
- በሶማሌና በአፋር ክልል አዲስ ዕዞች ይቋቋማሉ፤ ለምን?
የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጪ ግንባር /ህወሓት ሊያጣው የማይፈልገውን የመከላከያና የደኅንነት ሥልጣንን አስጠብቆ ለመኖር ፍትጊያ እያደረገ መሆኑ በተደጋጋሚ የሚገለጽ ቢሆንም ብወዛው እንደማይቀር የጎልጉል የአዲስ አበባ መረጃ አቀባይ ጠቁሟል። መከላከያ በኮሚቴ (ካውንስል) ሊመራ ነው። አራቱ የኢህአዴግ ድርጅቶች አንድ አንድ ወኪል አላቸው። በሶማሌና አፋር ክልል ሁለት አዲስ ዕዞች ይቋቋማሉ፤ በማን እንደሚመሩ ለጊዜው አልታወቀም።
ይህንን አዲስ አወቃቀር ተግባራዊ ለማድረግ አዲሱ ጠ/ሚ ዓቢይ አህመድ የመከላከያ ሠራዊት ከፍተኛ አመራሮችን የሥራ ኃላፊነት የሚመለከት ብወዛ ለማካሄድ ብሎም በጡረታ ለመሸኘት በደመቀ መኮንንና በአባዱላ ገመዳ የሚመራ የመከላከያ ከፍተኛ መኮንኖችን ያካተተ አንድ ግብረ-ኃይል (ታስክፎርስ) እንዲቋቋም አድርገዋል። እንደ ጎልጉል ዘጋቢ የመረጃ ምንጮች ከሆነ ግብረኃይሉ በዋናነት የሚከተሉትን ተግባራት እያከናወነ እንደሚገኝ ይገኛል።
- ሁለት አዳዲስ ዕዞች ያቋቁማል፤
አሁን ካሉት አራት ዕዞች፣ ሰሜን ዕዝ (መቀሌ)፣ ደቡብ ምስራቅ ዕዝ (ሐረር)፣ ምዕራብ ዕዝ (ባህር ዳር) ማዕከላዊ ዕዝ ጠቅላይ መምሪያ (አዲስ አበባ ጃንሜዳ) በተጨማሪ ሁለት ዕዞችን ለማቋቋም የቅድመ ዝግጅት ሥራዉ ተጠናቋል። በዚህም መሠረት አዲስ የሚቋቋሙት ሁለት ዕዞች፤ የሰሜን ምስራቅ ዕዝ (አፋር) እና የምስራቅ ዕዝ (የኢትዮጵያ ሶማሌ) ላይ እንደሚቋቋሙ ከመረጃው ለማረጋገጥ ተችሏል።
ቀደም ሲል በነበረዉ አሠራር አሁን አዲስ ዕዝ እንዲመሠረት የታሰበባቸው ክልሎች ውስጥ በክፍለ ጦር ደረጃ ሠራዊት ነበር። መረጃው በዝርዝር እንዳሰፈረው የአፋርና ኤርትራ አዋሳኝ ቦታዎች የህወሓቱ ሌ/ጄ ገብራት አየለ በሚያዘው የሰሜን ዕዝ ሥር ባለ አንድ ክፍለ ጦር የሚመራ ሲሆን የኢትዮጵያ ሶማሌው ደግሞ በተመሳሳይ መልኩ ሌላኛው የህወሓት ጄኔራል አብርሃ ወ/ማርያም ሐረርን ማዕከል ባደረገው የደቡብ ምሥራቅ ዕዝ ሥር ባለ ክፍለጦርና ተወርዋሪ ቃኝ ሻለቃዎች ይመራ ነበር። በዚሁ መሠረት በአዲሱ አወቃቀር በአፋር ክልል የሰሜን ምስራቅ ዕዝ፤ በኢትዮጵያ ሶማሌ ደግሞ የምስራቅ ዕዝ ተብሎ በአዲስ መልኩ ይቋቋማሉ።
- የኤታማዦር ሹመትን የተመለከቱ ዝርዝር ነጥቦችን ይፈትሻል፤
ከዚሁ ጋር ተያይዞ አስራ ሰባት አባላት ያሉት የወታደራዊ ካዉንስል በአዲስ መልኩ ስለሚቋቋምበት ሁኔታ ቅድመ ዝግጅትች በመካሄድ ነው። ከዚህ ቀደም በሳሞራ የኑስ የበላይነት ተጠርንፎ ተይዞ የነበረዉ የኤታማዦር ሹም ኃላፊነት ቦታ እንደ ቀድሞው በአንድ ጄኔራል የሚመራ ቢሆንም፣ የዉሳኔ አሰጣጥ በተመለከተ “የኤታማዦር ኮሚቴ” እንዲሆን ይደረጋል። በዚህም መሠረት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከተነሳ ወይም ከተጠናቀቀ በኋላ ባሉ ጥቂት ጊዜያት ዉስጥ የሳሞራ የኑስ ጡረታ መዉጣት በአገዛዙ ሚዲያ ይፋ ተደርጎ አዲሱ የቡድን ወይም የኮሚቴ ውሳኔ አሰጣጥ የሚመራው አሠራር ይፋ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።
