
እለተ እሁድ 04/09/05 ከምሽቱ ሁለት ሰዓት በባህርዳር ከተማ አባይ ማዶ ተብሎ በሚጠራው ሰፈር እንዲሁም የብአዴን ዋና ፅ/ቤት ከሚገኝበት “የሰማእታት ሀውልት” ተብሎ ከሚጠራው ቦታ አቅራቢያ አንድ የፌደራል ፖሊስ በንፁሐን ዜጐች ላይ በከፈተው የሩምታ ተኩስ 16 ሰዎችን ሲገድል በርካቶችን አቁስሏል ከሆስፒታል ምንጮች እንደሰማሁት የሟቾች ቁጥር ከዚህም በላይ ሊያሻቅብ ይችላል ገዳዩ የፌደራል ፖሊሱ ከግድያው በኋላ ምንም እንኳን ቦታው ብዙ ወታደሮች የሚንቀሳቀሱበት አካባቢ ቢሆንም ከቦታው ሊያመልጥ ችሏል።አገዛዙን የተቃወመ ንፁሐን ዜጋ ሁሉ የሽብር ሴራ አከሸፍኩ እያለ የአሸባሪነት ታርጋ እየለጠፈ ወደ እስር የሚያወርደው የወያኔ መንግስት ጉያው ውስጥ ደብቆ ያቆየው የአገዛዙ የመንፈስ ልጅ አሸባሪ ሕዝብን ጨርሶ ሲያመልጥ “ስንት የሽብር ጥንስስ አከሸፈ” የተባለለት ፀረሽብር ግብረ ሀይል በቦታው የለም። ለነገሩ የወያኔ ደህንነት፥ወታደር፥ፀረሽብር ግብረ ሀይል፥ ፖሊስ፥ፌደራል ፖሊስ ገለመሌ አገዛዙን ከሕዝባዊ ማዕበል እንዲጠብቁ እንጅ የሕዝብን ደህንነት የሚጠብቁበት ስልጠናውም ልምዱም የላቸውም ።
ጽሁፉ ሙሉ በሙሉ ከነፎቶው የተወሰደው ከ “Addisu Wond” ላይ ነው።
በባህር ዳር የ12 ሰዎችን ህይወት ያጠፋው ግለሰብ አስክሬን ተገኘ
አዲስ አበባ ፣ግንቦት 5 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በባህር ዳር ከተማ ልዩ ስሙ አባይ ማዶ በተባለ አከባቢ ከትናንት በስቲያ አንድ ግለሰብ 12 ሰዎችን መግደሉ ይታወሳል፡፡ ከስፍራው የደረሰን መረጃ ግለሰቡ ሰክሮ እንደነበር ነው የሚያመለክተው።
የባህር ዳር ከተማ ፖሊስ ኮሚሽን መምሪያ ሀላፊ ኮማንደር ደረጀ አቻምየለህ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንደገለፁት ፥ ግለሰቡ በውል ባልታወቀ ምክንያት በመንገድ ላይ በከፈተው ተኩስ ከሞቱት 12 ሰዎች በተጨማሪ ሌሎች ሁለት ሰዎች ክፉኛ ቆስለዋል።
በሰዓቱም ግለሰቡን በቁጥጥር ስር ለማዋል ፖሊስ ክትትል ሲያደርግ እንደነበርና በመጨረሻም ራሱን በወንዝ ውስጥ በመወርወር መሰወሩን ገልፀው ነበር ። በአሁኑ ወቅት የግለሰቡ አሰክሬን በአባይ ወንዝ ውስጥ መገኘቱን ፖሊስ ገልጿል።
ድርጊቱን የፈፀመው ግለሰብ የፖሊስ አባል መሆኑን የገለፁት ኮማንደሩ ፥ ድርጊቱን የፈፀመበት ምክንያት ግለሰባዊ እንደሆነ አመልክተዋል ። ትናንት ምሽት 2 ሰዓት ከ45 ላይ በተፈፀመው ድርጊት ከሞቱት መካከል ሴቶች ፣ ህፃናትና አዛውንቶች ይገኙበታል ።ከተገደሉት ግለሰቦች መካከልም የሰባቱ የቀብር ስነ ስርዓት በደብረ አባይ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስትያን በጋራ ተፈፅሟል ።