• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

የቂሊንጦ ወኅኒ ቤት ቃጠሎ ጉዳይ…

September 4, 2016 01:42 am by Editor Leave a Comment

በምርጫ 1997 ማግስት የአደባባይ አመፆች ተበራክተው ነበር፡፡ በጥቅምት 24፣ 1998 አዲስ አበባ በሕዝባዊ አመፅ ስትናወጥ፣ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት ውስጥም ሊሰጠው ይገባው የነበረውን ያክል ትኩረት ሳያገኝ ያለፈ ትራጄዲ ተከስቶ ነበር፡፡ በወቅቱ እልፍ በኦ.ነ.ግ. ሥም ተወንጅለው የታሰሩ የፖለቲካ እስረኞች የቃሊቲ ግቢ ውስጥ ታጉረው ነበር፡፡ ታዲያ ግቢው ውስጥ በተፈጠረው ግርግር ‹ሊያመልጡ ሞክረዋል› በሚል 163 የሚደርሱ ታራሚዎች በተተኮሰባቸው ጥይት ሕይወታቸውን አጥተው ነበር፤ መንግሥት የሟቾቹ ቁጥር ዐሥር እንኳን እንደሚሞላ አላመነም ነበር፡፡

‹ሻዕቢያ› በቂሊንጦ እና ቃሊቲ ወኅኒ ቤቶች እጅግ ዝነኛ ሥም ነው፡፡ ‹ሻዕቢያ› በሚባል ቅፅል ሥም የሚጠራው የዋርድያዎች ኃላፊ፣ በቂሊንጦ የሚገኙ ተመላላሽ እስረኞች በፍርሐት ይርዱለታል፡፡ ‹ሻዕቢያ› ከ1998ቱ የቃሊቲ እስረኞች እልቂት ጋር ሥሙ በተደጋጋሚ ይነሳል፡፡ በወቅቱ የተነሳውን ግርግር ተከትሎ አግድም በመተኮስ ለብዙ እስረኞች እልቂት ምክንያት የሆነው ይኸው ‹ሻዕቢያ› የተባለ ግለሰብ እንደሆነ ይነገራል፡፡ በወቅቱ ቃሊቲ እስር ላይ የነበሩ ሰዎች እንደሚናገሩት፣ ሊፈቱ ጥቂት ቀናት የቀራቸው ሰዎች ሳይቀሩ ክፍላቸው በተቀመጡበት ለሞት ተዳርገዋል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ አግድም የተተኮሰው ጥይት ክፍላቸው ውስጥ አርፈው የተቀመጡትን እስረኞች የወኅኒውን የቆርቆሮ ግድግዳዎች እየበሳ በተቀመጡበት ጭንቅላታቸውን ስለመታቸው ነው፡፡ (‹ሻዕቢያ› በዚህ ዓመት አጋማሽ በከባድ የውንብድና ወንጀል ተጠርጥሮ ከሥራ ታግዷል)

ይህ በሆነ ማግስት እና በተከታዩ ሳምንት የቤተሰብ መጠየቂያው አጥር የቀብር ቦታ ይመስል እንደነበር በወቅቱ እዚያ የነበሩ ሰዎች ተናግረዋል፡፡ በወቅቱ እስረኛ ቤተሰብ የነበረው ሰው ሁሉ ይመጣና ‹እከሌን አስጠሩልኝ› ሲል የሞት መርዶ ይመለስለት እና ‹ዋይታ› መጠየቂያውን ቦታ ያጥለቀልቀው እንደነበር በሐዘን ያስታውሳሉ፡፡

‹ዋይታ› ራሱን ደገመ!