ሳሞራን ይተካል ተብሎ የሚጠበቀዉ በአሁኑ ሰዓት የመከላከያ የሥልጠናና ዘመቻ መምሪያ ኃላፊ የሆነዉ ጄኔራል ሰዓረ መኮንን ይመር እንደሚሆን ተጠቁሟል። ሰዓረ በአዲሱ ኢታማዡር ኮሚቴ ኢታማዦር ተብሎ የሚሾም ይሆናል። ቀሪዎቹ የኮሚቴዉ አባላት እንዲሆን የተመለመሉት፤
1 – ጄኔራል ብርሃኑ ጁላ ገለልቻ (የሰላም አስከባሪ ግዳጅ ኃይል ዋና ኃላፊ – ኦህዴድ)
2 – ጄኔራል አደም መሐመድ ሟህመድ (የአየር ኃይል ዋና ኃላፊ – ብአዴን)
3 – ሌ/ጄኔራል ሞላ ኃይለማርያም አለማየሁ (የኮር አመራር የነበረ- ከደኢህዴን)
ሰዓረን ጨምሮ ብርሃኑን እና አደምን የምክትል ጠቅላይ ኤታማዦር ሹመት በመስጠት የሙሉ ጄኔራልነት ማዕረግ ጥር 26፤ 2010ዓም ያጎናጸፋቸው ሃይለማርያም ደሳለኝ ነበር። በዚሁ ዕለት ሞላም የሌ/ጄኔራልነት ማዕረግ ተሰጥቶታል።
- ወታደራዊ ካውንስል ያደራጃል፤
አስራ ሰባት አባላት ያሉበት የመከላከያ ወታደራዊ ካዉንስል ሲደራጅ በዋናነት የኤታማዦር ኮሚቴዉን፣ የዕዝ ኃላፊዎችን እንዲሁም የወታደራዊ ደህንነት፣ የሎጀስቲክስ፣ የልዩ ኃይል፣ የመስመር ኃይል ኮር አመራር የበላይ ኃላፊዎችን ባካተተ መልኩ እንደሚሆን የጎልጉል ዘጋቢ አመልክቷል። የኤታማዦር ቦታዉ እንደማይነካበት ቃል የተገባለት ህወሓት በወታደራዊ ካዉንስሉ በኩል ቁጥሩ የላቀ አባላቱን ለማስመልመል የሚችለውን ሁሉ እያደረገ መሆኑንም መረጃ አቀባዮቹ አስታውቀዋል።

በዚሁ መሠረት ህወሓት በመከላከያ ወታደራዊ ካዉንስል ዉስጥ ወሳኝ ሚና እንዲጫወቱለት ወደፊት ያወጣቸዉ ዋና ዋና አመራሮቹ የሚከተሉት ናቸው፤
- ሜ/ጄኔራል አታክልቲ በርሀ ገብረማርያም
- ሜ/ጄኔራል ያይኔ ስዩም ገብረማርያም
- ሜ/ጄኔራል ሙሉ ግርማይ ገ/ህይወት
- ሜ/ጄኔራል ፍሰሃ ኪ/ማርያም ወ/ሂወት
- ሜ/ጄኔራል ገብራት አየለ
- ሜ/ጄኔራል ፍስሓ አዳነ
- ሌ/ጄኔራል መሐሪ ዘውዴ ገ/ማሪያም
- ጄኔራል አብረሃ ወ/ማርያም ገንዘቡ
- ጄኔራል ሰዓረ መኮንን ናቸዉ። (በተራ ቁጥር 5 እና 6 ከተጠቀሱት በስተቀር ሌሎቹ በሙሉ ሃይለማርያም ደሳለኝ በጥር ወር ለፕሬዚዳንቱ አስቀርቦ ሹመት ያሰጣቸው ናቸው፤ ይህም የሚያሳየው ህወሓት የፖለቲካ ሥልጣኑን ማጣቱ እውን እየሆነ ሲሄድ የመከላከያውን ጉዳይ ከእጁ እንዳይወጣ አስቀድሞ የቤት ሥራውን ሲያከናውን እንደነበር ጠቋሚ ነው)
በዝርዝሩ እንደተመለከተው ከአስራ ሰባቱ ወታደራዊ ካዉንስል አባላት ውስጥ ዘጠኙ የህወሓት ነባር ታጋዮች እንዲሆኑ ህወሓት የሞት ሽረት ትንቅንቅ በማድረግ ላይ ይገኛል። እንደ ጎልጉል ምንጭ ከሆነ ሳሞራ “ጥቂት ጊዜ ስጡን” ያለበት ምክንያትም ከዚሁ ጋር የሚያያዝ እንደሆነ ግምታቸውን ሰጥተዋል። የጻድቃን ገብረትንሳኤ መከላከያውን እና ደኅንነቱን ሳንነካ የፖለቲካ ተሃድሶ እናድርግ ዕቅድም ከዚሁ ጋር እንደሚያያዝ አስተያየት ይሰጥበታል።