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስቴር ፅ/ቤት ግድያውን አስነዋሪ የጭካኔ ተግባር ሲል አውግዞታል ፤ ለሟች ቤተሰቦችም መፅናናትን ተመኝቷል:: በቀብር ስነ ስርዓቱ ላይ የተገኙት የአማራ ክልል ርእሰ መስተዳድር አቶ አያሌው ጎበዜም የክልሉ መንግስት የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን በመግለፅ ለሟች ቤተሰቦች መፅናናትን ተመኝተዋል ።
የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን በበኩሉ በግለሰቡ ድርጊት ህይወታቸውን ባጡ ዜጎች ህልፈት የተሰማውን ሀዘን ገልጿል፡፡ በእንዲዚህ አይነቱ ወንጀልም በህብረተሰቡና በፖሊስ መካከል ለዓመታት የቆየው መልካም ግንኙነትም አይሻክርም ብሏል በመግለጫው ፡፡
የፖሊስነት ሙያዊ ዲስፕሊን በጎደላቸው መሰል ፖሊሶችም ይህ አይነት ክስተት ደግም እንዳይፈጠር እንደሚሰራም ያለውን ቁጥርጠኝነት አረጋግጧል ፡፡
ፖሊስ በጉዳዩ ላይ እያደረገ ያለውን ምርመራ እንዳጠናቀቀም ተጨማሪ መረጃ እንደሚሰጥ ነው ያስታወቀው :: አዲስ አበባ፣ ግንቦት 5 (ኤፍ.ቢ.ሲ)
“በባህር ዳር ንጹሃንን የጨፈጨፈው ፖሊስ አማርኛ ተናጋሪ አይደለም”
በባህር ዳር የንጹሃንን ህይወት ያጠፋው የፌደራል ፖሊስ አባል አማርኛ ቋንቋ በደንብ መናገር የማይችል፣ የክልል አንድ ተወላጅ መሆኑንን የአካባቢው ነዋሪዎች ለጎልጉል በላኩት የጽሁፍ መልዕክት ገለጹ። በመልዕክቱ እንደተገለጸው ንጹሃኑን የገደለው ፖሊስ ርምጃውን የወሰደው ወደ ቤቱ በመሄድ መንግስት ያስታጠቀውን የጦር ጠመንጃ በማምጣት ነው።
ከመልዕክቱ ጋር ተያያዥነት ያለው ውይይት ሲያካሂድ የነበው ደብተራ ሊቅ የተባለ የፓልቶክ ክፍልም ተመሳሳይ መረጃ ሲሰጥ ለማዳመጥ ተችሏል። በዚሁ ክፍል ውስጥ ፖሊሱ ራሱን አባይ ወንዝ ውስጥ ወርውሮ አጠፋ መባሉ ሲያከራክር ነበር። በድረገጽ ዜናውን የሚከታተሉ ይሀንኑ መቀበል እንዳቃታቸውና አንድ ሰው ይህንን ያህል ሰው እስኪጨርስና ራሱን ገደል ወርውሮ እስኪጥል “ህግ አስከባሪዎች” የት ነበሩ? ሲሉ ጠይቀዋል። በሌሎች አገሮች እንደሚደረገው ጠቅላይ ሚኒስትሩ አስቸኳይ የሃዘን መግለጫ ለጉዳተኛ ቤተሰቦች አለማድረሳቸውና ወንጀሉን ተከትሎ ሊወሰድ ስለሚችለው የመንግስት አቋም አለመናገራቸው አስገራሚ ሆኗል። ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ዘንድም እስካሁን የተባለ ነገር የለም።
ሦስት የደኅንነት መሥርያ ቤቶችን 180 ሚሊዮን ብር ያለመረጃ አጠፉ
