• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ሌንጮ ለታ – ታሪክ ሊሰሩ ወይንስ ታሪክ ሊጽፉ…?

February 3, 2014 07:20 am by Editor Leave a Comment

ኢትዮጵያዊው ቱጃር ለለውጥ ብለው በኮንትራት ታክሲ በመሄድ ላይ ናቸው። እሳቸውን የጫነው ታክሲ መስቀል አደባባይ ላይ ሲደርስ በድንገት ቀጥ ብሎ ቆመ። ሾፌሩ ተደናጋጠ። መኪናውን እንደገና ለማስንሳት ብዙ ሞከረ። ከብዙ ሙከራ በኋላ ጥረቱ ስላልተሳካለት ቱጃሩን ለትብብር ጠየቃቸው። እንዲህ ሲል።  “ወጣ ብለው ይግፉ።”  ቱጃሩ በመገረም ሾፌሩን አዩት።  “ይግዙ” ማለትህ ነው ሲሉም መለሱለት። እኚህ ሰው መኪናውን ከመግፋት ይልቅ አዲስ መኪና መግዛት ይቀላቸዋል።  የቤቶች ድራማ ላይ እከ ደከ አስር ጊዜ “እኔን ነው?” የሚለው ወዶ አይደለም። ማመን የሚቸግሩንን ነገሮች ማጣራት ስንፈልግ እንደጋግማለን።

በዚያን ሰሞን በኦቦ ሌንጮ ለታ የወጣው ዜና ብዙዎችን አስገርሟል።

“ሃገር ቤት ገብተን በመታገል አዲስ ታሪክ እንሰራለን።” የሚል ነበር የዜና እወጃው ርዕስ። ይህን ርዕስ እንዳየሁ አይኔን በደንብ ጠረግ ጠረግ አደረግኩና እንደገና አነበብኩት።

“ታሪክ እንሰራለን” የሚለው ሃረግ በስህተት የሰፈረ ነበር የመሰለኝ።  ሌንጮ ለማለት የፈለጉት “ታሪክ እናነባለን” ይሆናል በሚል ጥርጣሬ ደጋግሜ ያየሁት።  ያነበብኩት ነገር ትክክል ነው። ይህንኑ ቃል ከራሳቸው አንደበትም ሠማሁ።  በስህተት የሰፈረ ዜና አልነበረም።  ታሪክን ማንበቡም ሆነ መስራቱ ቀርቶ “ሃገር ቤት ገብተን አዲስ ታሪክ እንጽፋለን።” የሚል ቢሆን እንኳን ግርታውን ይቀንሰው ነበር።

በፍትህ ሳይሆን ይልቁንም በአዋጅ በምትተዳደር ኢትዮጵያ፤ እጅና እግራቸውን ብቻ ይዘው በመግባት ታሪክ መስራት የሚችሉ ከሆነ በምትሃት አልያም በመለኮታዊ ሃይል ብቻ መሆን አለበት። ሌንጮ ሃገር ቤት ገብተው ሰላማዊ ትግል ለማድረግ መወሰናቸው ላይ ምንም ችግር የለብኝም። የዚህ ውሳኔ ትክክለኝነት የሚዳኘው አስቀድመው በሚተቹ እና በሚተነብዩ የፖለቲካ ነብያት አይደለም። ፍርድ የሚሰጠው ሂደቱ በተግባር ሲፈተን ብቻ ይሆናል። ይህን ለማየት ደግሞ ብዙም ሩቅ አይሆንም።  በጎረበጠ የፖለቲካ መንገድ ላይ ጉዞ ለማድረግ ወደ ሃገር ቤት ለመግባት መወሰናቸው ግን አስመራ ላይ፤ በሻእቢያ ከታገቱት የኦነግ መሪዎች የተሻለ ውሳኔ ይመስላል።  ታሪክ ለመስራት አስመራ የመሸጉት እነ ዳውድ ኢብሳ ታሪክ ሆነው ቀርተዋል።

ችግሩ ያለው “ታሪክ እንሰራለን” ማለቱ ላይ ነው። እንደዚህ አይነት የፖለቲካ ትግል ውሳኔ ላይ መድረስ ቀላል ነገር አይደለም። ከመቅጽበት የመጣው ይህ ውሳኔ ልክ እንደ ኦሎምፒክ ውድድር ዝግጅቱን እንዳጠናቀቀ አትሌት ይመስላል። አትሌቲክስም ቢሆን የአካል ብቃትና በቂ ዝግጅትን ይጠይቃል።  ፖለቲካ ደግሞ ዘው ብለው ገብተው ታሪክ የሚሰሩበት በኦሎምፒክ የውድድር መድረክ አይደለም። እነ ሌንጮ እየነገሩን ያሉት አዲስ አበባ ገብተው በባላገሩ አይደል ላይ ለመወዳደር አይደለም። በባላገሩ የጫወታ ደንብ ጥሩ ስራ የሰራም፤ አስቀያሚ ስራ የሰራም ይሸለማል። ሌንጮ ታሪክ እንሰራለን የሚሉት “ስልጣን ወይንም ሞት!” የሚል መፈክር አንግቦ እስካፍንጫው የታጠቀ ሃይልን በመጋፈጥ ነው።odf lencho

ታሪክን ለመስራት ብቃት ያላቸው ድርጅቶች በኢትዮጵያ የፖለቲካ መድረክ ጠፍተው አያውቁም። ከኦሮሞ ድርጅቶችም ቢሆን እነ ኦቦ ቡልቻ ደመቅሳ እና ፕ/ር መረራ ጉዲና አሉ።  የኦሮሞን ህዝብ አደራጅተው በምርጫም፣ በፓርላማም፣ በሰልፍም፣ በእርግማንም፣ በጸሎትና ምልጃም፣  በወረቀትም … ብዙ ተጉዘዋል። የእነዚህ ድርጅቶች አባላት እንደጥጃ እየተለቀሙ እስር ቤቱን ከማጨናነቃቸው በቀር ታሪክ ሲሰሩ አላየንም። አንድ እርምጃ ወደፊት፤ አስር እርምጃ ወደኋላ እየተጓዙ ሄደው…ሄደው በመጨረሻ ራሳቸውም ታሪክ ከመሆን አላለፉም። ይህ ለአቶ ሌንጮ ለታ እንግዳ ነገር አይደለም። አቶ ሌንጮ በኢትዮጵያ የፖለቲካ መድረክ በከባድ ሚዛን ደረጃ የሚመደቡ ናቸው።

በዛሬይቱ ኢትዮጵያ በፖለቲካ ታግሎ ታሪክ ከመስራት ይልቅ ነድጅ ቆፍሮ ታሪክ መስራት እንደሚቀል ለሌንጮም አዲስ ነገር አይደለም። እርግጥ ነው።  የታሪክ ትርጉም አሰጣጣችን ላይ እንለያይ ይሆናል። የገዥው ፓርቲ የታሪክ ትርጉምም ከልማት ጋር ይያያዛል። በዘመናችን ብዙ ታሪኮችን እየሰማን ነው። ልማታዊ አስተሳሰብ ያለው ሰው ሁሉ ዛሬ ታሪክ ሰሪ ይባላል። ታሪክ ሰርተው የሚሸለሙ የልማት አርበኞችን በቴሌቭዥን እናያለን።  በአነስተኛና ጥቃቅን እየተደራጁ የኮብል-ስቶን ድንጋይን እያናገሩ ያሉ ወጣት ምሁራንም በታሪክ መዝገብ ላይ እየሰፈሩ ይገኛል።

ኦቦ ሌንጮ ታሪክ የሚሉን እንዲህ አይነቱን ድራማ እንደማይሆን እርግጠኞች አይደለንም።  እኝህ የፖለቲካ መሪ ታሪክ መስራት ከነበረባቸው ግዜው አሁን አይደለም። በሽግግሩ ዘመን 20 ሺህ ጦር እና 20 መቀመጫ ይዘው በነበሩበት ጊዜ ለዚህ እድሉ ነበራቸው። ያንን እድል ይዘው ታሪክ ከመስራት ይልቅ ድርጅታቸው ጥቁር ነጥብ ጥሎ ነበር ያለፈው።  አቶ ሌንጮ ታሪክ መስራት ከነበረባቸው በሽግግሩ መንግስት የኢትዮጵያ መሪ ሆነው በተመረጡ ግዜ ነበር። በወቅቱ ምን ነበር ያሉት?  “በዚህ ላይ አልተዘጋጀሁበትም።” ሲሉ የእድሉን በር ራሳቸው ዘጉት። በርግጥ ያን ጊዜ ከኦሮሚያ የመገንጠል አዙሪት ውስጥ አልወጡም ነበር። ትልቅ ህዝብን ይዘናል እያሉ፤ የመገንጠል ጥያቄን ሲያነሱ በአለም ላይ የመጀመሪያዎቹ ብቻ አይደሉም። የኦሮሞን ህዝብ በፖለቲካ አናሳ ማድረጋቸው የታያቸውም ከ40 አመታት በኋላ መሆኑ ነው።  በዚያን ወቅት ኢትዮጵያን መምራት እንችላለን ለማለት በራስ መተማመን አልነበራቸውም። አንድ ሰው አንድ ድምጽ በሚል መርህ ምርጫ አድርገው ከመጓዝ ይልቅ፤ እንደ አናሳ ጎሳ “መገንጠል አለብን” የሚል ያታሪክ ስህተት ውስጥ ነበሩ።

ከኦሮሞ ነጻ አውጭ ግንባር ወጥተው የኦሮሞ ዲሞክራቲክ ግንባርን መመስረታቸው ከታሪክ ተወቃጭሽነት ሊያድናቸው ይችላል ። ይህንን በማድረጋቸው የሰማይና የምድርን ያህል ርቆ የነበረውን የፖለቲካ መስመር ሊያጠበው እንደሚችል ግልጽ ነው። ዛሬ የመገንጠልን ጥያቄውን ውድቅ አድርገው ለዲሞክራሲና ለፍትህ መታገል መምረጣቸው ታሪክ ሰሪ ሊያደርጋቸው አይችልም። ይህ ሊሆን የሚችለው ለውጥ አምጥተው ፍትሃዊ ስርዓት ማስፈን ሲችሉ ብቻ ነው።