በሶማሌ ክልል ህወሓት አለው ከሚባለው ልዩ ፍላጎትና አሁን ካለው ችግር አኳያ፣ እንዲሁም ለትግራይ አጎራባች ከሆነውና ሰፊ ክልሉ የተወሰደበት አፋር ላይ አዳዲስ የጦር ዕዞች ለማቋቋም የተያዘው ዕቅድ ዓላማው በተለይ ከህወሓትም ሆነ ከትግራይ ጥቅም አንጻር ምን እንደሆነ የመረጃው ምንጮች እየመረመሩ እንደሆነ የጎልጉል ዘጋቢ አመልክቷል። የኃላፊዎች ምደባ ይፋ ሲሆን ጉዳዩ ይበልጥ ግልጽ እንደሚሆንም አክለዋል። የሶማሌ ክልል ልዩ ሃይል በህወሓት ጄኔራሎች የሚመራና እንዳሻው የሚፈነጭ፣ የክልሉም ርዕሰ መስተዳድር አብዲ ኢሌይ ከልካይ የሌለው በደም የተጨማለቀ አምባገነን መሆኑን የሚጠቅሱ በሁለቱ ክልሎች ህወሓት የራሱን ሰዎች እንደሚያስቀምጥ ከወዲሁ አስታውቀዋል።
ኦህዴድና ብአዴን በመከላከያና በደኅንነት ውስጥ ያለው ውክልና ሙሉ በሙሉ ሚዛን የሳተ እንደሆነ በግምገማ ወቅት ቁርጠኛ አቋም ይዘው ሲሟገቱበት እንደነበር የሚታወስ ነው። በተለይም ኦህዴድ በያዘው የፈረጠመ አቋም የተነሳ ግምገማው መራዘሙና በመቋጫው ህወሓት አምኖ ማስተካከያ እንዲደረግ ስምምነቱን መግለጹ አይዘነጋም። አስራ ሰባት አባላት በሚኖሩት ካውንስል ውስጥም ዘጠኙን የህወሓት ጄኔራሎች ከወሰዱት ቀሪው ስምንት በኦህዴድ፣ በብአዴንና በደኢህዴን መካከል እንዲሆን የመደረጉ ጉዳይ በተለይ ኦህአዴድና ብአዴን ለመቀበል የሚቸግራቸው ከመሆኑ አንጻር አሁን ያለው አካሄድ ተለዋጭ አሠራር ሊቀርብበት ይችል ይሆናል የሚል ግምት አለ። ህወሓት ግን ከዘጠኝ ያነሰ ድምፅ ሰጪዎች በሚኖሩበት ካውንስል ውስጥ የሚፈልገውን አጀንዳ በድምፅ ብልጫ ማስፈጸም የማይችልበትን አካሄድ ለመቀበል የተዘጋጀ አይመስልም በማለት የመረጃው ምንጮች ለጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ የአዲስ አበባ መረጃ አቀባይ አስረድተዋል።
ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ®ንብረት ናቸው። ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (https://www.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን።
Selam Wendimoche,
Please add FB link so I can post or share this article to my FB page
Thank you
Ayu
Thanks for your suggestion. There is some tech issue and we are working on it.
Regards,
Editor
ትግሬዎች 5% ሆነው እንዴት ከ ግማሽ በላይ ፣ ማለትም ከ 17 ወንበር 9 ኙ፣ ለ እኛ ይሰጠን ይላሉ? አሳፋሪ እና መሆን የማይገባው ነው። ይህን መፍቀድ የ27 አመቱን ግፍ አገዛዝ ቀጥሉ ማለት ነው። ሊኖራቸው የሚገባቸው አንድ ብቻ ነው። እዚህ ላይ ምንም አይነት ድርድር ማድረግ አይገባም።