• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ምርጫ ቦርድ የስድስተኛውን አገራዊ ምርጫ ውጤት አሳወቀ

July 10, 2021 08:09 pm by Editor Leave a Comment

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም በ440 የምርጫ ክልሎች የተከናወነውን አጠቃላይ ምርጫ  ውጤት ሐምሌ 3 ቀን 2013 ዓም  በስካይላይት ሆቴል በተከናወነ መርሐ ግብር ይፋ አደረገ፡፡

ቦርዱ እስካሁን በሒደት ካሳወቃቸው የተረጋገጡና ጊዜያዊ የምርጫ ውጤቶች በማስከተል ምርጫው በተከናወነ በ20 ቀናት ውስጥ የምርጫውን ውጤት ማሳወቅ እንደሚኖርበት በሕግ በተደነገገው መሠረት ቅዳሜ ሐምሌ 3 ቀን 2013 ዓ.ም. በስካይላይት ሆቴል በተከናወነ መርሃ ግብር አስታውቋል፡፡

ቦርዱ ይፋ ባደረገው ውጤት መሠረትም፣ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ድምጽ ከተሰጠባቸው 425 የምርጫ ክልሎች መካከል

ብልጽግና ፓርቲ 410 መቀመጫዎችን ያሸነፈ ሲሆን፣

የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ አምስት፣

የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ ፓርቲ አራት፣

በኦሮሚያ የተወዳደሩ ሦስት የግል ዕጩዎች፣

በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አንድ ዕጩ፣

እንዲሁም በደቡብ ክልል የጌዴኦ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ሁለት መቀመጫዎችን አግኝተዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ በዘጠኝ የምርጫ ክልሎች ድጋሚ ቆጠራ እንዲከናወን የተወሰነ ሲሆን፣ በሰባት የምርጫ ክልሎች ደግሞ ምርጫው በድጋሚ ይከናወናል፡፡

በአጠቃላይ በሁሉም ክልሎች 38,954,430 መራጮች ለምርጫው የተመዘገቡ ሲሆን፣ ከተመዘገቡ መራጮች መካከል

በአዲስ አበባ 99 በመቶ፣

በአፋር 97 በመቶ፣

በአማራ 94 በመቶ፣

በቤንሻንጉል ጉሙዝ 55 በመቶ፣

በድሬዳዋ 95 በመቶ፣

በጋምቤላ 89 በመቶ፣

በኦሮሚያ 96 በመቶ፣

በሲዳማ መቶ በመቶ እንዲሁም በደቡብ ክልል 91 በመቶ መራጮች መርጠዋል፡፡

በተጨማሪም፣ ለክልል ምክር ቤቶች በተደረጉ ምርጫዎች ብልጽግና ፓርቲ ያሸነፈ ሲሆን፣ በአፋር የአርጎባ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት አንድ የክልል ምክር ቤት መቀመጫ፣ በአማራ ክልል የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ ስድስት የክልል ምክር ቤት መቀመጫዎችን፣ በጋምቤላ ክልል የጋምቤላ ሕዝቦች ነጻነት ንቅናቄ ሁለት የክልል ምክር ቤት መቀመጫዎችን፣ እንዲሁም በደቡብ ክልል ኢዜማ አራት፣ የጌዴኦ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ሁለት መቀመጫዎችን አሸንፈዋል፡፡ ይኼም እስካሁን ድረስ በአንድ ፓርቲ ብቻ ተይዘው በነበሩ የከልል ምክር ቤቶች ውስጥ አዲሱ ክስተት ሆኗል፡፡

የቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ አቶ ውብሸት አየለ ባሰሙት የምርጫ ሒደት ሪፖርት፣ ለምርጫው የቁሳቁስ ዝግጅት 847.7 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገ ሲሆን፣ በ674 የምርጫ ክልሎች የመራጮች ምዝገባ ተከናውኗል፡፡

የምርጫ ምልክት በወሰዱ 49 የፖለቲካ ፓርቲዎች እንዲሁም የግል ተወዳዳሪዎች አማካይነት 9,505 ዕጩዎች የተመዘገቡ ሲሆን፣ 148 የግል ዕጩዎችና 1987 ሴት ዕጩዎች ተወዳድረዋል፡፡

በጠቅላላ 152700 የምርጫ አስፈጻሚዎች የተሠማሩ ሲሆን፣ በምርጫ ቀን 42585 የምርጫ ጣቢያዎች ተከፍተው ድምጽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡ ቦርዱ በሒደቱ ያገዙትን የተለያዩ 39 ድርጅቶችንም አመስግኗል፡፡

የቦርዱ ሰብሳቢ ወ/ሪት ብርቱካን ሚዴቅሳ በዕለቱ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር ምርጫው የተከናወነው ቀላልና አስደሳች እንዲሁም ውጤቱ ይኼ ነው በሚባል ጊዜ የተከናወነ እንዳልሆነ በማሳወቅ፣ ምርጫው የተከናወነው በተለዋዋጭ ሁኔታዎች፣ የጸጥታ ችግር በነበረበት፣ ዜጎች በተለያዩ ችግሮች ውስጥ በነበሩበትና ውጣ ውረድ በነበረበት ጊዜ የተከናወነ ነው ብለዋል፡፡

ይሁንና ቦርዱ ባስቀመጠው መረሃ ግብር መሠረት የሕዝብን ድምጽ ወደ ሥልጣን ለመቀየር ሲሠራ ቆይቷል ያሉ ሲሆን፣ ቦርዱ ያደረገውን ምርጫ ከነ እንከኖቹ ባለድርሻዎቹ እንዲያዩት ለማድረግ በሚል ውጤት ማሳወቂያ መርሃ ግብሩ እንደተዘጋጀም አስታውቀዋል፡፡ በርሃ ግብሩም አገራችን በምርጫ ብቻ ሥልጣንን ከአንድ እጅ ወደ ሌላ እንዲሸጋገር የምናረጋግጥበት መድረክ ይሆናል ብለው እንደሚያምኑም ጠቅሰዋል፡፡

የምርጫ ቦርድ የደባርቅ የምርጫ ክልል ኃላፊ ሳዲያ ዳውድ በመድረኩ ባስተላለፉት መልዕክት አገሪቱ እንዲኖራት በሚመኙት ዴሞክራሲያዊና ፍትሐዊ ምርጫ ውስጥ እንዲሳተፉ በመደረጋቸው ደስታ እንደተሰማቸው በመግለጽ ቦርዱንም አመስግነዋል፡፡ እንደ እርሳቸው እምነትም ምርጫው ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለዓለም ትምህርት መሆን የሚችል ሆኖ እንዳለፈ አክለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ሲቪል ማኅበረሰቦች ጥምረት ለምርጫ ሰብሳቢ አቶ ታምራት ከበደ በመድረኩ ባደረጉት ንግግር ጥምረቱ ለምርጫ ሲባል በ2011 ዓ.ም. መመሥረቱን ጠቁመው፣ ለዚህም ሲባል የመራጮች ትምህርትና የሚዲያ ሞኒተሪንግ ተግባራት መከናወናቸውን ተናግረዋል፡፡ ምርጫውን ለመታዘብም ጥምረቱ 144 ታዛቢዎችን ያሰለጠነና 117 ያህል ታዛቢዎችን ደግሞ እንዳሰማራ አስታውቀዋል፡፡

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኢትዮጵያ ቋሚ ተወካይ ወኪል ሞሪን አቺንግ ምርጫ ቦርድን ምርጫውን ግልጽ በሆነ መንገድ በማካሔዱ ያመሰገኑ ሲሆን፣ የአውሮፓ ኅብረትን ጨምሮ የተለያዩ ለጋሾችን አመስግነዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ምርጫው መስከረም ላይም የሚቀጥል እንደሆነ በመግለጽ፣ ለዚህ ድጋፍ ለማድረግ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ቁርጠኛ እንደሆነም ተናግረዋል፡፡

በኢትዮጵያ የጀርመን አምባሳደር ስቴፋን አዎር የዛሬው የመጀመሪያው ዙር ምርጫ ውጤት ማስታወቂያ ሒደት የኢትዮጵያ ዴሞክራሲ ሽግግር ማሳያ ነው በማለት፣ ለምርጫ የወጡ በርካታ ኢትዮጵያውያንን አመስግነው አድንቀዋል፡፡ አክለውም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ቁርጠኝነትና ገለልተኝነትን ያደነቁ ሲሆን፣ በተለይም ለቦርዱ ሰብሳቢ ወ/ሪት ብርቱካን ምስጋና አቅርበዋል፡፡

