
ዐባይ ቢሻው ይጉረፍ በጣና ላይ ነግሶ
አሎሃ ይደፍርስ ተከዜም ደም ለብሶ
ማሂንም አቋሽም ጓንግም በሙላቱ
መሻገሪያ ይንሳ እስኪያልፍ ክረምቱ
ይፎክር ያቅራራ ይኩራ በጉልበቱ
ድሮም እንዳይፀዳ በጎርፍ ውኃ ታጥቦ የጀግና ሰው ሞቱ
ያውቃሉ እናውቃለን ዛሬም እንደ ጥንቱ
ደም በደም ይፀዳል ደም ነው ሥርየቱ።
ለጀግና ዕምባ አይረጩም ፀጉርም አይላጩም
ዋይታና ለቅሶ ሙሾ አይደረድሩም ወይም ፊት አይነጩም
እንደ አባት አደሩ እንደ ጎንደር በሃል
ደም ነው ሥርየቱ ደም በደም ይፀዳል።
አለፋ ጣቁሳ ደንቢያና ፎገራ
ጭልጋ ገለድባ ከሽንፋ እስከ ቋራ
ጎዛምን በላያ ከመተክል ፓዌ ከሻግኔ ወንበራ
ከፍኖተ ሰላም ማንኩሳ እንጅባራ
መተማ ሰራቆ ጫቆና አዳኝ አገር
ቆላ ደጋ ዳሞት ቋሪትና አቸፈር
እነሴና ነብሴ ሞጣ ቀራኒዎ ጭስ ዐባይ ባህር ዳር
ነፋስ መውጫ ጋይንት እስቴ ደብረ ታቦር
መልዛ መቀጠዋ ዝዊና ዘሃዬ
እንደ ኮስትር በላይ ገልሞና ገብርዬ
ከዚያ እስከዚህ ድረስ ሞፈር መቁረጥ ያውቃል
ካልተለበለበ እምቢተኝነቱ መቼ ይታረቃል።
ወልዲያና ሰቆጣ ዳህናና ሳህላ
ዳሆጭና ኮዛ ኪንፋዝ ወይ በገላ
ጠለምትና አምባራስ ሰሜን ጃናሞራ
ወልቃይት ጠገዴ አጅሬ ጃኖራ
ቦህ ቦህና ማሂን ሰራቆ ገንበራ
አርማጭሆና እንቃሽ አይባና ወገራ
አያውቅም ለቅሶ ደም ይረጫል እንጂ እየፈላ አሞቱ
የይሁዳን ክህደት ቀራኒዎን ሲመስል ጎቤ መልኬ ሞቱ
እንደ አምላኩ ስቅለት ደም በደም ይፀዳል ደም ነው ሥርየቱ።
የካቲት 2009
አብርሃም በየነ (ፎቶ: አርበኛ ጎቤ)
Leave a Reply