ዛሬ (ነሐሴ 29፣ 2008) ቂሊንጦ የታሰሩ ወዳጅ ዘመዶቻቸውን ሊጠይቁ የሔዱ ሰዎች እስረኞቹ ሁሉ የሉም የሚል መልስ እየተሰጣቸው በዋይታ እና ለቅሶ እየታጠቡ ግማሾቹ ተስፋ ባለመቁረጥ እዚያው አካባቢ በፖሊስ እየተዋከቡ ሲቆዩ፣ ቀሪዎቹ መሔጃ በማጣት እና በተስፋ መቁረጥ ወደቤታቸው እየተመለሱ ነው፡፡ የዚህ ሁሉ መንስዔ ትላንት በወኅኒው ግቢ የተነሳው ከፍተኛ የእሳት አደጋ ነው፡፡

ቅዳሜ (ነሐሴ 28 ቀን 2008) ጠዋት 2፡30 ጀምሮ እስከ 10፡00 ሰዐት ድረስ ቂሊንጦ የሚገኘው ‹በፌዴራል ማረሚያ ቤቶች የአዲስ አበባ የቀጠሮ እስረኞች ማቆያ› በእሳት ተያይዞ ሲነድ እና ከባድ የተኩስ ድምፅ ሲሰማ ውሏል፡፡ በወቅቱ የተነሱ የምስል ማስረጃዎች እደሚያረጋግጡት እና በወቅቱ በአካባቢው የነበሩ ሰዎች እንዳስረዱት እሳቱ ከፍተኛ በሚባል ደረጃ ሲነድ እና ከውስጥ የፍንዳታ ጩኸትም ይሰማ እንደነበር፣  ጭሱ እስከ 10 ኪሎ ሜትር የሚደርስ ርቀት ላይ ሲታይ እንደነበር ነው፡፡

የአደጋው ሪፖርት

የእሳት አደጋውን የአገር ውስጥ ብዙኃን መገናኛ እየተከታተሉት ሲዘግቡ ውለዋል፡፡ በገዢው ፓርቲ አባላት የሚዘወረው ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት በድረ-ገጹ እንደዘገበው በአደጋው ምክንያት አንድ ሰው እንደሞተ እና እሳቱን በቁጥጥር ሥር ለማዋል በቦታው የተገኙ 3 ‹የአዲስ አበባ ከተማ እሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከል እና መቆጣጠር ባለሥልጣን› ባልደረቦች ቀላል ጉዳት እንደደረሰባቸው፤ የፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬትን ጠቅሶ ዘግቧል (በምሽት የሬድዮ ዘገባው ቀላል ጉዳት የደረሰባቸውን ሰዎች ቁጥር 6 አድርሶታል)፡፡ ሪፖርተር ጋዜጣም በዘገባው እሳቱ እስረኞች ማቆያ ግቢ ውስጥ ከሚገኝ የመመገቢያ ቦታ (ካፌ) እንደተነሳ እና ዞን 3 ደርሶ እንደ ነበር በሥም ያልጠቀሳቸውን ምንጮች ጠቅሶ ዜና የሠራ ሲሆን እስረኞች ለማምለጥ ሙከራ ከማድረግ እንዲቆጠቡ የማረሚያ ቤት ፖሊሶች ለማስፈራራት ወደ ሰማይ ሲተኩሱ ነበር ብሏል፡፡ ገዥውን ፓርቲ የተመለከተ ካልሆነ የፖለቲካ ዘገባ ሲሠራ የማይታወቀው እና በእግሊዘኛ ቋንቋ የሚታተመው ሳምንታዊው ፎርቹን ጋዜጣም አደጋውን በመከታተል ሲዘግብ እሳቱ ሆን ተብሎ በታራሚዎች የማምለጥ ሙከራ የተቀሰቀሰ እንደሆነ በድረ-ገጹ አስነብቧል፡፡ ፎርቹን ማምሻውን የድረ-ገጹ ዘገባ ላይ አዲስ መረጃ ሲያክል ‹20 የሚደርሱ ታሳሪዎች ተተኩሶባቸው እንደሞቱ› ዘግቧል፡፡ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ቴሌቭዥን አደጋውን እስረኞች ያስነሱት አድርጎ ዘግቧል፡፡

የእሳት አደጋው ሲደርስ በእስረኞች ማቆያ አካባቢው የነበሩ የእስረኛ ቤተሰቦች እና ታዛቢዎች እሳቱ የተነሳው የቤተሰብ መጠየቂያ ሰዐት ከመድረሱ በፊት እንደነበር እና ጭሱ ጎልቶ መታየት ከመጀመሩ በፊት የማረሚያ ፖሊሶች ከቦታው እንዳስለቀቋቸው ይናገራሉ፡፡ ማምሻውን የኦሮሞ መብት ተከራካሪው ጃዋር መሐመድ የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ‹22 የታሸጉ አስከሬኖችን ከቂሊንጦ ወኅኒ እንደተረከበ እና አስከሬኖቹ በወታደር እየተጠበቁ እንደሆነ› መረጃ እንደደረሰው ዘግቧል፡፡ ለአደጋው ሽፋን የሰጠው የበይነ-መረቡ ሬድዮ ዋዜማ በበኩሉ አካባቢው ላይ ከነበሩ የዓይን እማኞች አገኘሁ ያለውን መረጃ ጠቅሶ የማረሚያ ፖሊሶች ከመጠበቂያ ማማ ላይ ሆነው ወደ እስረኞች ሲተኩሱ እንደነበር ዘግቧል፡፡

የቂሊንጦ ወኅኒ ቤት ገጽታ

ቂሊንጦ የሚገኘው የአዲስ አበባ የቀጠሮ እስረኞች ማቆያ የፍርድ ቤት ጉዳያቸውን በእስር ላይ ሆነው የሚከታተሉ 3,100 በላይ የሚሆኑ ወንድ እስረኞች የሚገኙበት ሲሆን፣ በአራት ዞኖች የተከፋፈለ ነው፡፡ ከአራቱ ዞኖች መካከል ሦስቱ እያንዳንዳቸው ለእስረኞች የትኩስ መጠጥ አገልግሎት የሚሰጡበት አነስተኛ ካፌ ያላቸው ሲሆን፣ እነዚህ ካፌዎች ለማብሰል (ለማፍላት) የሚጠቀሙት የኤሌክትሪክ ኃይል ነው፡፡ በቅርቡ አገልግሎት መስጠት የጀመረው ዞን 4 በቅጣት ምክንያት ከሌሎች እስረኞች እዲገለሉ የተወሰነባቸው እስረኞችን ማቆያ ነው፡፡ በዚህ ዞን ውስጥ ካፌ የለም፡፡ ዞን 1፣ 2 እና 3 እያንዳንዳቸው 130 የሚጠጉ እስረኞችን የሚያሳድሩ ስምንት-ስምንት ክፍሎች ሲኖሯቸው፣ ዞን 4 ውስጥ ሁለት የእስረኛ ማቆያ ቤቶች ይገኛሉ፡፡

እስር ቤቱ በቀን ሦስት ግዜ ለእስረኞች ምግብ ያቀርባል፡፡ ይህ ምግብ የሚበስለው በተለምዶ እስረኞች ሜንሲ ቤት ብለው የሚጠሩት ከዞኖቹ ተገልሎ ካለ ቦታ ሲሆን ምግብ የሚታደልበት ሰዓት ሲደርስ ከየቤቶቹ ውስጥ በወር አነስተኛ ክፍያ የሚከፈላቸው በተለምዶ ሰፌድ እና ጎላ ሠራተኞች ተብለው የሚጠሩ እስረኞች ሜንሲ ቤት ድረስ በመሔድ ምግቡን እስረኞች ክፍል ድረስ ተሸክመው ያመጣሉ፡፡

እስር ቤቱ ውስጥ ሲጋራን ጨምሮ ማንኛውንም ዓይነት አደንዛዥ ዕፅ መጠቀም የተከለከለ ነው፡፡ ሆኖም ሱስ ያለባቸው እስረኞች በዋነኝነት ከማረሚያ ፖሊሶች ጋር በመመሳጠር ሲጋራና አጤፋሪስን የመሳሰሉ አደንዛዥ ዕፆች አስገብተው ይጠቀማሉ፡፡ እነዚህን ዕፆችን በእስር ቤቱ ውስጥ ለማስገባት እና ለማከፋፈል በአንዳንድ እስረኞች መካከል ከፍተኛ የሆነ የቡድን ፀብ የሚያስነሳ ፉክክር የሚካሔድ ሲሆን ከኮንትሮባንድ ንግዱም የሚገኘው ገቢ እጅግ ከፍተኛ ነው (የአንድ ኒያላ ሲጋራ ዋጋ ቢያንስ 20 ብር ነው)፡፡

