
አንድ የሰዋስው ተማሪ ውሃ ለመቅዳት ወደ ጉድጓድ ሄደ፡፡ ሆኖም በጥንቃቄ ጉድለት የተነሳ ተንሸራተተና ከጉድጓዱ ውስጥ ተደፋ፡፡ እዚያም ሆኖ ዋይታውን ሲለቀው አንድ መንገደኛ ሰማውና ሊረዳው መጣ፡፡
“ምን ሆንክ?”
“እንደምታየው ከዚህ ጉድጓድ ውስጥ ልሰጥም ነው፤ ቶሎ ገመድ አምጥተህ ካላወጣኸኝ መሞቴ ነው”
“እሺ ገመድ ልፈልግና ልምጣ፤ እስከዚያው ግን የጉድጓዱን ዳር ይዘህ ለመንሳፈፍ ብትሞክር ይሻላል” መንገደኛው ይህንን ተናግሮ ሊሄድ ሲል ተማሪው አላስችል አለው፡፡
እናም “አንድ ጊዜ ቆየኝ እስቲ” በማለት መንገደኛውን ከመንገድ ጠራውና እንዲህ አለው፡፡ “ቅድም የተናገርከው ዐረፍተ ነገር የሰዋስው ደንብን የጠበቀ አይደለም፤ ስለዚህ ላስተካክልልህ ብዬ ነው የጠራሁህ”፡፡
መንገደኛው ይህንን ሲሰማ በጣም ተናደደ፡፡ ከጉድጓድ ውስጥ ለሚንቦጫረቀው ተማሪም እንዲህ አለው፡፡ “እንደዚያ ከሆነ ሰዋስው ተምሬ እስክመጣ ድረስ እዚሁ ጉድጓድ ውስጥ ብትቆየኝ ይሻላል”
(Idries Shah, “Tale of the Dervishs”, 1971)
(ምንጭ: Afendi Muteki facebook)
Leave a Reply