• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ከቆሻሻ ኑሮና ሞት ለመላቀቅ ቆሻሻውን ስርዐት ማስወገድ

April 2, 2017 06:58 am by Editor Leave a Comment

ነገሩ ሁሉ ከድጡ ወደማጡ በሆነባት ሀገራችን በየጊዜው የሚፈራረቁት ሰቆቃዎች ልብን በሀዘን ካራ ማድማታቸውን እንደቀጠሉ ነው። ባለፈው አንድ ዓመት ብቻ ከደረሱብን መዓቶች ጥቂቱን ብናነሳ፤ በረኃብ አለንጋ እየተገረፉ ደጃፋቸው ላይ ድፍት ብለው የቀሩትን፣ መብታቸውን ለመጠየቅ ሲጮሁ የጥይት ራት የሆኑትን፣ የኢሬቻን በዓል ለማክበር አምረው ደምቀው እንደወጡ ገደል ሰብስቦ ያስቀራቸውን፣ እንዲሁም በቅርቡ በቆሻሻ ናዳ ታፍነው እስከወዲያኛው ያንቀላፉትን ወገኖቻችንን በቁጭትና በመሪር ሀዘን እናስባለን።

እነዚህን አደጋዎች ይበልጥ አሳዛኝና አስከፊ የሚያደርጋቸው ደግሞ በሀገሪቱ የተንሰራፉት አምባገነንነት፣ ዘረኝነት፣ ምዝበራ፣ ራስወዳድነትና ግድየለሽነት ውጤት መሆናቸው ነው። በአስራዎች በመቶ እድገት ሽምጥ ስለሚጋልበው ኢኮኖሚዋ ነጋ ጠባ የሚዘመርላት የወያኔዋ ኢትዮጵያ ዘራፊዎቿ ከቪላ ቪላ እያማረጡ ሲኖሩና ቤተሰቦቻቸውን ለትምህርት፣ ለወሊድና ለህክምና ወደ ውጭ ሲልኩ፤ ደሀው በጥይት የሚቆላባትና የሚበላው አጥቶ ቆሻሻ ላይ የሚወድቅባት ሀገር ሆናለች። ብሄራዊ ውርደታችንም አሰቃቂ ደረጃ ላይ የደረሰባት ሀገር።

በቅርቡ የደረሰውና ከ115 ሰዎች በላይ በአሰቃቂ ሁኔታ ያለቁበት የቆሻሻ ናዳ አደጋም የዚሁ ሀቅ ምስክር ነው። በዚህ አደጋ ያለቁት ሰዎች በስርዐቱ ስግብግብነትና ደንታ ቢስነት ተገፍተው የተጣሉ ምስኪንና ረዳትአልባዎች ናቸው። መሬት እየዘረፈና ኮንዶሚኒየም እየገነባ ከመቸብቸብና በስጋና በሌብነት ለሚቀርቡት ወዳጆቹ ከማደል ውጭ ስራ የሌለው ይህ ስርዐት የህዝቡን መከራ ዞር ብሎ ባለማየቱ የምስኪኑ ደሀ መኖሪያ የቆሻሻ ክምር ላይ ሆነ። የት ወደቅህ ባይ የሌለው ምስኪን ሃብታም አላምጦ የጣለውን ሊለቅም ቆሻሻ ሲጭር እዚያው ተቀብሮ ህይወቱን አጣ – ድሮም ቆሻሻ ላይ ህይወት ያለ ይመስል። እናት ክንዷ ላይ ያቀፈቻቸውን ልጆቿን ይዛ አሸለበች። ከአንድ ቤተሰብ አምስትና ስድስት እየሆኑ ተያይዘው ሄዱ። በዚህ ዓይነት አሰቃቂ ሁኔታ ልጆቿን ያጣችው አዲስ አበባም መቀነቷን አስራ አስከሬን ስትለቅም ከረመች።