ሌንጮ ለታ አዲስ አበባ በመግባት ታሪክ እሰራለሁ ሲሉ ይህ የመጀመርያቸውም አይደለም። እ.ኤ.አ. 1993 የስራ ባልደረባቸውን ከከርቸሌ ለማስፈታት አዲስ አበባ ዘው ብለው ገብተው ነበር። እኝህ ሰው ሲገቡ ቦሌ ላይ ልዩ አቀባበል ተደረገላቸው። በብረት ተጠፍረውም ከርችሌ ተወረወሩ። በወቅቱ አዲስ አበባ ላይ ተካሂዶ በነበረው የግዮኑ የሰላም እና እርቅ ጉባዔ ላይ ለመሳተፍ ሲገቡ የታሰሩ ልኡካንን እዚያው ተቀላቀሉ።

ሌንጮ በዚያ ሰዓት ታሪክ ይሰራሉ ብለን ጠብቀን ነበር። ግን ይቅርታ ጠይቀው ከእስር ለመውጣት አንድ ሳምንትም አልፈጀባቸውም።  በወቅቱ ከአቶ ሌንጮ ለታ ጋር ረጅም ቃለ-መጠይቅ አድርጌ ይህንን ታሪክ በማሳትመው ጋዜጣ ላይ ለህዝብ ይፋ አድርጌዋለሁ። እርግጥ ነው። የሌንጮ ለታ ፖለቲካ እውቀት የሚደነቅ ነው። በፖለቲካ ብስለታቸውና ትንተናቸው ከማደንቃቸው የፖለቲካ ሰዎች አንዱ ናቸው።  ፖለቲካ ማወቅ እና ህዝብን መምራት ግን በጣም የተለያዩ ነገሮች ናቸው። ብዙውን ግዜ የሰዎችን የፖለቲካ ብቃት የምንለካው በንግግር ችሎታው ብቻ ነው። ጥሩ የፖለቲካ መሪ አስተዋይም መሆን አለበት። የመሪ አስተዋይ አለመሆን ደግሞ ችግር የመፍታት ብቃታ ማጣቱን ነው የሚያሳየን። ኦነግ ከ40 አመታት በላይ በትግል ላይ እንደሆነ ይነገረን እንጂ ድርጅቱ ድል አድርጎ አይተን አናውቅም። የሽግግሩን መንግስት ላይም ቢሆን የተገኘው በድል አድራጊነት ሳይሆን ከህወሃት እና ከሻእቢያ ጥሪ ተደርጎለት ነበር።

በአሁኑ የአዲስ አበባ ጉዞ ሌንጮ እንደቀድሞው ልዩ አቀባበል ላይገጥማቸው ይችላል። በእርግጠኝነት ለመናገር ከጉዞው በፊት አንዳች ቅድመ ሁኔታዎች ወይንም ስምምነቶች ይኖራሉ።  ይህ ካልሆነ ግን እኝህን ሰው በቀይ መስመር ላይ ማስቆም ወይንም ደግሞ ማኖ ማስነካቱ አይቀሬ ነው። እሳቸውን ቀይ መስመር ላይ ለማቆስም በጣም ቀላል ነው። የበደኖው፣ የዋተሩና የአርባጉጉ ፋይሎች እየተመዘዙ ማውጣት ብቻ ይበቃል። አልያም ቦሌ ላይ እነ ዋልታ ብቅ ብለው በካሜራ ይቀበሏቸዋል። ልማቱን እንዲያደንቁ ይጠየቃሉ። በእስር ያሉ ወገኖችና “ሽብርተኞች”ን ማውገዛቸውም የግድ ነው። በዚህ መስመር ላይ ከሄዱ  “አባ ጸበል ይርጩን” ብለው እንደገቡት እንደነ ስም አይጠሬ ተዋርደው ይመለሱና የፖለቲካ ሞትን ዳግም ይቀምሷታል።

ለእንደዚህ አይነቱ “ልማታዊ” የተቃውሞ አስተሳሰብ ሳይገዙ ታሪክ መስራት ከተቻለ ግን ተአምር ይሆናል።  ለማንኛውም መልካም ጉዞ…

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Left Column

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am
  • Rusted screws, metal spikes and plastic rubbish: the horrific sexual violence used against Tigray’s women July 4, 2025 01:48 am
  • በሞርሞን ቤ/ክ ዕርዳታ የኪዳነምህረት ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ማምለኪያ ሥፍራ አገኘች July 2, 2025 01:28 pm
  • የበረከት ስምዖን “አየር ላይ ትዕይንት” አየር ላይ ተበተነ July 2, 2025 01:24 am
  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am
  • ከትግራይ ሾልኮ የወጣው ምሥጢራዊው ሰነድ ምንድነው? May 20, 2025 09:18 am
  • በደቡብ ጎንደር በጸዳሉ ደሴ የተመሩት 72 ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ May 19, 2025 02:24 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule