• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

አማራነቴስ እሺ፤ ጨዋነቴስ?

February 13, 2017 03:53 am by Editor 3 Comments

ከተወለድኩበት እለት ጀምሮ በቅጡ የማውቀው ጎጃሜነቴን ነበር። ከዚያ ልዩ የምጠራበት ስም እንዳለኝ የሰማሁት እያደር ነው። ሌላው ቀርቶ ኢትዮጵያዊ እንደምባል እንኳን የገባኝ ትምህርትቤት ገብቼ ሶስተኛ ወይም አራተኛ ክፍል ግድም ስደርስ ሳይሆን አይቀርም።

ከዚያም ሙት ወቃሽ እንዳልሆን ስማቸውን የማላነሳው ግን እጅግ የምወዳቸው ዖሮሞው የህብረት አስተማሪዬ የዛሬን አያድርገውና ኢትዮጵያ 14 ክፍለሀገሮች እንዳሏት ሲነግሩኝ ለካ ከጎጃም ሌላ ሀገር አለ ብዬ ደነቀኝ።

በኋላማ አማርኛ የማይናገር ወገን እንዳለኝ ሳስተውል ሆጃሜ ብቻ እንዳልሆንኩ በሚገባ መገንዘብ ጀመርኩ። ልባድርጉልኝ፣ እስካሁን ድረስ (አረ ምን እስከዛ ድረስ ብቻ እስከኋለኛው የስርአት ለውጥ ድረስ) አማራ ነህ ያለኝም፣ እኔም አማራ ነኝ ያልኩበት ጊዜ ትዝ አይለኝም። ብቻ በልጅነቴ አዋቂዎች ሲያወሩ (ያን ጊዜ ከአዋቂ ጋር እኩል ማውራት እንጂ አዋቂ ሲያወራ ማዳመጥ ይፈቀድ ነበርና) ከመካከላቸው አገር አውርቶ ለጨረሰው አንድ ጉዳይ እንግዳ የሆነ ሰው ሲያጋጥማቸው፥ ይህማ እስላም አማራው አውርቶ የጨረሰው ጉዳይ እኮ ነው፥ ሲሉ ትዝ ይለኛል። ከዛም አማራ ማለት ክርስቲያን ማለት እንጂ አማርኛ ተናጋሪ ማለት እንዳልሆነ ገብቶኝ አደግሁ። እዚህ ላይ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያምን ያስታውሷል። ፕሮፌሰሩ ከአቶ መለስ ዜናዊ ጋር መከራከር ይቻል በነበረበት ጊዜ አማራ የሚባል ማንነት የለም ብለው መከራከራቸውን አስታውሳለሁ። እውነቱን ለመናገር እኔም ብሆን ዛሬም ስሜ የሚመስለኝ ሆጃሜነት እንጂ አማራነት አይደለም።

ዛሬ ግን ጨዋታው ተቀይሯል። እኔም ብሆን የኋላ ኋላ በህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ የበረሃ የፖለቲካ መርሃግብር ላይ አማራ ስለሚባል ህዝብ በተለይ መስፈሩን፣ በደርግ  ውድቀት ማግስት በየክልሉ አማራ የሚባል ህዝብ እየተለየ በጭካኔ መጨፍጨፉን፣ ከዚያም በኋላ በየጊዜው ይሄው ህዝብ ተለይቶ አንጡራ ሀብቱን በጉልበት እየተቀማ ከየክልሉ መባረሩን ስሰማ አማራ ሃይማኖት ሳይሆን ብሄር መሆኑ ገባኝ። ከዛም ሆጃሜነት መገኛዬ፣ አማራነት መጠሪያዬና ኢትዮጵያዊነት ጥላዬ መሆኑን አመንኩ።

የዛሬ መነሻዬ የብሄር ትንተና አይደለም። ስለሰሞነኛው ያማራ አርበኝነትና የብሄር አብዮተኝነትም ቢሆን ለጊዜው የምለው የለኝም። አማራ መደራጀት አለበት ወይስ የለበትም? በጎንደር በኩል ከመንግስት ጋር የሚዋጋው አማራ ነው ወይስ ግንቦት 7? በሚሉ የጅል ጥያቄዎችም ላይ ቢሆን የማጠፋው ጊዜ የለኝም። እነዚህ ጥያቄዎች ያላዋቂ ወይም የጅል ጥያቄዎች ናቸው የምልበትን ምክንያት ግን መጠቆም ሳይኖርብኝ አይቀርም። ምክንያቴን እነሆ።

ግቡ ህገወጥ እስካልሆነ ድረስ ወይም ለጥፋት አላማ እስካልታቀደ ድረስ ማንም ሰው ላመነበት አላማ መደራጀት መብት መሆኑ እየታወቀ አማራ ባማራነቱ ሊደራጅ አይገባም በሚል ዘራፍ ማለት በተለይ ስለሰባዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች የሚያውቅ ሰው ተቃውሞውን ያላዋቂ ሊለው መብት ያለው ይመስለኛል። ይህም ብቻ አይደለም፤ አገር ምድሩ በየዘውጉ ተሸንሽኖ እኔ እኮ እገሌ እባላለሁ፣ እንቁልጭጫችሁ እያለ ባማራው ላይ ሲቀልድና አልፎም ሀገር እንደሌለው ካገር ውጣ ሲባል ለመሆኑ እኔ ማነኝ? ሀገሬስ የት ነው ብሎ መጠየቅ ነውር ነው ሲባል ያናድዳል። በሌላ በኩል ደግሞ መንግስትን የሚወጋው አማራ ነው ወይስ ግንቦት ሰባት የሚለውም ቢሆን ነጥብ ለማስቆጠር የሚደረግ ገና ያልተሰራ ታሪክ ለመሻማት የሚደረግ ልላኛው መንትያ የጅልና የስግብግቦች ጥያቄ ነው። አሁን ይህን ጉዳይ በቀጠሮ ትቼ የተነሳሁበትን ጉዳይ ልናገር።

እኔን ያሳሰበኝ አዲስ ያማራ መብት ተሟጋቾች ወይም አርበኞች መነሳት ጉዳይ አይደለም። ከንቅናቄው መጀመር በላይ እጅግ አሳሳቢው ጉዳይ የንቅናቄው መሪዎች ዲሲፕሊን ባማራው ህዝብ ጨዋነት፣ ሆደሰፊነትና ኩሩነት የደቀነው ግልፅ አደጋ ነው። ስጋቴን በሁለት ምሳሌዎች ላስረዳ፤ አንድ የእንቅስቃሴው መሪ የሰጡት ቃለመጠይቅና የቡድኖቹ እንደአሸን መፍላት።

ሰውየውን (ወጣቱን ልበል መሰለኝ) በስም ካልሆነ በአካል አግኝቸውም ሆነ በድምፅ ሰምቼው አላውቅም ነበር። ደራሲ፣ ያማራው ጠበቃ፣ አርበኛም ሲባል እሰማለሁ። ለነገሩ ከመሪነቱ ፅነፅሁፉ ያምርበት ነበር ያሉኝም ነበሩ። ብቻ መቼም ያላንድ ነገር ይህ ሁሉ መወድስ አይወርድለትም ብዬ እኔም አድንቄው ነበር።

በቅርቡ ለአንድ የሬዲዮ ጣቢያ ቃለመጠይቅ ሲሰጥ በሰማሁት ጊዜ ግን የፍቅር እስከመቃብሩ በዛብህ ቦጋለ ትዝ አለኝ። በዛብህ ከደብረወርቅ ከተማ ተነስቶ ወደዲማ ሲጓዝ ስመገናናው የዲማ ጊወርጊስ ደብር አነስተኛ መንደር ሆኖ ባገኘው ጊዜ፥ አይ ዲማ፣ ባላይህ ኖሮ እድሜዬን ሁሉ ሳከብርህ እኖር ነበር፥ እንዳለው ሁሉ እኔም ይህንኑ ወጣት ቃለመጠይቁን ሳልሰማ በተከታዮቹ ውዳሴ ሳከብረው ብኖር ይሻለኝ ነበር ማለቴ አልቀረም። ወጣቱ የሚናገረው በደም ፍላት ነው። የሚጠቀምባቸው ቃላት ያድማጭን ደም ያስቆጣሉ። አንዳንዶቹም ይዘገንናሉ። ከዚህ ሁሉ በላይ ግን የወጣቱ ንግግር ባደኩበት ያማራ ባህል የማውቀው ጨዋነት የለውም። ባደኩበት ያማራ ባህል የ60ና የ70አመት አረጋውያን በመጀመሪያ ስማቸው ብቻ አይጠሩም። አንተ ወይም አንቺም አይባሉም። ተናጋሪው እነአቶ ሌንጮ ለታን፣ እነ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋንና ሌሎችንም የእድሜ ባለፀጎች ያለማንጠልጠያ ሲዘረጥጣቸው መስማት እጅግ ይዘገንን ነበር።

ያማራ ህዝብ ታላላቆቹን ቀርቶ ታናናሾቹን እንኳ አንቱ የሚልበት ጊዜ አለ። ያማራ ህዝብ አንደበቱ የተገራና ትህትና ያለው ነው። ጠላቱን እንኳን የሚያናግረው በጨዋ ቋንቋ ነው። አይባልግም።

ይህን ጨዋ ህዝብ ባደባባይ ወክሎ ለመናገር ጨዋነቱን መላበስ ያስፈልጋል። አማራን መወከል ከነክብሩ ነው። አማራ ሲሟገት እንኳን በጨዋነት ነው። በጨዋነቱም ይረታል። ለዚህም ነው ካነጋገር ይፈረዳል ካያያዝ ይቀደዳል ሲል ያንደበት ልእልናን የሚነግረን። ከዚህ አንፃር ከአዲሶቹ የአማራ ብሄርተኝነት መሪዎች መካከል አንዱ የሆነው የዚህ ወጣት ንግግር ግን ያማራ ጨዋነት፣ ሰው አክባሪነትና ትህትና አልነበረውም። በዚህም ምክንያት ባቀራረቡ የሚወክለውን ኩሩ ያማራ ህዝብ እውቅ እሴቶችን የወረሰ መሪ ሳይሆን በውዳሴ ከንቱ የነገሰ የእብሪትና ትእቢት ተናጋሪ አስመስሎታል። በዚህም ደንግጫለሁ።

በኢትዮጵያ የፖለቲካ ታሪክ በየጊዜው የሚነሱ የእውቀት ሳይሆን የስሜትና የጉልበት መሪዎች ብዙ መከራ አድርሰውብናል። ዛሬም መዘዙ አለቀቀንም። እናም እኒህ አዲስ ያማራ ንቅናቄ መሪዎች በዚህ አያያዛቸው ባማራው ህዝብ ታሪክ፣ ባህልና ክብር ላይ የማይመለስ ጉዳት እንዳያደርሱ ስጋት አለኝ። ከጀግንነትና የማይናወጥ ሀገራዊ ፍቅር በቀር ሌላ አበሳ ለሌለበት መከረኛ ህዝብ መብትና ክብር መቆማቸው ሲያስመሰግናቸው አያያዛቸው ጠበኝነት፣ እብሪትና ግንፍልተኝነት ያየለበት ስለሚመስል አሳሳቢ ነው። የሚወክለን ካለ ስማችንን ብቻ ሳይሆን ጨዋነታችንን  ጭምር መውረስ አለበት። በዚህ ላይ አጀንዳው በተነሳ ማግስት ትግሉ አንዲት ጋት እንኳን ሳይራመድና ስራው እፍኝ ሳይሞላ ድርጅቶቹ ደረብ አኻዝ ሊሞሉ መቃረባቸው ሲታከልበት አደጋውን የበለጠ ያገዝፈዋል። ጎበዝ መፋቀር ቢያቅተን እንዴት በስነስርአት መጣላት እንኳን ያቅተናል?!

ህሩይ ደምሴ (zobar2006@gmail.com)


“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Comments

  1. አለም says

    February 14, 2017 06:34 pm at 6:34 pm

    ውድ ህሩይ፣
    የሚገርመው ይህ ያንተ የሕይወት ልምድ የአብዛኛው ወጣት ልምድ መሆኑ ነው። ከአዲስ አበባ ወጣ ብሎ ደብረ ብርሃን ወይም ጊንጪ ያለ የሚያስበው መንደርተኛነትን እንጂ ብሔረተኛነትን አይደለም። የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሲገባ፣ በዘመቻና በሥራ ሲመደብ ያኔ ከየክፍለ ሃገሩ የመጣውን በማየት ከአገራችን ወርድና ስፋት ጋር ይተዋወቃል። ይህ እድል ያጋጠመው ጥቂቱን ክፍል ብቻ ነው። አብዛኛው አንተ በገለጽከው ሁኔታ የሚገኝ በመሆኑ ዛሬ ለሚያወናብዱ ሰለባ ሆኗል። መፍትሔው እንደ ጀመርከው መጻፍና መናገር ነው። በመነጋገር ውስጥ ዋሾው ይገለጣል። መንግሥት የመገናኛ መስመሮችን አጥብቆ የተቆጣጠረው ለዚሁ ነው። ራሱ መርጦ በፈጠረው እውነት ትውልዱን እያደነቆረ ይገኛል። ቁምነገሩ እውነቱን መግለጥ ላይ ነው እንጂ መንግሥትና ተቃዋሚዎቹ እንደሚያደርጉት ውሸት መዝራት ከሆነ ምን ፋይዳ ይኖረዋል? በርታበት።

    Reply
  2. Tadesse says

    February 14, 2017 07:30 pm at 7:30 pm

    wed wndme,and Eritrawi yetsafew lechmer,le mefaker emanchel kehone,tekebabren menor endet yaktenal.

    Reply
  3. Tadesse says

    February 14, 2017 07:32 pm at 7:32 pm

    wede amarigna tergume new yetsafkut.

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • “ዛሬ ‘ኃያል ነን’ የሚሉ ሀገራት ኢትዮጵያ ላይ በሚዲያ /በመረጃ/፣ በዲፕሎማሲ፣ በሳይበር እና በተልእኮ የተቀነባበረ ‘ግራጫ ጦርነት’ እያካሄዱባት ነው” ጠ/ሚ ዐቢይ July 7, 2022 10:03 am
  • የኦሮሞ ልሂቃንና ፖለቲከኞች በአማራ ተወላጆች ላይ እየደረሰ ያለውን “የዘር ማጥፋት” ወንጀል እንዲያወግዙት አብን ጠየቀ July 6, 2022 01:38 pm
  • “አማራን ኦሮሚያ ውስጥ የመግደል እና የመጨፍጨፍ እቅድ የኦነግ ሳይሆን የኦሮሚያ ብልጽግና ነው” አቶ ሃንጋሳ July 6, 2022 01:53 am
  • “በኢትዮጵያዊያን የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ በመግባት ሀገሪቱን ማተራመስ አለብን” አይማን አብድልአዚዝ ግብጻዊው ፖለቲከኛ July 5, 2022 12:57 pm
  • ባልደራስ የአገርን ደኅንነት አደጋ ላይ በመጣል ሊጠየቅ ይገባዋል ተባለ July 1, 2022 09:23 am
  • “ሚካኤል ችግኝ ነው። … ችግኝ ይተክላል” ቴዲ አፍሮ June 29, 2022 03:30 am
  • “የእኔን ልጆችና የልጅ ልጆች (22ቱንም) የቀበርኩት እኔ ነኝ” አቶ መሀመድ የሱፍ ከምዕራብ ወለጋ June 28, 2022 01:07 pm
  • የገዳ ሥርዓት እና የኦሮሞ ገዢ መደብ June 20, 2022 11:34 pm
  • “የወልቃይትን ጉዳይ ለድርድር የማናቀርበው ቀይ መስመራችን ነው” ርዕሰ መስተዳድር ይልቃል June 12, 2022 07:09 pm
  • የሰሜን ምዕራብ ዕዝና የአማራ ልዩ ኃይል ተከዜ ክፍለ ጦር ዕውቅናና ሽልማት ተሰጣቸው June 12, 2022 06:21 pm
  • ሀገር በቀል ባህላዊ የግጭት አፈታቶችን በተገቢው በመጠቀም ዘላቂ እርቅና ሰላምን ማምጣት ይቻላል June 12, 2022 05:40 pm
  • የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በገረጂና በቀበና ያስገነባቸውን የመኖሪያ አፓርትመንቶች አስመረቀ June 12, 2022 05:35 pm
  • በኦነግ ሸኔ ፈርሶ የነበረውና ወታደራዊ ጠቀሜታ ያለው ድልድይ ተጠግኖ አገልግሎት መስጠት ጀመረ June 10, 2022 09:13 am
  • ጃዋር በዳውድ ኢብሣ ቀይ መስመር ተሰመረለት June 8, 2022 12:59 pm
  • ወልቃይት: ቢመረንም ለመዋጥና ራሳችንን ለመመልከት እንሞክር June 8, 2022 11:53 am
  • እብድ ይሻለዋል እንጂ አይድንም፤ ሐጂ ጃዋር አሁን ለምን ብቅ አለ? June 8, 2022 05:59 am
  • ሕዝብ ድምፅ የነፈጋቸው “ፓርቲዎች” የሽግግር መንግሥት ይቋቋም አሉ June 7, 2022 01:11 am
  • “አድጌ እንደናንተ መሆን እፈልጋለሁ” June 5, 2022 06:58 pm
  • በሳምንት ለ100 ያህል ሕሙማን አገልግሎት የሚሰጥ የኩላሊት ዕጥበት ማዕከል ሥራ ጀመረ May 30, 2022 02:20 am
  • የጥቁር አንበሳ ዕጩ መኮንኖች (ካዴቶች) ተመረቁ May 29, 2022 04:01 pm
  • “ኢትዮጵያን መንካት አይቻልም!!” በሚል ቁጭት ነው እየሠራን ያለነው May 29, 2022 01:04 pm
  • “ከሞፈርና ቀንበር ወደ ትራክተር” በሚል መርህ ለአማራ ገበሬዎች የግብርና ሜካናይዜሽን ተሰጠ May 29, 2022 02:02 am
  • ኢትዮ 360 “የወያኔ፣ የጁንታ ሚዲያ ነው” – ባለከዘራው ጄኔራል May 27, 2022 02:51 am
  • “እኛ የምናውቀው ነገር የለም፤ የሚያጣሉን ፖለቲከኞች ናቸው” የአማራ ወዳጃቸውን አደራ ቤት የመለሱ የቅማንት ተወላጅ May 27, 2022 01:40 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2022 · Goolgule