ዕፅ ለማጨስ መለኮሻ የሚሆን እሳት ለማግኘት ከፍተኛ ችግር ስላለ፣ የተለያዩ አልባሳትን ቀዶ በመግመድ ወይንም ለመተኛ ከሚገለገሉበት ፍራሽ ስፖንጅ በመቅደድ እና በማያያዝ አንዴ የተገኘውን እሳት ለቀናት ሳይጠፋ ያቆዩታል፡፡

በአሁኑ ወቅት እስር ቤቱ ውስጥ በመላው ኦሮሚያ እየተካሔደ ካለው የፀረ-አምባገነን ተቃውሞ ጋር በተያያዘ ታስረው የሽብር ክስ የተመሠረተባቸው የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት አቶ በቀለ ገርባ እና የመብት ተሟጋቹ ዮናታን ተስፋዬ፣ የነገረ ኢትዮጵያ ዋና አዘጋጅ ጌታቸው ሽፈራው እና የሰማያዊ ፓርቲ አባላት የነበሩ ሌሎች ወጣቶች፣ በሚያዝያ 2006 የታሰሩት ኦሮሞ ተማሪዎች እና ወደኤርትራ ሊኮበልሉ ሲሉ ተያዙ የተባሉት የአየር ኃይል ጓዶች (በእነመቶ አለቃ ማስረሻ መዝገብ) እንዲሁም ሌሎች በመቶዎች የሚቆጠሩ የፖለቲካ እስረኞች ይገኛሉ፡፡

በቃጠሎውና በተኩሱ ምክንያት የተጎዱ እስረኞች ቁጥር ስንት እንደሆነና ጉዳት የደረሰባቸው እስረኞች ማንነት ባለመገለጹ ምክንያት፣ እንዲሁም እስረኞቹ ወደሌላ ወኅኒ ቤት ተዛውረዋል በሚል ቤተሰቦች የዘመዶቻቸውን ደኅንነት ባለማረጋገጣቸው በእስር ቤቱ ውስጥ ወዳጅ ዘመድ ያላቸው ሰዎች ከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ ገብተዋል፡፡ በፖለቲካ እስረኞች ላይ የደረሰ ጉዳት ካለ ወይንም ስለ ደኅንነታቸው ማረጋገጫ መንግሥት የማይሰጥ ከሆነ ከፍተኛ አፀፋዊ የሕዝባዊ የአመፅ እርምጃ እንደሚወስዱ የኦሮሞ መብት አራማጆች ትላንት ማምሻውን ማስጠንቀቂያ ሰጥተዋል፡፡

እያገባደድን ባለው ዓመት ሕዳር 21 ቀን በጎንደር በሚገኝ እስር ቤት ውስጥ በተነሳ እሳት17 ሰዎች መሞታቸው ይታወሳል፡፡

በናትናኤል ፈለቀ
(አርታኢ፤ በፍቃዱ ኃይሉ)
(ምንጭ: ዞን 9)
Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am
  • Rusted screws, metal spikes and plastic rubbish: the horrific sexual violence used against Tigray’s women July 4, 2025 01:48 am
  • በሞርሞን ቤ/ክ ዕርዳታ የኪዳነምህረት ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ማምለኪያ ሥፍራ አገኘች July 2, 2025 01:28 pm
  • የበረከት ስምዖን “አየር ላይ ትዕይንት” አየር ላይ ተበተነ July 2, 2025 01:24 am
  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am
  • ከትግራይ ሾልኮ የወጣው ምሥጢራዊው ሰነድ ምንድነው? May 20, 2025 09:18 am
  • በደቡብ ጎንደር በጸዳሉ ደሴ የተመሩት 72 ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ May 19, 2025 02:24 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule