
የሕይወትን እውነትና ትክክለኛ ትርጉም ተረድተን በሰላምና በፍቅር ለመኖር የሚያስችል የአእምሮ መታደስ ለማድረግ የሚከተለውን ላካፍላችሁ፡
ከሁሉ አስቀድሜ ልረሳው የማልችለውን መልካም ባህላችንን ተጠቅሜ እንኳን ለብርሃነ ልደቱ አደረሰን እላለሁ፤ እኔም ከሃገር፣ ከቤተሰብ፣ ከዘመድና ከጓደኛ ተለይቼ ባህሉንና ወጉን ጠንቅቄ ከማላውቀው ሕዝብ ጋር በእኛ አቆጣጠር ባለፈው ታሕሳስ 16 ቀን 2009 ዓ/ም የፈረንጆችን የገና በአል አክብሬ አሁን ደግሞ የእኛን ታሕሳስ 29 ቀን 2009 ላይ ከኢትዮጵያውያንና ከኤርትራውያን ወገኖቼ ጋር ለማክበር በዝግጅት ላይ ነኝ፤ እዚህ ላይ የቀን ልዩነት ቢኖርም የመከበሩ ዋና ዓላማና የቀኑ ባለቤት የሆነው ግን አንድ ነው፤ እሱም ከድንግል ማርያም ተወልዶ ሰው በመሆን በሰው ልጆች መካከል በመመላለስ “እግዚአብሔር ከእኛ ጋር” ለማለት ድፍረት እንዲሆነን “አማኑኤል” የተባለው ጌታ ኢየሱስ ነው።
ዛሬ ይችን አጭር መልእክት ጽፌ እንድልክ ያነሳሳኝ ዋና ጉዳይ በተለያየ ሚዲያ ሁላችንም እንዳየነው በዚህ የፈረንጆች ክሪስመስ አከባበር ላይ ሰፊ ትኩረት የተሰጠው ጉዳይ ስጦታን እርስበርስ መቀባበል እንጂ የበአሉ ዋና ባለቤት በሆነው ላይ አለመሆኑ አስገርሞኝ ነው፤ በእኛ አገርም ሁሉም እንደ አቅሙ ድፎ ዳቦው፣ ቆሎው፣ ዶሮው፣ በጉ፣ ቅርጫው፣ ጠላው፣ ጠጁ፥ አረቄው ከገና ጨዋታውና ከዘፈኑ ጋር አይቀርበትም፤ ይህን ሳስብ ታዲያ ምንም እንኳን ይህን በመሰለና መጠኑን በጠበቀ መልኩ በአግባቡ ደስ መሰኘቱ ባይከፋም እንደ ባለ አእምሮ ሰው ቆም በማለት የሚከተሉትን ሦስት የሕይወት ጥያቄዎች በማስተዋልና ትኩረት በመስጠት አብረን እንድናያቸው ወደድኩ፡-
1) ይህ በታላቅ ፌስታ የምናከብረው የልደት በዓል በእውነት ባምሳሉ ለክብሩ ለፈጠረው የአዳም ዘር በሙሉ ፋይዳው ምንድር ነው??? የሚለው ወሳኝ የህይወት ጥያቄ ዋናውና የመጀመሪያው ይሆናል ማለት ነው።
መልሱን የሚነግረን በዘላለም ፍቅሩና ምህረቱ ይህንኑ ሥራ የሠራልን ፈጣሪ አምላክ በህያው ቃሉ እንጂ ሰው በራሱ ሊመልስ ይቅርና የሚናገረውንና የሚጠቅመውን እንኳ የሚያውቅ አይመስለኝም፤ ሁሉን ቻይ የሆነው እግዚአብሔርም (በሉቃስ 2፡10-11) ላይ “እነሆ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋልና’’ ይለናል።
ይህን ቃል ለትምህርታችን ዘርዘር በማድረግ አብረን በትእግስት እስቲ እንየው፡- ለሕዝቡ ሁሉ ስላለ ሁላችንንም ይመለከተናል፤ ታላቅ ደስታ በመባሉ ደግሞ ጊዜያዊ የሆነው ሰው ሠራሽ ምድራዊ ደስታ ከሰማይ በመላእክት በኩል የመጣውን ደስታ ፈጽሞ አይተካውም ፤ በአጠቃላይ ከሰማናቸውና ከምንሰማቸው በላይ የሆነና የምሥራች ተብሎ የተነገረ፣ በሚያስፈራ በሽታም ሆነ በሌላ አስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ እንኳን ብንሆን ፍርሃታችንን አስወግዶ ደፋር የሚያደርገንና ፍጹም ፈዋሽ የሆነ የማያዳግም መድሐኒት ከሴቶች መካከል የተባረከች ከተባለች ከድንግል ማርያም ክርስቶስ ብቻ ሳይሆን ጌታና አማኑኤል የሆነ ለእኛ እንደተወለደልን ማስተዋልና የመለኮትን የመድሃኒትነት ስጦታ በቃሉ እንደተነገረን ትእዛዝ/Prescription/ ተቀብለን ሰዎች ከሚሰጡን ጊዜያዊ ስጦታ ባለፈ መልኩ መጠቀም መቻል ብልህነትና አስተዋይነት ይመስለኛል፤ ሕይወት ጅማሬ ብቻ ሳይሆን መጨረሻም አለውና።
እስቲ እዚህ ላይ ስጦታን በተመለከተ ይህን ልበልና ላጠቃል፣ አንድ የሚወደን ሰው ፍቅሩን ለመግለጽ በውድ ዋጋ ገዝቶ በሰርጋችን እለት በብዙ ሕዝብ ፊት ሲሰጠን አልቀበል ብንለው ምን ይሰማው ይሆን? ታዲያ በዮሐንስ ወንጌል 3፡16 ላይ እንደተጠቀሰው በሃጢአት ምክንያት ለሞተው የሰው ዘር በሙሉ ውድ አንድ ልጁን በመድኒትነት የሰጠውን የምህረት አምላክን ስጦታ አልቀበል ብንል ማነው የሚጎዳው? ሰጪው ደስ ብሎት ሲሰጥ ተቀባዩ ገብቶት በመቀበል ካልተጠቀመበት ሰጪውን እስከነስጦታው መናቅ አይሆንብንምን?ደግሞስ ለዚህ ሰሞኑን ለምናከብረው በዓል ምክንያት ስለሆነው ሰማያዊ ስጦታ ሰጪው እንድንመራበት በሰጠን መጽሐፍ ቅዱስ ላይ፡ አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ሰውን ሁሉ ስለመውደዱ /ዮሐ 3፡16/ ለገዛ ልጁ ሳይራራ ስለ ሁላችን በደል አሳልፎ የሰጠው /ሮሜ 8፡32/ ሰዎችን ሁሉ የሚያድን የእግዚአብሔር ጸጋ ተገለጠ….ወዘተ ለሚለው ህያው ቃል እያንዳንዳችን በግል ምን ዓይነት መልስ ይኖረን ይሆን???
2) ሌላው የሕይወት ትክክለኛ ትርጉም በእውነት ምንድር ነው? የሚለው ይሆናል፤ ምናልባት መልሱ፡- መብላት መጠጣት፣ ንብረት ማካበት፣ ማግባትና ልጅ መውለድ፣ እድሜ ጠግቦ ጉዞን መጨረስ ይሆን ይሆናል፤ እነዚህ ሁሉ መልካም ናቸው፤ ነገር ግን ሁሉም ጊዜያዊና ጠፊ በመሆናቸው ብል ሳይበላው ከሞት ባሻገር አብሮ የሚሻገር የዘላለም ርስታችንን በዚች በተበላሸች ምድር እያለን ካላረጋገጥን እጅግ የሚያሳዝን መንፈሳዊ የሕይወት ክስረት ነው የሚሆነውና አሁንም እናስተውል::
3) ጌታ ኢየሱስ በምድር አስተምሮው ላይ ስም ሰጥቶ የሃይማኖት ድርጅት በመመስረት የዚህ ሃይማኖት ተከታይ ካልሆናችሁ መንግሥተ ሰማይ አትገቡብ አላለም፤ ነገር ግን በሩ እኔ ነኝ በእኔ የሚገባ ይድናል/ዮሐ 10፡9/፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም /ዮሐ 14፡6/፤ ልጅም ትወልዳለች እርሱ ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋል /ማቴ 1።21/፤ ልጁ ያለው ሕይወት አለው የእግዚአብሔር ልጅ የሌለው ሕይወት የለውም /1ኛ ዮሐ 5፡12/፤ በአጠቃላይ ከዘፍጥረት እስከ ራእይ ድረስ ያሉት መጽሐፍት የሚናገሩት የምህረት አምላክ የሆነው ቸሩ እግዚአብሔር በኃጢአት ምክንያት ከኤደን ገነት የወጣውን የአዳም ዘር በልጁ ሞትና ትንሳኤ መልሶ ማስገባቱን ነው፤ ወንድም ወንድሙን አያድንምና /መዝ 49፡7/ ስለዚህ የገዛ ክንዱ መድሃኒት አመጣለት /ኢሳ 59፡16/ ስለሚል ባለንበት ሃይማኖት ውስጥ በመሆን መጽሐፍ ቅዱስን ትኩረት ሰጥተን ለማጥናት ቀኑ ሳይመሽ አሁኑኑ እንድንጀምር በእግዚአብሔር ፍቅር ከልቤ አሳስባለሁ፤
ትናንት ላናገኘው አልፏል፤ ነገም የእኛ መሆኑን አናውቅም፤ ዛሬ ግን እንድንጠቀምበት የተሰጠን የእድሜያችን እንቁ ሃብት ነውና ብልህና አስተዋይ እንሁን።
ቸሩ በቸርነቱ ይርዳን!!!
አሜን።
እውነቱ ይነገር ነኝ (eunethiwot@gmail.com)
“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡
እውነት ነው፤ እኛ ሁላችን ልናስብበት የሚገባና ቆም ብለን በማሰብ ድካማችንን በማስወገድ እውነተኛ ማንነታችንን በፍቅርና በሰላም አብረን ለመኖር ብልህ ሰዎች እንሁን!
Agree and liked it very much.
Guys!!! Politics has no truth as mathematics has. It is human philosophy. Otherwise, our theory would be metaphysics. It will not be materialistic. Don’t expect from any politician truth.