ይህ አሳዛኝ እልቂት የተከሰተበት ስፍራ ከ50 ዓመት በፊት ለቆሻሻ መቅበሪያነት (landfill) ሲመረጥ ከከተማው ያለው ርቀት በተገቢ ሁኔታ ታሳቢ ተደርጎ ነው። ይህን ለመገንዘብ ደግሞ በወቅቱ የአዲስ አበባ ከተማ የነበራትን የህዝብ ብዛትና ስፋቷን ከግምት ማስገባት ነው። ከግማሽ ምዕተ ዓመት አገልግሎት በኋላ በስፍራው የተከማቸው ቆሻሻ 36 ሄክታር ስፋት ያለው ቦታ ሸፍኖ 13 ሜትር ያህል ተቆልሏል (ይህ እንግዲህ ከክምሩ ስር 40 ሜትር ጥልቀት ያለው ጉድጓድ ውስጥ ተቀብሮ ያለውን ቆሻሻ ሳይጨምር ነው)።

ይህ ሁሉ ሲሆን በዓመት 300 ሺህ ቶን የሚጠጋ ቆሻሻ እየተደፋበት የተገነባው ይህ ተራራ በህዝብም ሆነ በአካባቢው ላይ አደጋ እንዳያደርስ የተወሰደ አንድም እርምጃ የለም። ይልቁንም የትም የተጣሉ ድሆች ክምሩ ላይ ጎጇቸውን በላስቲክ ቀልሰው ሞት አይሉት ኑሮ ሲገፉበት ቆዩ። በዚህ ሳያበቃ፤ ሌሎች ምስኪኖችም አልጠግብ ባዮቹ ዘራፊዎች በቆሻሻው ዙሪያ ካለው መሬት ሸንሽነው በሸጡላቸው ቦታ ላይ እንደአቅማቸው ቤት ሰርተው መኖር ጀመሩ። እንደዚህ ያለውን ሀላፊነት የጎደለው ተግባር ወያኔ ከሚመራው በደናቁርት የታጨቀ ስርዓት ውጪ ማን ሊፈፅመው ይታሰበዋል።

የቆሻሻ ማጠራቀሚያ ስፍራ ከጥይት መጋዘን ባልተናነሰ ከፍተኛ ጥንቃቄና ክትትልን የሚፈልግ አደገኛ ቦታ ነው። ጥንቃቄ የጎደለው የቆሻሻ አወጋገድ በቀጥታ ከምናያቸው አደጋዎች ባሻገር የማናስተውላቸውና በቀላሉ የማንረዳቸው እጅግ ከባድ ችግሮች በህብረተሰብና በአካባቢ ላይ ያስከትላሉ። በተከማቸ ቆሻሻ ውስጥ የሚፈጠሩ መርዛማ ንጥረ ነገሮች የአካባቢ አየርን ውሀንና አፈርን ይበክላሉ። በዚህም ሳቢያ በአቅራቢያው የሚኖሩ ሰዎች ለካንሰር፣ ለአስምና ሌሎች ከባድ በሽታዎች በቀላሉ ይጋለጣሉ። በእርጉዞች ላይ የመውለድ እክል ሲከሰት ህጻናትም የማደግ ችግርና ሌሎች የጤና መታወኮች ይደርስባቸዋል። ከቆሻሻው ክምር መንጭቶ ወደ መሬት የሚገባው ፈሳሽ (leachate) እጅግ መርዛማ በመሆኑ አፈርን፣ የከርሰ ምድር ውሀንና ሌሎች የውሀ አካላትን ይበክላል። የአፈሩ ምርታማነት ስለሚቀንስ ድርቅና ረሀብ ይከተላል። የተመረዘውን ውሀ የሚጠቀሙ ሰዎችና እንስሳትም በሽታ ላይ ይወድቃሉ። እነዚህን ችግሮች ለመከላከል ሊወሰዱ ከሚችሉ እርምጃዎች መካከል የቆሻሻን መጠን መቀነስ (waste reduction) እንዲሁም ቆሻሻን መልሶ መጠቀም (recycling)፣ በአግባቡ ማቃጠል (incineration) እና ለማዳበሪያንት ማዋል (composting) ይጠቀሳሉ። ሀገራችን ካላት የአቅምና የተማረ የሰው ሀይል ማነስ ምክንያት እነዚህን እርምጃዎች ተግባራዊ ማድረግ አስቸጋሪ ቢሆን እንኳን፤ ዋነኛውና እጅግ ቀላሉ መወሰድ የነበረበት እርምጃ ሰዎችና እንስሳት በአካባቢው እንዳይኖሩም ሆነ እንዳይደርሱ ማድረግ ነው።

