• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ምኒልክን ከዓድዋ ለመነጠል መሞከር ባርነት መምረጥ ነው

March 4, 2022 12:18 am by Editor Leave a Comment

ጀግንነቱን ዓለም መስክሮለታል፣ ስሙን ከፍ አድርጎ ጠርቶታል፣ ታሪክ በማይጠፋ ቀለም፣ በማያረጅ ብራና አስፍሮታል፡፡ ጠላት ሮጦለታል፣ በስሙ ተሸብሮለታል፣ ከእግሩ ሥር ወድቆ ይማሩኝ ንጉሥ ኾይ ብሎለታል፡፡ በጀግንነቱ በጠላቶቹ ልብ ላይ የነገሠ፣ በዝናው ዓለምን ያዳረሰ፣ የጠላቶቹን አንጀት የበጠሰ፣ የወዳጆቹን አንጀት ያራሰ ጀግና ነው እርሱ፡፡

የማይገመት ልብ ያለው፣ ጠላት የማይችለው፣ ጀግንነት፣ ብልሃት፣ አሸናፊነትና ጽናት የታደለው ኃያል ንጉሥ፡፡

ነጭ ባየለበት ዘመን በነጭ ላይ የገነነ፣ የነጭን ኃያልነት የበጣጠሰ፣ የነጭን አብዮት ያፈራረሰ፣ የጥቁርን ክብር የመለሰ፣ ያለቀሱትን እንባቸውን ያበሰ፣ በጨለማ ውስጥ ለነበሩት የደረሰ፣ በድል ብቻ የገሰገሰ፣ በጨለማው ምድር ብርሃን ያበራ፣ ከተራራ የገዘፈ፣ ዘመናትን በክብር ያለፈ ታሪክ የሠራ፣ የጥቁር አባት፣ የነጻነት መሪ፣ የጨለማ ዘመን አሻጋሪ፣ የአሸናፊነትን ድል አብሳሪ ነው ኃያሉ ንጉሥ፡፡

በደል ያልተገኘባቸው የአፍሪካ ሀገራት በበደለኞች እጅ ወድቀው ነበር፡፡ ቀኝ ገዢዎች በእርስታቸው በተቀመጡት ደጋግ ሕዝቦች ላይ ተነስተው የግፍ ግፍ ይፈጽማሉ፡፡ ሰዎችን እንደ ሸቀጥ ይሸጣሉ፣ ይለውጣሉ፡፡ እያሰሩ አያሌ በደሎችን ይፈጽማሉ፡፡ ባለ እርስት የሆኑት ጥቁሮች በባዕዳን መከራው ጠንቶባቸዋል፡፡ በበደለኞች ተገፉ፣ ተዳፉ፡፡ አፍሪካን የመከራና የስቃይ ምድር አድርገው ኃያልነታቸውን ማስፋት ፈለጉ፡፡ ኃያል ያደርገናል ያሉትን ሁሉ በአፍሪካ ምድር ላይ ፈፀሙ፡፡ ብዙዎችን ያለ በደላቸው በቀያቸውና በእርስታቸው በግፍ ገደሉ፡፡

አፍሪካን የደም ምድር አደረጓት፣ ብርሃኗን ነጥቀው በጨለማ ውስጥ እንድትኖር ፈረዱባት፣ ማንነቷን ወስደው የማይመስላትን ማንነት ልበሽ አሏት፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ታዲያ ጨለማ ያልደረሰባት፣ የባዕድ ማንነት ያልነካካት፣ ጨለማ የማይደፍራት፣ ብርሃን የከበባት፣ ጀግና ልጆች ያሏት፣ ደፋር ኩሩ ንጉሥ የነገሠባት ምድር ነበረች፡፡ በጨለማው መካከል ብርሃን ያበራች፣ በጠላት ያልተደፈረች፣ በደምና በአጥንት የተጠበቀች፣ ጀግና ልጆችን የወለደች ወልዳም ያሳደገች ምድረ ቀደምት ሀገር ናት፡፡

ጠላቶች እንደሌሎቹ ሁሉ ሊያጠፏት፣ ክብሯንና ማንነቷን ሊነጥቋት ወደ እርሷ ወሰንም ዘለቁ፡፡ እነዚያ የሮም መሪዎች ነጻ የሆነችው ሀገር ነጻነቷን ሊነጥቋት ቋመጡ፡፡ በሌሎች ሀገራት ድል ለምደዋልና በኢትዮጵያ ሰማይ ሥርም በድል እንደሚንበሸበሹ ተማምነዋል፡፡ ዳሩ ኢትዮጵያ ከሁሉም ትለያለች፣ ለአሸናፊነት የተፈጠረች እንጂ መሸነፍ በፍጹም አይነካካትም፡፡