የአገር መከላከያ ሚኒስቴር፣ የመረጃ መረብ ደኅንነት ኤጀንሲና ሌሎች የብሔራዊ ደኅንነት ጉዳይ የሚመለከታቸው መሥርያ ቤቶች የበጀት አፈጻጸምን በጥልቀት ኦዲት ማድረግ የሚቻልበት ሕጋዊ አሠራር እየተጠና ነው፡፡
ባለፈው ሳምንት የ2004 ዓ.ም. የመንግሥት መሥርያ ቤቶች የበጀት አፈጻጸምና የሥራ ክንውን በመመርመር ሪፖርት ያቀረበው የፌደራሉ ዋና ኦዲተር፣ መከላከያ ሚኒስቴር 3.2 ቢሊዮን ብር ለምን ጉዳዮች ወጪ እንዳደረገ ምንም ዓይነት ማስረጃ ማግኘት አለመቻሉን ገልጿል፡፡
የመረጃ መረብ ደኅንነት ኤጀንሲም በምንም ዓይነት መረጃ ያልተደገፈ የ180 ሚሊዮን ብር በ2004 ዓ.ም. ማውጣቱን ሪፖርቱ ይገልጻል፡፡ ሁለቱ መሥርያ ቤቶችና ሌሎች ተመሳሳይ የብሔራዊ ደኅንነት የሚመለከታቸው መሥርያ ቤቶች በተደጋጋሚ የሚወቀሱበትን በማስረጃ ያልተደገፉ በቢሊዮኖች የሚቆጠሩ ወጪዎችን አባክነዋል ማለት እንደማይቻል ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡
ችግሩ የሚመነጨው እነዚህ መሥርያ ቤቶች ኦዲት የመደረግ ግዴታ ያለባቸው መሆኑና ኦዲት በሚደረጉበት ወቅት መረጃዎችን እንዴት ማቅረብ ይኖርባቸዋል በሚሉ ጉዳዮች ላይ ክፍተት በመኖሩ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ ያወጡትን ወጪ በመረጃ በማስደገፍ ለዋና ኦዲተሩ ማቅረብ ማለት የብሔራዊ የደኅንነት ሚስጥሮችን ለሦስተኛ ወገን አሳልፎ መስጠት እንደሆነ የሚያስረዱት ባለሙያዎቹ፣ ይህንን ያገናዘበ አሠራር መኖር እንደሚገባው ያስረዳሉ፡፡
በዚህ የመረጃ ልውውጥ ወቅት ሚስጥሮች ቢባክኑ የሚጠየቅበት ሕግ ባለመኖሩ፣ የደኅንነት መሥርያ ቤቶቹ ኦዲት የመደረግ ግዴታቸውን ቢያንስ መረጃውን በመደበቅ እየተወጡ መሆኑን የሚያብራሩት እነዚሁ ባለሙያዎች፣ ይህንን ችግር መቅረፍ የሚቻልበት ዓለም አቀፍ አሠራርን ያገናዘበ ጥናት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ዋና ኦዲተሩ አቶ ገመቹ ዱቢሶም ይህንኑ ያረጋገጡ ሲሆን፣ የእሳቸው መሥርያ ቤት የሚመራውና ሌሎች አካላትን ያካተተ ኮሚቴ ጥናት እየደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በቀጣዩ ዓመት ጥናቱ ተጠናቆና ረቂቅ ሕጉ ተዘጋጅቶ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንደሚቀርብም አስረድተዋል፡፡ (ዘገባው የሪፖርተር ነው)
ደቡብ ሱዳንና ኢህአዴግ በጋራ ፓርክ መሰረቱ
የጋምቤላ ብሔራዊ ፓርክን ደቡብ ሱዳን ውስጥ ከሚገኘው ቦማ ፓርክ ጋር በማቀናጀት ወጥ በሆነ መንገድ ‹‹ቦማ ጋምቤላ ድንበር ተሻጋሪ ፓርክ›› ለመመሥረት እንቅስቃሴ መጀመሩን፣ የኢትዮጵያ የዱር እንስሳትና ልማት ጥበቃ ባለሥልጣን ማስታወቁን ሪፖርተር አስታወቀ። ሪፖርተር ባይገልጸውም ውሳኔው ስጋት የፈጠረው እንደሆነ ተመልክቷል።
በሁለቱ አገሮች ስምምነት በሚመሠረተው ኩታ ገጠም የጋራ ፓርክ በየዓመቱ ከአንዱ ፓርክ ወደ ሌላኛው ፓርክ የሚደረገውን የዱር እንስሳት ወቅታዊ ፍልሰት ለቱሪስቶች ተደራሽ በማድረግ ጠቀም ያለ ገንዘብ ለማግኘት ታቅዷል፡፡
በጋምቤላ ክልል የነጭ ጆሮ ቆርኪና ናይል ለችዌናን ጨምሮ በርካታ የዱር እንስሳት ይገኛሉ፡፡ በተለይ ከአንድ ሚሊዮን በላይ የሚሆኑት ነጭ ጆሮ ቆርኪዎች እንደየወቅቱ ሁኔታ በአንድ ጊዜ በርካታ ቡድኖችን እየፈጠሩ ወደ ደቡብ ሱዳን ቦማ ፓርክ ይጓዛሉ፡፡ ከቦማ ፓርክም ጊዜ ጠብቀው ወደ ጋምቤላ ብሔራዊ ፓርክ ይመለሳሉ፡፡
በኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ልማትና ጥበቃ ባለሥልጣን ይህ የእንስሳት ፍልሰት እንዳለ ቢታወቅም፣ ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ ጥናት ተሠርቶ ስትራቴጂ ያልወጣለት በመሆኑ፣ የእንስሳቱ ጉዞ በኬንያና በታንዛኒያ መካከል እንደሚገኘው ሰረንጌቲ ፓርክ ለቱሪስቶች ተደራሽ ሳይሆን ቆይቷል፡፡
ባለሥልጣኑ ይህንን ሁኔታ በመቀየር በዘርፉ አንዳች ለውጥ ለማምጣት የሚያስችለውን ጥናት ሌሎች ባለድርሻ አካላትን በማስተባበር እያካሄደ ይገኛል፡፡ የተካሄደው ጥናት ባይጠናቀቅም ፍልሰት መኖሩ በመረጋገጡ እንስሳቱ የሚፈልሱባቸውን ኮሪደሮችና የሚያቋርጧቸውን ወንዞች ለመለየት ለቱሪስት ግልጋሎት የሚሰጡ፣ ሎጆችና የመሳሰሉት መሠረተ ልማቶች እንዲሟሉ ይደረጋል ሲሉ የባለሥልጣኑ የኅብረተሰብ ባለሙያ አቶ ቸሬ ናውጋ ገልጸዋል፡፡
ጋምቤላ ብሔራዊ ፓርክ በ1966 ዓ.ም. ነው የተመሠረተው፡፡ ፓርኩ በአጠቃላይ 5,061 ካሬ ኪሎ ሜትር ስፋት አለው፡፡ ፓርኩ ከአዲስ አበባ 777 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ይገኛል፡፡ የጋምቤላ ብሔራዊ ፓርክ ከሰው ንክኪ ነፃ በመሆኑ በውስጡ ብዛት ያላቸው የዱር እንስሳት ይገኙበታል፡፡
የዱር እንስሳቱ የፍልሰት ሁኔታ ከተጠና በኋላ ፕሮጀክቱ ወዲያውኑ ወደትግበራ እንደሚገባ ተገልጿል፡፡ ከሰረንጌቲ ፓርክ በዓመት 100 ሚሊዮን ዶላር የሚገኝ ሲሆን፣ ከቦማ ጋምቤላ ድንበር ተሻጋሪ ፓርክም ይህን ያህል ገንዘብ የማይገኝበት ምክንያት የለም በሚል የባለሥልጣኑ ማኅበረሰብ በመንቀሳቀስ ላይ ነው፡፡ይህንኑ ፕሮጀክት እውን ለማድረግ ባለሥልጣኑ ከደቡብ ሱዳን አቻው ጋር በመጪው ሐምሌ አዲስ አበባ ላይ ስብሰባ እንደሚቀመጥ ግለጻ የዘገበው ሪፖረተር ነው። ስምምነቱ በአካባቢው ደን ውስጥ ይንቀሳቀሳሉ የሚባሉ ክፍሎችን ለመቆጣጠርና ምናልባትም ወደፊት ፈታኝ ሁኔታ ሊከሰት ይችላል ከሚል ስጋት የተነሳ እንደሆነ ከግምት በላይ የሚናገሩ አሉ።
የፍትህ ሚኒስትሩ መባረር በይፋ መንስዔ በይፋ አልታወቀም
ፎርቹን የተሰኘው የእንግሊዝኛ ጋዜጣ ለንባብ ያበቃው ዜና እንደሚለው አቶ ብርሃን ሃይሉ ከፍትህ ሚኒስትርነታቸው የተባረሩት በብቃት ማነስ ነው። የማስታወቂያ ሚኒስትር ሲፈርስ ወደ ፍትህ ሚኒስትርነት የተሸጋገሩት አቶ ብርሃን ቀደም ሲል ድርጅታቸው ብአዴን ከነበራቸው የፓርቲ ሃላፊነት አንስቷቸው እንደነበር አመልክቷል። ፎርቹንን ጨምሮ የተለያዩ መገናኛዎች የህንን ቢሉም ዋናው የመባረሪያቸው ምክንያት ሚስጥር መደረጉን የሚናገሩ አሉ።

አቶ ብረሃን ግንቦት 1 ቀን 2005 ዓ ም የመስሪያ ቤታቸውን የዘጠኝ ወር የስራ አፈጻጸም ሪፖርት አቅርበው ነበር። ሪፖርትር እንዳለው የተወካዮች ምክር ቤት የህግ ቋሚ ኮሚቴ የሚኒስትሩን ሪፖርት አልወደደላቸው ነበር። ከአቶ መለስ ጀርባ ጥቁር መነጽር በማድረግ በመቀመጣቸው የሚታወቁት የኮሚቴው ሰብሳቢ ከሪፖርቱ በሁዋላ እሳቸው የሚመሩት መስሪያ ቤት መፋዘዙን ነግረዋቸው ነበር።
ሪፖርትር ምንጮቼ ጠቁመውኛል በማለት እንደገለጸው አቶ ብርሃን ሪፖርታቸውን ባቀረቡበት እለት ነው አቶ ሃይለማርያም የ” በቃዎት” ደብዳቤ የላኩላቸው። አቶ ብርሃን በቀጣይ የት እንደሚመደቡ ለጊዜው አልተገለጸም። በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ከታሰሩት ባለስልጣነት ጋር ግንኙነት ይኑራቸው አይኑራቸው እስካሁን የተባለ ነገር የለም።ሚኒስትሩ በአቅም ችግር ከተሾሙበት ጊዜ ጀምሮ ይታሙ ነበር።
አቶ ብርሃን ቀድሞ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት ሃላፊ ከነበሩትና አሁን በኢህአዴግ ጽ/ቤት ውስጥ እንዲቀመጡ ከተደረጉት አቶ ብርሃኑ አዴሎ ጋር የስራ ግንኙነት እንደነበራቸው የሚያውቁ ተናግረዋል። አቶ ብርሃኑ አዴሎ ከሙስና ጋር በተያያዘ በከፍተኛ ደራጃ ክስ የሚቀርብባቸው ባለስልጣን ነበሩ። አቶ ብርሃኑ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት ሃላፊ እያሉ አሁን በቁጥጥር ስር ከዋሉት ባለስልጣናት ጋር የታክስ ቅነሳና የቀረጥ ነጻ ደብዳቤ ለሚታወቁ ባለሃብቶች በመጻፍ የሚታወቁ ባለስልጣን ናቸው። አቶ ብርሃኑ በዶ/ር አሸብር ወ/ጊዮርጊስ ተሸንፈው ከፓርላማ የተወገዱ ብቸኛው የክልል የኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣን ናቸው። በወቅቱ ደ/ር አሸብር በሚያሳትሙት “ቻሌንጅ” ጋዜጣ አቶ ብርሃኑ አዴሎን ገበና በስፋት አጋልጠው እንደነበር አይዘነጋም። ዶክተሩ አሁን ብቸኛ የግል ተወዳዳሪ የፓርላማ አባል ቢሆኑም በተደጋጋሚ ኢህአዴግን እንደሚደግፉ በመግለጽ ይታወቃሉ።
Leave a Reply