እንደወያኔ ያለ ደንታ ቢስ በሚፈነጭበት ሀገር ግን ይህ አይታሰብም። በሀገሪቱ በሰፈነው ራስ ወዳድነትና ውንብድና ሳቢያ ስንቱ የበሽታ ሰለባ ሆኖ አልጋ ላይ እንደቀረ ብሎም ለሞት እንደበቃ ቤቱ ይቁጠረው። ሌላው አሳዛኝ ጉዳይ ጭካኔው ዘርፈ ብዙ የሆነው ይህ ስርዐት አደጋው ከተከሰተ በኋላ ያሳየው ቸልተኝነት የተሞላበት ምላሽ ነው። እንደተለመደው ወያኔ ችግሩ አደጋው ሳይሆን የሟቾቹ ቁጥር እንደሆነ ራሱ የሚያውጃቸው ዜናዎች አሳብቀውበታል። ዘወር ብሎ ያላያቸውን ምስኪኖች መውቀስና በቸልተኝነት የታጀበ “ብሄራዊ ሀዘን” ማወጅ ማላገጥ ካልሆነ ምን ይባል ይሆን? በአንፃሩ ህዝቡ በራሱ ተነሳሽነት ያሳየው ፈጣን ምላሽና ለወገን ደራሽነት እጅግ የሚደነቅና የሚያኮራ ከመሆኑም በላይ ይህ ድንቅ ህዝብ ምን ያህል የማይመጥነው ስርዓት ላይ እንደወደቀ ተጨማሪ ማረጋገጫ ሆኗል። ምንም እንኳን ወያኔን መምከር የገደል ላይ ጩኸት ቢሆንም እመራዋለሁ ከሚለው ህዝብ አቅሙ የሚፈቅድለትን ያህል ለመማር ቢሞክር ምንኛ መልካም ነበር።

ፅሁፌን ከማጠቃለሌ በፊት አንድ ወዳጄ ያካፈለኝንና እኔም ሙሉ በሙሉ የምስማማበትን ሀሳብ ልጥቀስ። ወዳጄ አደጋው በደረሰበት አካባቢ የሚኖሩ ሰዎች የተደረገላቸውን ቃለመጠይቅ አዳምጦ የታዘበውን ሲያጫውተኝ አብዛኞቹ በገዢው ቡድን ተከታታይ በደል የሚደርስባቸው ብሄር ተወላጆች እንደሚመስሉ ጠቀሰልኝ። ይህ “ቤት የእግዚዐብሄር ኮንዶሚኒየም የገብረእግዚዐብሄር” በሆነባት አዲስ አበባ እየሆነ ስላለው ነገር የሚጠቁመው ትልቅ ነገር አለ። ስለሆነም ያገባናል የምንል ሁሉ በአደጋው የሞቱትንና የተጎዱትን እንዲሁም በአካባቢው የሰፈሩትን ሰዎች ማንነት አጣርተን ይፋ ማድረግ ይኖርብናል–የስርዐቱን ቆሻሻነት ፍንትው አድርጎ ለማሳየት።

የሞቱትን ነፍሳቸውን ይማርልን፣ ያለነውንም ለቆሻሻ ኑሮና ለቆሻሻ ሞት ከዳረገን ቆሻሻ ስርዐት ይገላግላን።

ከመሳፍንት ዘፈረንሳይ ለጋሲዮን
(tmesafint@gmail.com)


“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

Recent Posts

  • ለሱዳንና ኤርትራ ሲከራከሩ የነበሩት አበባው ባለመመረጣቸው “በጣም ተድጃለሁ” አሉ June 26, 2026 12:29 am
  • “ትህነግ ወደ ዓለምአቀፍ ወንጀለኛነትና አሸባሪነት እየተምዘገዘገ ነው” June 25, 2026 01:00 am
  • አሜሪካ በሕገወጡ ትህነግ አመራሮች ላይ ጠንካራ የቪዛ እገዳ ጣለ June 18, 2026 10:29 am
  • እንደ ሌሊት ወፏ የሚንቀሳቀሰው ኢህአፓ/ትብብር   June 18, 2026 09:36 am
  • የታርጋ ጫጫታ June 15, 2026 05:16 pm
  • ፋንታኹን ዋቄ ከአሜሪካ የሃይማኖት እልቂት አወጁ June 15, 2026 02:12 am
  • ሕገወጡ ትህነግ ወጣቶችን ለዳግም ዕልቂት እያሰናዳ ለፈረንጆች “ኢትዮጵያን አውግዙልኝ” እያለ ነው June 11, 2026 12:57 am
  • በሐዘንና ግልፅ ደብዳቤ ስም የተሸፈነ የድህረ ምርጫ ሀገር የማተራመስ ስትራቴጂ June 10, 2026 12:19 am
  • የጽምዶ ልክፍት June 9, 2026 12:49 am
  • ገዳዩ ማነው? አስገዳዩስ ማነው? June 5, 2026 02:37 pm
  • ጽንፈኝነት ግን በኢትዮጵያ ምድር ፈጽሞ ቦታ የለውም! June 5, 2026 01:47 pm
  • የትብብሩ “ብናሸንፍም ፓርላማ አንገባም” መግለጫ “ወንበር ስታጡ ነው” የሚል ከፍተኛ ተቃውሞ አስነሳ June 4, 2026 12:04 am
  • አዲሱ የትራምፕ የምርጫ መመሪያ፡ የአሜሪካ ዲፕሎማቶችን አፍ ያስዘጋ፤ ተቃዋሚዎች ተስፋ ያስቆረጠ June 3, 2026 08:50 pm
  • “ኢህአፓ ከምርጫው በኋላ ይሰነጠቃል” May 29, 2026 07:07 pm
  • ሪፖርተር፡ “ስውር ተልዕኮ” – በከባድ ወንጀል ሊከሰስ May 6, 2026 11:55 pm
  • የፋኖ ኃይል በደረሰበት ጉዳት ሃምሳ ሺህ የሚጠጋ ትጥቅ ጥሎ ጠፋ April 29, 2026 02:27 pm
  • አዲሱ የቴድሮስ ካሳሁን 888 ኮድ፤ እንደ 666?! April 15, 2026 05:53 am
  • ምኑ ነው ያሳቃችሁ፤ ያስደሰታችሁ? April 2, 2026 10:52 am
  • የጀዋር መሃመድ የፖለቲካ ማንነት እና የባዕዳን ተልዕኮ April 2, 2026 10:16 am
  • ከግብፅ በዳያስፖራ ትርምስ ጠማቂዎች በኩል ፋኖ ወደ አዲስ አበባ የላከው “ስጦታ” March 27, 2026 09:14 am
  • “ሰላማዊ ታጋዮቹ” እነ ልደቱ ከአራጁ ሸኔ ጋር ተጣምረዋል March 25, 2026 01:04 pm
  • ጸረ-ኢትዮጵያዊ የሆነው የሪፖርተር አዘጋገብ March 19, 2026 11:54 am
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ የኦሮሚያ የልማት ድርጅቶች March 18, 2026 10:48 am
  • የጃኖ ስጦታና የዶሮ ፖለቲካ በጎንደር March 10, 2026 09:24 am
Copyright © 2026 · Goolgule