አምባሳደሩ በአንዳንድ ክልሎች የዘገየውን ምርጫ በማስመልከትም ምርጫ በትግራይም ይደረጋል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ ያሉ ሲሆን፣ ለችግሩ ወታደራዊ መፍትሔ የለውም ብለዋል፡፡ በትግራይ መንግሥት ያወጀውን የተኩስ አቁም እርምጃ ያደነቁ ሲሆን፣ በቀጣይም ያልተገደበ የሰብዓዊ ዕርዳታ መስመር እንዲኖርም አሳስበዋል፡፡ ከዚህ ባለፈም በግጭቱ ተሳታፊ የሆኑ አከካላት በሙሉ የተኩስ አቁም ውሳኔውን እንዲቀላቀሉ ጠይቀዋል፡፡ ከፍተኛ የሰብዓዊ ቀውስ በትግራይ እየታየ ነው ሲሉም አክለዋል፡፡ ”በትግራይ የሚያስፈልጉ የሰብዓዊ ዕርዳታዎችን ማዘግየት ይቅር የማይባል የሰብዓዊ ድጋፍ ግዴታችንን ሳንወጣ መቅረት ነው፤” ብለዋል፡፡

ለኢትዮጵያ ችግሮች መፍትሔ ለመሻት ብሔራዊ ውይይት እንደሚያስፈልግ በመናገር ለዚህም ድጋፍ እንደሚያደርጉ ቁርጠኝነታቸውን በማረጋገጥ፣ ጉዞ ደጋፊ ጓደኛ ሲኖር ደግሞ ቀላል ይሆናል ሲሉ አጋርነታቸውን አረጋግጠዋል፡፡

በመድረኩ አስተያየታቸውን የሰጡት የቦርዱ አባል ወ/ሮ ብዙወርቅ ከተተ፣ ከፍተኛ ድምጽ ያገኘ ፓርቲ መንግሥት እንዲመሠርት የሚያደርገው የምርጫው ሥርዓት መቀየር እንዳለበት እንደሚያምኑ በመድረኩ የተናገሩ ሲሆን፣ ይኼም የፖሊሲ ጉዳይ ስለሆነ ቦርዱ እንደሚወያይበትም አስታውቀዋል፡፡

የቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ አቶ ውብሸት አየለ በበኩላቸው፣ በቦርዱ በነበራቸው ቆይታ የቦርዱን የሥራ ማሻሻያዎች በሚሠሩበት ጊዜ በቦርዱ የቆዩ ሠራተኞችን ወደ ሌላ የመንግሥት ተቋም ማሸጋገር አስፈልጎ ውሳኔ ከተላለፈ በኋላ፣ ለሠራተኞቹ ይኼንን ማሳወቅ እንደ ግለሰብ ከባድ እንደነበረባቸው የተናገሩ ሲሆን፣ ቦርዱ በፖለቲካ ፓርቲዎች የሴቶች ተሳትፎ እንዲጨምር ማበረታቻ ተደርጎ መሠራቱን እንደ ስኬት እንደሚያዩት ተናግረዋል፡፡

የቦርዱ ሰብሳቢ ብርቱካን ሚዴቅሳ በበኩላቸው ከቦርዱ አባላት በርካታ ነገሮችን መማራቸውን በማስታወስ፣ በምርጫው ሒደት ከባድ የነበረው የሎጂስቲክስ ሥራው እንደነበረ አስታውቀዋል፡፡ ይኼም የሆነበት ምክንያት ኢትዮጵያ ትልቅ አገር ስለሆነችና የሚኖሩባትም ምን ያህል ትልቅና መልከ ብዙ እንደሆነች ስለማያውቁ አዳጋች እንደሚያደርገው በመጥቀስ፣ የሎጂስቲክስ ችግር ግን በሒደት እንደሚስተካከልና በዚሁ እንደማይቀጥል እምነታቸው እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ (ብሩክ አብዱ-ሪፖርተር)

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Left Column, News Tagged With: birtukan midekssa, election 2013, election 2021

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am
  • Rusted screws, metal spikes and plastic rubbish: the horrific sexual violence used against Tigray’s women July 4, 2025 01:48 am
  • በሞርሞን ቤ/ክ ዕርዳታ የኪዳነምህረት ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ማምለኪያ ሥፍራ አገኘች July 2, 2025 01:28 pm
  • የበረከት ስምዖን “አየር ላይ ትዕይንት” አየር ላይ ተበተነ July 2, 2025 01:24 am
  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am
  • ከትግራይ ሾልኮ የወጣው ምሥጢራዊው ሰነድ ምንድነው? May 20, 2025 09:18 am
  • በደቡብ ጎንደር በጸዳሉ ደሴ የተመሩት 72 ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ May 19, 2025 02:24 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule