቆለጳጵሰዋል… መቼም ከባለቤቱ ያወቀ ቡዳ ነው የአፍሪካ ሕዘብ የሚጠቅመውን ሳያውቅ ሌሎች ስለእሱ ሲመሰክሩ መስማት እራሱ ታላቅ ውርደት ነው። ነገሩ በሆነ ባልከፋ መንገድም ተሰራ ህንፃ በሀገራችን ነው ግን ብዙ ቅድሚያ ሊሰጣቸው የሚገቡ መሠረታዊ ነገሮች አልተሰሩም አድናቂዎቻችንም ተደናቂዎችም የድንቁርና ‘ራዕይ’ አላቸው እንላለን።
    “ጫማ ተጫምቶ ሱሪ ለማጥለቅ የመተናነቅ ቅጥ አንባሩ የጠፋ አባዜ! ይህ ሁሉ አፍረሶ መሥራት ለምን አስፈለገ?
    &&&&&&&&&&&&&&&&&%%%%%%%%%%%%%%%%%
    አድናቆት የተቸረው የቀለበት ማሳላጫ መንገድ ለባቡር ሀዲድ ሲባል በመጠኑ ይፈርሳል…መቶ ዓመት ያስቆጠሩ በቅርስነት መጠበቅ የሚገባቸው ጥንታዊ ህንፃዎች ይፍረሱ!…ለምን? ቢባል ታሪክና ሕዝብ ከኢህአዴግ በፊት አልነበረም የሕገ መንግስቱን ፅሁፍ በጥሞና ያንቡ እያንዳንዳችሁ ከሚከተለው አንዱ ደርሶባችኋል አትደብቁ!!አደራ
    …ዕድር፤ ዕቁብ፣ፀበል ፀዲቅ፣ አድባር፣ አበልጅ፣ ያገር ልጅ፣ ማህበርተኛ፣አብሮ አደግ፣ጉርብትና፣ የትምህርት ቤት ጓደኛ፣ የመሥሪያ ቤት ጓደኛ፣ጋብቻሞች፣የቤተሰብ የቀብር ቦታ፣ተስካር መደገስ(ማስተዛዘን)፣ከጥንት ወዳጅ ጋር ልጅን መዳር፣ በዓመት በዓል(የሥጋ ቅርጫ) መገባበዝ፤ቡና መጠራራት፣ እና ሌሎችም(…)አሁን አሉን ? ? የሉም ! አይኖሩምም !ይህ ከቀጠለ አንድ ትሆናለህ!ትተባበራለህ !ትመክራለህ!ታልማለህ !ትሰባሰባለህ! ትፅፋለህ! ታነባለህ! መብትህን ትጠይቃለህ!ትጠነክራለህ!ግን እላችኋለሁ ወዳጆቼ ወገኖቼ ተሞኛችሁ! ተሸወዳችሁ!እራሳችሁን አጠፋችሁ!! ለሌባ በራችሁን ከፍታችሁ ተዘረፍን ትላላችሁ! ፍቃደኛ ሆናችሁም ስትራዱ ኖራችሁ አሁን የአዞ እንባም ታነባላችሁ? ነውር ነው!!

    ቀበሮ ያህያ ጆሮ ይወድቃል ብላ ስትከተል ውላ ደከማት ጠኔ ይዟት በአፍ ጢሟ ተደፋች አሉ…ያየ ሰው ነው የነገረኝ…የብሔር ብሔረሰቦች ሕዝቦች ከላይ የነበራቸውን (ሕብረሰባዊነት)መብት ሁሉ ጥለው ወያኔ እጥልላችኋለሁ ያላቸውን አማራ መጥፋት እና መውደቅ ሲከተሉ እለግሳችኋለሁ ያለውን መሬት፣ ሥልጣን፣ፍርፋሪ ጥቅም ሲያሳድዱ ህሊናቸውን ሸጡ ካዳሚም ሆኑ ወያኔ ዞሮ ከእላያቸው ላይ ቄጤማ ጎዝጉዞ ጨበሰባቸው!!።

    በሁለት የድሮ የመንግስት ት/ቤት የገጠመኝ…’ከጉዞዬ ማስታውሻ’ ትንሽ ላካፍላችሁ(…) ነባሮቹ በንጉሳን የተሰየሙ ት/ቤቶች ከግማሽ ምዕተ ዓመት በላይ ያስቆጠረ ህንፃ ዘር ሃይማኖት ቋንቋ ዘር ሳይል የድሃ ልጅ ዕውቀት ቀስሞ ለሀገሩ የተሰማራበት እስከዛሬም በእነኝህ ት/ቤት ግብረገብነትን፣ ኢትዮጵያዊነትን አጎልብቶ ትውልዱን የተካ ዜጋ የፈለቀበት ቤት ተከተሉኝ >ኑ>ግቡ> ዛሬ ከመግቢያ በሩ ወደ ትምህርት ክፍሎች ለመሄድ በበጋ ከዘራ በክረምት ጀልባ ያሰፈልግዎታል… ወንበርና ጠረጴዛው ላይ ያለ ሚስማር ለልብስና ለሰውነት አደለም ለዓይን የሚያስፈራ ነው፣ ጣሪያቸው ያፈሳል፣መስኮቶቻቸው የሉም፣ግድግዳው ቀለም የነካው በዚያው በሰገሌ ዘመቻ ጊዜ ነው፣ጥቁር ሰሌዳው ገበጣ ያጫውታል፣የኮርኒሱ ግጥምጣም ተነቅሎ ጠፋ ይላሉ፣ በሮቻቸው አይገጠሙም በድንጋይ ተደግፈዋል፣ መምህር እና ተማሪዎች ይላፋሉ፣በት/ቤቱ አጥር ግቢ ጥጥና አልኮል የያዘች ተንቀሳቃሽ ትንሽ የመጀመሪያ ዕርዳታ መስጫ ሳጥን አለች(አይቻት አሳዘነችኝ!)በባዶ እግሩ የሚሄድ ተማሪ አላየሁም አብዛኛው ተማሪ ያደረገው የቻይና የፕላስቲክ ሲሊፐር ግማሹ አካሉ ተቆረጦ የለም፣ሁሉም ተማሮ(ሪ)ዎች ዩኒፎርም አላቸው ግን የተቀደደ እና የተተለተለ የለበሱት ይበዛሉ፣ሕፃናት ለእስፖርት ግድ ያላቸው አይመስልም የእስፖርት ሜዳው እዳሪ የእርሻ ቦታ መስሏል ልጆች ሲጫወቱ ሲዘሉ ሲቦርቁ አይታዩም ተሰባስበው ተደብተው ቆመውም ተቀምጠው ይታያሉ ሲጮሁ ይሰማል ተነጋግረው መደማመጣቸውን እንጃ…ተጠራጣሪ ፈሪ ድንጉጥ ናቸው።በመንግስት ይሁን በት/ቤቱ አስተዳደር ወጪ በመሠራትም ላይ ያለ የተሰራም አዲስ ሕንፃ አለ ግራ ያጋባው ከመግቢያ በሩ እስከ አዲሱ ህንፃ ያለው መንገድ ጭቃ በቻይና ሲሊፐር ተዝቆ ፎቁ ላይ ወጥቷል በረንዳው ሲታጠብም ሕንፃው ላይ እዥ ፈጠሮ ነባሩ ሕንፃ ከአዲሱ ከውጭ ያምራል ከተሰራ ሁለት ዓመት ያልሆነው ህንፃ መፈረካከስ ጀምሯል። አቤት እየሰሩ ማፍረስ? ?እያፈረሱ መሥራት መፀዳጃ ቤቶች ውሃ መጠጫው አካባቢንም አየሁ!!!
    አሁን ወጣሁ <<<ኑ<<<

    ከዋናው መግቢያ ሙሉ ለሙሉ አጥሩ ፈርሷል።የውስጥ መንገዱን ያልሰራ መሃዲስ? መማሪያ ክፍሎቹን ያላደሰ ምሁር!ቀደም ተከተል የማያውቅ አሰተዳደር? እንዴት? አጥሩ ታየው? ሲመልሱልኝም "ዕድሜው ከ፵ ዓመት በታች የሆነ ሁሉ የኢህአዴግ ልጅ እንጂ ያለፈው ዘመን ልጅ አደለም የድሮውን ታሪክ፣ባሕል፣ሃይማኖት፣ በጭራሽ ሊያውቅ አይገባውም ስለዚህ መፍረስ አለበት።ምክንያት የተደረገው ግን "የዲያስፖራውን ድልድይ" ለመሥራት ሲባል ነው። ድልድዩ እና ት/ቤቱ ምን አገናኘው? ይህ ሁሉ በአንድ መስመር የሚገኝ የ፭ ኤምባሲዎች አጥር ለምን አለፈረሰም? አልሰማኽኝም እንጂ ምክንያት!በቃ የማፍረስ ምክንያት!!(አሁንም የባቡሩ ሀዲድ በምክንያት ሆን ተብሎ በሀውልቶች ላይ የተሰመረ ይሆን??…አዎን ያጫወትኳችሁ ስለ የቀድሞው ት/ቤቴን የቀዳማዊ ኀይለስላሴ አንደኛና ሁለተኛ ት/ቤት(ኮከበ ጽብሐን) ነበር። የመጨረሻውንም ላውጋችሁ ለመሆኑ የግንቡ ጥርብ ድንጋይ እና ሥም ያለበት ብረቶች የት አሉ? አልኳቸው… አዎን, የትምህርት ቤቱ አስተዳደር መልሶ ለመገንባት ወላጆችን ሰብስቦ ገንዘብ እንዲያዋጡ ጠይቋል ሕዝቡም ፍራሹ ንብረት የት ሄደ?ሲል ጠይቋል?። ምላሹ ሌባ ወስዶታል ነው!።ይቺ ነች ጨዋታ!!ለምን መጀመሪያውኑ ፈረሰ ለሚለው ግን በኢንጂነሩ (መሐንዲሱ) በሥራ ተቋራጩ ስሕተት ለድልድዩ መሠራት የሚያደናቅፍ ስለመሰለው!።በለው! በለው!

    የኢትዮጰያ ልጆች ሆይ ! በመጀመሪያ ስሕተት እንቢኝ! ካላላችሁ ሁለተኛ ጥፋት ሆን ተብሎ ይፈፀማል።አራት ነጥብ። እየተለመደም ይሄዳል!። ባህልም ህግም ይሆናል… ቀሪውን በሌላ ጊዜ ታሪክን ቅርስን አብረን እንታደግ የጥፋት ጨርቆችን እናስቁም ከአደራ በቸር ይግጠመን ..በለው! ከሀገረ ከናዳ

    Reply
  2. GetYoh says

    January 2, 2013 09:05 pm at 9:05 pm

    A story with some truth .
    But so one sided that it is not expected from someone with secondary school education.
    It may be enough to convince the diaspora community far from home but not every one else.
    Visit http://www.lonelyplanet.com/themes/best-in-travel-2013/top-10-cities/ for another side of the story

    Reply
  3. ዱባለ says

    January 3, 2013 02:04 am at 2:04 am

    Contrary to woyane’s claim, the economic growth is only 5% as stated in the report in the link provided by GetYoh, which most of it might come out of big influx of aid and borrowed money. The report does not deny unwise destruction of private and community properties by woyane government.

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ቤተሰቦች አስከሬን መውሰድ እንደሚችሉ ተነገረ January 14, 2021 06:48 pm
  • ስብሃት፤ “ከሞትን ቆይተናል፤ … አሁን የቀብር ሥነ-ስርዓታችን” እየተፈጸመ ነው January 14, 2021 01:37 pm
  • “ተመልሰን እንነሳለን” ያሉት ህወሓቶች ተመልሰው ወደማይነሱበት ተሸኙ January 13, 2021 01:12 pm
  • አፋር ነፃ አውጪ (ኡጉጉሙን) ለመጠቀም የታቀደው የህወሃት ሤራ ከሽፏል January 13, 2021 01:10 pm
  • ህወሃትን ወደ ጅቡቲ ለማሻገር ሲሰሩ የነበሩ የአፋር ታጣቂዎች በሰላም ወደ ክልሉ ገቡ January 13, 2021 06:47 am
  • በታህሳስ ወር ብቻ ከ344 ሚሊየን ብር በላይ የኮንትሮባንድ ዕቃ ተያዘ January 13, 2021 06:10 am
  • የብልፅግና ፓርቲ ቀጣይ ፈተና ምን ሊሆን ይችላል? January 13, 2021 04:10 am
  • ለትምህርት እንዲሆነን January 11, 2021 01:20 pm
  • “ከተቀበሩበት የጃርት ጉድጓድ ነው ያወጣናቸው” መቶ አለቃ ስዩም ቱርቦ January 11, 2021 12:11 pm
  • የተደመሰሱና በቁጥጥር ሥር የዋሉ የወንበዴው አባላት ይፋ ሆነ January 7, 2021 01:16 pm
  • ዐቢይና መኮንኖቹ በመቀሌ፤ “ድሉ የመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው” December 13, 2020 02:36 pm
  • ወንበዴው ህወሓት ከ1.4 ትሪሊዮን ብር በላይ ዘርፎ በውጭ አገራት ባንኮች አስቀምጧል December 8, 2020 01:05 am
  • ማይካድራ – የትህነግ የዘር ማጥፋት ጥግ ቋሚ ምስክር December 8, 2020 12:57 am
  • የወልቃይት ጠገዴ እናቶች ሰቆቃ ሲታወስ December 8, 2020 12:50 am
  • የደብረጽዮን ዋሻ December 7, 2020 11:30 pm
  • ባለ ከዘራው ኮሎኔል December 7, 2020 05:15 pm
  • ሰላማዊ ሕይወት በማይጨው December 7, 2020 04:12 pm
  • ተጠርጣሪ የፌዴራልና የአዲስ አበባ ፖሊሶች የመያዣ ትዕዛዝ ወጣባቸው December 7, 2020 11:46 am
  • ከ3 ሺህ በላይ ተተኳሽ ጥይቶች በወልዲያ ጉምሩክ ሊያሳልፉ የሞከሩ 4 ግለሰቦች ተያዙ! December 7, 2020 11:18 am
  • ወንበዴዎቹ ይጠቀሙባቸው የነበሩ ተሽከርካሪዎችና የግል ሰነዶቻቸው ተያዙ December 7, 2020 10:50 am
  • ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ በሶማሌ ክልል ተመሠረተ December 7, 2020 10:31 am
  • የኦነግ ሸኔ አባላትን ዕድሜ ለማሳጠር የጂፒኤስ ቴክኖሎጂ ጥቅም ላይ እየዋለ ነው December 7, 2020 12:38 am
  • የቆሰሉ ወታደሮች በጠቅላይ ሚኒስትሩ ተጎበኙ December 6, 2020 11:41 pm
  • “ከዚህ በኋላ ይዘን እንታገላለን እንጂ ሠጥተን አንጠይቅም” ኮሎኔል ደመቀ December 2, 2020 12:24 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2021 · Goolgule