ኢትዮጵያውያን ልዩ ልዩ በዓሎቻቸውን ስለየበዓላቱ ትርጉም ባላቸው ዝማሬዎችና ጭፈራዎች ያደምቁታል፡፡ ከእነዚህ አንዱ የሆነው የዘመን መለወጫንም ‹‹እንቁጣጣሽ››ን በ‹‹አበባ አየሽ ሆይ›› ያደምቁታል፡፡
እንቁጣጣሽ ሲመጣ ልጃገረዶች ከበሯቸውን ይዘው በየቤቱ እየዞሩ ‹‹አበባ አየሽ ሆይ›› እያሉ ሲጨፍሩ፣ ድምፃዊቷ ዘሪቱ ጌታነህም በየራዲዮ ጣቢያው ‹‹እንቁጣጣሽ እንኳን መጣሽ…›› እያለች በቀጭኑ ድምጿ የምታቀነቅነው ዘፈን ሲሰማ በዓሉን ለመቀበል ያለውን ስሜት ሞቅ ሞቅ ያደርጋል፡፡
ቀደም ሲል ልጃገረዶች ‹‹አበባ አየሽ ሆይን›› ለመጨፈር ተቧድነው እንግጫ ይዘው፣ ከበሯቸውን እየመቱ ከዋዜማ እስከ በዓሉ ዕለት ይጨፍራሉ፡፡ ያኔ የነበረው ጭፈራ የግጥምና የዜማ መፋለስ ችግር አልነበረበትም፡፡ ጨፋሪዎቹም ለዓይን ሞላ ያሉ ነበር፡፡ ጨፍረው ሲያበቁም በዋናነት የሚሸለሙት ቤት ያፈራውን ስለነበር ለሳንቲምና ለብር ብዙም ቦታ አልነበራቸውም፡፡ ልጆቹም ‹‹አበባ አየሽ ሆይ…›› ሲሉ የሚጨፈርላቸው ሰዎችም ትእግስቱ ነበራቸው፣ ለባህሉም ቦታ ይሰጡ ነበር፡፡
ዘንድሮስ? የዘንድሮዎቹ የአዲስ አበባ ጨፋሪዎች ቁጥር ለዓይን የጎደሉ፣ ግጥሙንና ጭፈራውን በተሟላ መልኩ የማይገልጹ እንደሚበዙባቸው ይነገራል፡፡ ልጆቹም እየተዘዋወሩ ሲጨፍሩ የሚጨፈርላቸው ሰዎች ሊለመኑ የተመጣባቸው ስለሚመስላቸው ‹‹አድርሰናል›› ወይም ደግሞ ‹‹አያስፈልግም ሂዱ›› ተብለው ልጆቹ ይመለሳሉ፣ ይባረራሉ፡፡ በምርቃት የሚሸኙ ጨፋሪዎች ካሉ እድለኞች ናቸው፡፡
የዘንድሮዎቹ ልጆች ሙሉውን ጭፈራ እንዲጨፍሩ ዕድሉ ቢሰጣቸውም፣ ሽልማቱ ዳቦ ይሆናል የሚል ግምት አያድርባቸውም፣ ሸላሚዎቹም ‹‹ዳቦ መች ይፈልጉና›› ብለው አቅም የፈቀደውን ሳይሆን ‹‹ይሄ ይበቃቸዋል›› በሚል ስሜት ገንዘብ ይሰጧቸዋል፡፡ ከሦስት ሳምንት በፊት የተከበረው ቡሄም እንደዚያው፡፡ የቡሄንና የእንቁጣጣሽን ጭፈራ በቀደሙት ጊዜያት ጠንቅቀው የሚያውቁ ሰዎች አሁን ላይ ያለው ጭፈራ ግጥሙም ዜማውም የተራራቀ እንደሆነ የሚናገሩትም ለዚሁ ነው፡፡
እነዚህ ባህላዊ እሴቶች ዘመን እየተለወጠ ሲሄድና ሥልጣኔ ሲመጣ አብረው የሚቀየሩ፣ የሚጠፉ ወይም የሚረሱ መሆን የለባቸውም፡፡ እነዚህ ጭፈራዎች በዓላቱ ሲመጡ ሁሌም መከናወን የሚገባቸው ኢትዮጵያዊነትን የሚገልፁ ናቸው፡፡
ለዘመናት የቆየን ባህል ስለማስተዋወቅና ለትውልድ ስለማስተላለፍ ሲወሳ የትግራይ፣ የላስታ ላሊበላና የሰቆጣ አሸንዳ (ሻዳይ) እንዲሁም የኦሮሞ ተወላጆች እያሴን ማስታወስ ተገቢ ነው፡፡ የትግራይ ልጃገረዶች ወገባቸውን በቄጤማ ሸብ አድርገው ከበሯቸውን እየደለቁ ከቦታ ቦታ እየተዘዋወሩ የሚጨፍሩት እዚያው ትግራይ ብቻ አይደለም፡፡ አሸንዳ በተከበረበት ያለፈው ሰሞን አንዳንድ የአዲስ አበባ ጎዳናዎች አሸንዳን የሚጨፍሩ ልጃገረዶችን ሲያስተናግዱ ነበር፡፡ ምሽት ላይም እንደልጅነታቸው ጸጉራቸውን የተላጩ፣ አብዛኛውን ተላጭተው የተወሰኑ ቦታዎች ላይ ጸጉራቸውን ጉች ጉች ያደረጉ ጎረምሶች በየምሽት ክበቡ እየገቡ በሚያስተጋባ ጭብጨባቸው፣ በኃይለኛ በሚደልቁት ከበሯቸው ድምፅ እንዲሁም ዝላይ እየታጀቡ ሲጨፍሩ ነበር፡፡
መስቀልንም በተመለከተ የኦሮሚያ ተወላጆች የእያሴ ጭፈራን እርጥብ ሣር በመያዝ ዱላቸውን ወደ ሰማይ ቀስረው በእግራቸው መሬቱን እየደበደቡና እየዘለሉ ሁሌ በየዓመቱ ይጨፍራሉ፡፡ ልክ እንደ እያሴና አሸንዳ የአበባ አየሽ ሆይ እና ሆያሆዬ ጭፈራዎች ባህሉንና ታሪኩን በጠበቀ መልኩ ለተተኪው ትውልድ ሲተላለፉ ግን አይታዩም፡፡
ፈረንጆቹ የሃሎዊን በዓልን ሲያከብሩ ልጆቻቸው የተለያዩ አልባሳትን በመልበስ በየቤቱ እያንኳኩ ከረሜላና ሌሎች ጣፋጮችን ሲሰበስቡ ይታያሉ፡፡ ይህ ልማድ በእነርሱ ዘንድ በፊትም ነበር፣ አሁንም አለ፡፡
ብዙዎች እንደሚያምኑት የኢትዮጵያ ብቻ የሆኑት ‹‹አበባ አየሽ ሆይ›› እና ‹‹ሆያ ሆዬ››ም ለትውልድ እየተላለፉ በፊት ወደነበራቸው የግጥምና የዜማ ወግና ባህል መመለስ ሲገባቸው ይህ ሲሆን አይታይም፡፡ በርካታ ዘመናትን ተሻግረው የመጡትን ባህሎች የማሠልጠን ስሜትም ሆነ የጊዜ መለወጥ ተጽዕኖ ሊያደርግባቸው ቢገባም አጨፋፈሩ እየተቃኘ ያለው በሥልጣኔ ሳይሆን ጭራሽ ሊጣጣም በማይችል ግጥምና ዜማ ነው፡፡
በኢትዮጵያ በፌዴራል ደረጃ፣ ክልሎችም እንደ ክልል አበባ አየሽ ሆይንም ሆነ ሆያ ሆዬን የቱሪስት መስህብ የማድረግና ባህልና ታሪኩን የማስጠበቅ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ የትግራይ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ጠፍቶ የነበረውን የአሸንዳ ባህል ለመመለስ በዕድሜ የገፉትን እናቶች አሳትፎ ባህሉ ለዛሬዎቹ ሕፃናትና ታዳጊዎች እንዲመለስ አድርጓል፡፡ የቱሪስት መስህብ ለማድረግም ጠንክሮ እየሠራ ነው፡፡
የአዲስ አበባ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ በሚዲያዎችና በተለያዩ አጋጣሚዎች ሆያ ሆዬም ሆነ አበባ አየሽ ሆይ ፈር መልቀቃቸው ሲነገር ዓመታት ቢያልፉም ጆሮ ሲሰጥ አልተስተዋለም፡፡ በመሆኑም የቱሪስት መስህብ ሊሆን የሚገባው ባህል እንደዋዛ እየተሸረሸረ ይዘቱን ለቋል፡፡
በጉዳዩ ላይ የተለያዩ ጥናቶችና መፍትሔዎች ቢቀርቡም ወደ ተግባር ሲለወጡም አይታዩም፡፡ በመሆኑም እንደነበረው ሳይሆን ከዓመት ዓመት ለዛቸውን ሲያጡና ማስተላለፍ የሚገባቸውን መልዕክት ሲሳቱ ይስተዋላሉ፡፡(ምዕራፍ ብርሃኔ)
Leave a Reply