በጦር ወግቶ ማሸነፍ ለእርሷ ብቻ የተፈጠረ እስኪመስል ድረስ በየዘመናቱ የተነሱትን ጠላቶቿን እየወጋች ድባቅ እየመታች ኖራለችና ማንም ቢነሳ አትበገርም፡፡ የጠላትን ፉከራና ድንፋታ አስቀድማ ሰምታ ነበር፡፡ ንጉሡ ምኒልክም የሀገሬው ሕዝብ ለዘመቻ እንዲነሳ በማርያም ምሎ አዋጅ አስነገረ፡፡ እንኳን በአዋጅ ተጠርቶ እንዲያውም ለሀገሩ መዝመት የሚወደው የሀገሬው ሰው የንጉሡን ቃል ከያለበት ሰምቶ ተንቀሳቀሰ፡፡

የሮም ሠራዊት በአፍሪካ ምድር የምታበራዋን ብኛዋን መብራት አጥፍቶ፣ አፍሪካን በድቅድቅ ጨለማ ሲያስውጣት ለማዬት የጓጉ የኢጣልያ ወዳጆች የድሉን ዜና ለማስማት ቸኮሉ፡፡

ድል ፈጽማ ከኢጣልያ ሠራዊት እንደማትርቅ ተማምነዋል፡፡ ጥያቄው ድሉ የሚበሰረው መቼ ነው የሚለው ነው፡፡ አይደርስ የለም ያ ቀን ደረሰ፡፡ ኢትዮጵያውያን ሳይደርሱባቸው አይደርሱም እንጂ ከደረሱባቸው አመላለሱን ያውቁበታል፡፡

አውግስቶስ ቄሳር በሮም ነግሦ በነበረበት በዚያ ዘመን ሮም ቁጥራቸው የበዙ የዓለም ሀገራትን አስገብራ ነበር፡፡ ይህም ንጉሥ ተከብራ እንጂ ተደፍራ የማታውቀውን ሀገር ኢትዮጵያን ለመውረር አይሎስ ጋሎስ በሚባል የጦር አበጋዙ የሚመራ ሠራዊት ወደ ኢትዮጵያ ምድር ላከ፡፡ ያም ዘመን ከክርስቶስ ልደት አስቀድሞ በ29 ዓ.ዓ እንደበር ይነገራል፡፡ በዚያ ዘመን ኃያል የነበረው የኢትዮጵያ መንግሥት ፈጽሞ ለጠላት የሚቀመስ አልነበረም፡፡ የአይሎስ ጋሎስ ሠራዊትም ከንጉሡ በታዘዘው መሠረት የኢትዮጵያን ወሰን ለመድፈር ጦርነት ከፈተ፡፡ ኢትዮጵያውያን ጀግኖች ሀገር ሊወር የመጣውን ጠላት ነዲድ እሳት ሆነው ጠበቁት፣ እንደ አመጣጡ እየለበለቡ አቃጠሉት፡፡

አውግስቶስ ቄሳር ያሰበው ሳይሳካ ሠራዊቱን አስጨረሰ፡፡ ከኢትዮጵያውያን ጦርና ጎራዴ የተረፈውን ሠራዊት ይዞ እንዲመለስ ለአይሎስ ጋሎስ ትዕዛዝ አስተላለፈ፡፡

ከኢትዮጵያውያን ጎራዴ የተረፈው ሠራዊትም ብዙዎችን በጎራዴ አስበልቶ፣ በሳንጃ አስወግቶ፣ በበረሃ ትቶ በሐዘን ወደሀገሩ ተመለሰ፡፡

በአውግስቶስ ቄሳር ዘመን የደረሰባቸውን ሽንፈት ያካክሱ ዘንድ ከክርስቶስ ልደት በኋላ በ54 ዓ.ም ወደ ኢትዮጵያ ሌላ ወራሪ ሠራዊት ላኩ፡፡ በዚያም ዘመን የነገሰው ኔሮ ነበር፡፡ እርሱም ኢትዮጵያን አስገብራታለሁ ሲል ፎክሮ ተነሳ፡፡ አማካሪዎቹ ኢትዮጵያውያንን ማስገበር ፈጽሞ እንደማይቻል አስቀድመው ነገሩት፡፡ እርሱ ግን አሻፈረኝ አለ፡፡ መጣም ተሸንፎ ተመለሰ፡፡

ከአባቶቻቸው የወረሱትን የዘር ሽንፈት ልጆቹ ሊደግሙ በዘመነ ምኒልክ ኢትዮጵያን ሊወሩ ገሰገሱ፡፡ ምኒልክም ሠራዊቱን አስከትሎ፣ ጀግኖቹን የጦር አበጋዞችን ይዞ፣ ከብርሃን ዘ ኢትዮጵያ እቴጌ ጣይቱ ጋር ጠላት ወዳለበት ገሰገሰ፡፡ በዚያም ጠላትን ድባቅ መታው፡፡ ከዘር የመጣው የኢጣልያ ሽንፍትም በዓድዋ ከፍ ብሎ ተሰማ፡፡ ኢጣልያ አፈረች፣ ኮሰመነች፣ የአፍሪካን ብቸኛ ብርሃን ልታጠፋ ስትቋምጥ የራሷን ብርሃን አጠፋች፣ በዓለም ፊት ተዋረደች፣ ምኒልክ ኃያላን ነን በሚሉት ሁሉ ተፈራ፤ ተከበረ፡፡

በአንድ ጀንበር ዓድዋ ላይ የዓለም ታሪክ ተቀየረ፡፡ አፍሪካ መውጫ ብርሃኗን ከወደ ኢትዮጵያ አየች፡፡ በዚያ መንገድም ለመጓዝ ተነሳች፡፡ ታላቁ ንጉሥ በዓድዋ ተራራ ላይ ጠላትን እንዳልነበር አደረገ፡፡

የኢጣልያ ሠራዊት አብዛኛው በኢትዮጵያውያን ጎራዴ ተበልቶ ላይመለስ አሸለበ፡፡ የቀረው እጁን ሰጠ፡፡ ጥቂቱም ፈርጥጦ አመለጠ፡፡ ጀግና አስታወይና ብልህ ነውና ምኒልክ የኢጣልያ ምርኮኞች በሰላም እንዲኖሩ አደረገ፡፡

ኒኮላስ ኒዎንቲቭን ጠቅሰው ጳውሎስ ኞኞ ሲጽፉ ʺ ንጉሡ ድል ማድረጋቸውን እንዳወቁ እጅ የሰጡትን ጣልያኖች ሠራዊታቸው እንዳይገድል አስጠነቀቁ፡፡ እንስራ ተሸክመው ለሠራዊቱ ውኃ ያቀብሉ የነበሩ የኢትዮጵያ ሴቶች ሁሉ ሸክማቸውን እያስቀመጡ ምርኮኞቹን በማገዝ ይረዱ ጀመር፡፡ አስክሬኖች በብዛት ተከምረዋል፡፡ በሜዳው ላይ በትንሹ ይወርድ የነበረው ደም ወደ ወንዝነት ተለውጧል” ብለዋል፡፡

ምኒልክ በጠላቶቹ ላይ አይጨክንም፡፡ መሸነፋቸውን አውቀው እጅ ከሰጡ ይንከባከባቸዋል እንጂ፡፡ ጀግና እጁን በሰው ክብር ላይ የሚዘረጋውን ይቀጣል እንጂ እጅ የሚነሳውን አይቀጣም ምኒልክም ጀግና ነውና ጠላት ስለሆኑ ብቻ ይገደሉ አላለም፡፡ ለምርኮኞች እንክብካቤ እንዲደረግ አዘዘ እንጂ፡፡

ʺበዚያ ጊዜ ምኒልክ አንድ መጠለያ አቋቁመው ስለነበር ልብስ፣ ምግብና ውኃ ይሰጣል፡፡ ለቁስለኞችም የሕክምና እርዳታ ይደረግ ነበር፡፡ የቆሰሉት ምርኮኞች የሚጓዙበት ተሰጥቷቸዋል” ሲሉ ጳውሎስ ግሊከንን ዋቢ አድርገው ጽፈዋል፡፡ ምኒልክ ጀግና ብቻ ሳይሆኑ ሩህሩህም ናቸው፤ ቆፍጣና እንጂ ጨካኝ አይደሉም፡፡

“እርር ቅጥል ቢሉም የእርሱ ጠላቶቹ፣
ምኒልክ ጀግና ነው እስከ ዘመዶቹ”

ባሕር ዳር: የካቲት 24/2014 ዓ.ም (አሚኮ)

Print Friendly, PDF & Email

60

SHARES
Share on Facebook
Tweet
Follow us
Share
Share
Share
Share
Share

Filed Under: Left Column, Opinions Tagged With: 126 adaw, adwa, emiye menelik, menelik

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • በጦርነቱ የተጎዱ አካባቢዎችን ለማቋቋም የሚውል የ15 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ድጋፍ የዓለም ባንክ May 16, 2022 10:22 am
  • በአዲስ አበባ 1 ሺህ 98 የብሬን እና 2 ሺህ 162 የክላሽ ጥይት ተያዘ May 16, 2022 10:10 am
  • በአዲስ አበባ ከተማ በግለሰብ መኖሪያ ቤት ከ5 ሺህ በላይ የአሜሪካ ዶላርና የተለያዩ አገራት ገንዘቦች ተያዙ May 16, 2022 09:53 am
  • አገር አፍራሹ ትህነግ ለቀለብ፣ መድኃኒትና ሥራ ማስኬጃ 76 ቢሊዮን ብር ቀርጥፏል May 16, 2022 08:30 am
  • እየተባባሰ ከመጣው የማህበራዊ ሚዲያ አጭበርባሪዎች ዜጎች ራሳቸውን እንዲጠብቁ ተጠየቀ May 15, 2022 09:38 am
  • የትህነግና ሸኔ መሠልጠኛ የምትባለው ዩጋንዳ መከላከያ ሚ/ር ከኤታማዦር ሹሙ ጋር ተወያዩ May 13, 2022 09:55 am
  • በትግራይ የውጊያ ምልመላው ጉዳይ May 11, 2022 02:37 am
  • መከላከያ በተጨማሪ ድሮን፣ በሥልጠና፣ በዝግጅት ራሱን አብቅቷል May 11, 2022 01:35 am
  • ትህነግ ለሌላ ውጊያ እየተዘጋጀ ነው ተባለ May 10, 2022 01:04 pm
  • ኤርትራ 8 ሩስያ ሠራሽ ድሮኖችን ተረክባለች May 10, 2022 12:37 am
  • ሙስሊምና ክርስቲያን በአንድነት የሚያከብረው የአኾላሌ ባሕላዊ ጭፈራ May 9, 2022 01:46 pm
  • በወልዲያ ፋኖዎች ተመረቁ May 9, 2022 12:51 pm
  • “ሠራዊታችን ድልን በአስተማማኝ መልኩ ማምጣት በሚችል ቁመና ላይ” ጀኔራል ጌታቸው May 9, 2022 11:57 am
  • ዋጋው 64 ሚሊዮን ብር የሚሆን (16 ኪሎ) ሕገወጥ ወርቅ ተያዘ May 9, 2022 11:51 am
  • አብን ክርስቲያን ታደለን ለመጨረሻ ጊዜ አስጠነቀቀ፤ 10 አባላቱን አገደ May 9, 2022 08:58 am
  • ራሱ አቡክቶ፣ ራሱ አሟሽሾ፣ ራሱ ጋግሮ በሰዓት 460 እንጀራ የሚያወጣ ፈጠራ May 9, 2022 08:17 am
  • በህገ ወጥ መንገድ 19 ህጻናትን ሲያዘዋወሩ የነበሩ 6 ሴቶች ተያዙ May 8, 2022 12:39 am
  • በአርሲ ሙስሊሞች ለቤ/ክ ማሠሪያ 3 ሚሊዮን ብርና 20 የቀንድ ከብት ሰጡ May 6, 2022 09:35 am
  • በአዲስ አበባ የሚኖረው የትህነግ ደጋፊ ማንነት በማስረጃ May 4, 2022 11:04 pm
  • ሙስሊም ወንድማማች የቤ/ክ ዘራፊዎችን በቁጥጥር ሥር አዋሉ May 4, 2022 09:04 am
  • ከ6 ሺህ የዓሳ ጫጩት ወደ 80 ሺህ May 4, 2022 08:57 am
  • ተስፋቢሱ ቴድሮስ May 3, 2022 12:16 pm
  • ከሽፏል! April 6, 2022 11:58 am
  • “ሩሲያ ዩክሬይንን ወረረች” እየተባለ ስለሚነዛው ወሬ ጥቂት እውነታዎች March 8, 2022 11:30 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2022 · Goolgule