
እንደ መግቢያ
ይህን ጽሁፍ ለመጻፍ ያነሳሳኝ ስለዶ/ር አብይ ያለኝ የጠለቀ እውቀት ወይም ከነበሩበትና ከተነሱበት ፓርቲና ፓርቲው ከሚያራምደው የፖለቲካ አመለካከት ጋር ያለኝ ጠብ ወይም ዝምድና አይደለም። ይልቁንም እንደ አንድሀገር-ወዳድ ኢትዮጵያዊ ባለው የህወሃት የበላይነትን የተከተለ ፍጹም ዘረኛ ጉዞ ሄደን ሄደን የደረስንበት ደረጃ በጣም አሳሳቢ መሆኑን በመመልከት ነው።
በዘረኛው የወያኔ ከሩብ ምእተ አመት የዘለለ የጥፋት ጉዞ ውስጥ ከተጓዙና ከጉያቸው የበቀሉ ዘረኛው ስርአት ከሚያራምደው የተለየና የተሻለ ራእይ ያለው ጉዞን የመረጠ የኦሮሞ፣ የአማራ እንዲሁም የመላው ኢትዮጵያ ወጣቶች በደምና በህይወት ጭምር ዋጋ የከፈሉበትን ትግል ባዳመጠ መልኩ የተቃኘ ‘ቲም ለማ’ ከተባለ የለውጥ አራማጆች ውስጥ የበቀሉት የዶ/ር አብይ ራእይ ምን ቢሆን ለሐገር የሚበጅ መድህን ይሆናል የሚለውን ለማየት የአዲሱን ጠቅላይ ሚስተር ራእይ ከተጨባጭና ከሐሳብ ወለድ መንደርደሪያ በመነሳት ጠቃሚ ያልኩዋቸውን ምልከታዎች በማጣመር ለመመልከት እሞክራለሁ።
የዶ/ር አብይ አህመድ ራእይ እንደማእከላዊ ነጥብ የዶ/ር አብይ ራእይ በማለት መጪውን የሀገሪቱን እጣ ፈንታ ለመመልከት በአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስቴር ውስጥ ቲም ለማን አካቶ ማየትንና የኒሁ ወጣት የለውጥ አራማጅ መሪን ጉዞ እሳቸውና ቡድናቸው ለወጣት ኢትዮጵያውያን በፈነጠቁት ተስፋና ባሳዩት የኢትዮጵያዊነት ስሜት ላይ በተመሰረተ አላማ ዙሪያ መመልከቱ አዲሱን ጠቅላይ ሚኒስቴር በወያኔ ዘመን ከተለመደውና በአንድ ጎሳ ጥቅም ዙሪያ ላይ አነጣጥሮ ከተመሰረተው ፓርቲያቸው (ኦሕዲድ) አላማ በሰፋ መልኩ የኦሮሞና የሌላው ኢትዮጵያዊ አንድነት በማይናወጥ መሰረት ባለው አመላካከታቸው በኢትዮጵያ መፈራረስ የሚምለው ህወሃት የጥፋት ጉዞን በፍርሐት ቆፈን ሳይሆን በተረጋጋ አስትዋይ ኢትዮጵያዊ አእምሮ መመልከታችውን በግልጽ በማሳየታችው ይህንን ራእይ ዘመኑ በፈጠረብን መጠራጥር ውስጥም እንኩዋን ተስፋን ልንቸረው ይገባል ባይ ነኝ።
የአብይን ራእይ በሐይለማሪያም ራእይ (እሱም ከነበረ) ለማወዳደር ባልዳዳም ጠቅላይ ሚኒስትርነት በኢትዮጵያ ምን ያህል የተዋረደና ተራ የአዛውንት ወያኔዎች ተላላኪ ከመሆን የዘለለ ወሳኝ ከፍተኛ የስልጣን ደረጃ መሆኑን ለመመልከት ያለንን ጉጉትና ፍላጎት ከፍ ማድረጉን ግን በንጽጽር መግለጹ ጥሩ ማሳያ ነው የሚል ስሜት አለኝ።
እነዶ/ር አብይ በብዙ ኢትዮጵያን ያተረፉት ቅቡልነት ‘ከሀምሳ ዘመን በላይ ዘርና ዘርን ብቻ ያቀነቀኑ የብሔር ፖለቲከኞት ለምን አላገኙትም?’ ብለን ብንል መልሱ ለኢትዮጵያዊነት የሰጡት ክብርና ስለሓገር አንድነት የተናገሩት መሳጭ ንግግሮቻቸው ለመሆኑ ብዙ አስረጂ የሚጠይቅ ጉዳይ አይመስለኝም።
ስርነቀል ወይስ የጥገና ለውጥ?
በኢትዮጵያ ለውጥ መደረግ የነበረበት የህወሀት የጥፋት መርዝ ስር ሳይሰድ በመጀመሪያወቹ ሁለትና ሶስት አመት የወያኔ የስልጣን ዘመን መሆን እንደነበረበት ቢሰማኝም አሁንም የቆሰለው አውሬ ሳያገግም በተጋጋለው የወጣቶች ትግል ታጅቦ መቀጠሉ የዚህን አዲስ ጠቅላይ ሚኒስትር ራእይ የሁላችን የጋራ ራእይ የማድረግ አቅም በመስጠት ጉልህ ድርሻ ይኖረዋል። አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስቴር በብዙ ምክኛቶች ወደሑዋላ ልመልከት ቢሉ እንኳን እንደሎጥ ሚስት እንደጨው አድርቆ የሚያስቀራቸው ይሆናል።
እነዶ/ር አብይ ሚና በለውጥ ሚዛን ሲታይ የጥገና ለውጥ አራማጅ (reformist) ሚናው ጎላ ይላል። ይህ የለውጥ አይነት ብዙዎቻችን ከወያኔ እኩይ ተልእኮ ልምድ በመነሳት የማንቀበለው ቢሆንም በአንጻሩ ከወያኔ ሀገሪቱ የተሰራችበትን ድርና ማግ የመበታተን የሩብ ምእተ አመት እኩይ ስራ በኋላ የሐገሪቱን የፓለቲካ አቅጣጫ በቀላሉ ወደ አዲስ ስርነቀል የለውጥ መንገድ መዘወር የራሱ የሆኑ ተፈጥሮአዊ አደጋውም የከፋ ውጤት ሊያመጣ መቻሉን ማሰተዋል የግድ ይላል። ይህንንም ሂደት የወጣቱ የትግሉ ወላፈን ለኣፍታም እንኳን ሳይቋረጥ ይህንን መሰረታዊ ሊባል የሚችል ግን የጥገና ለውጥ በጥሩ ተስፋና ቅቡልነት መመልክቱ ተገቢ መስሎ ይሰማኛል።
በመጨረሻም ለስር ነቀል ለውጥ ብንጓጓም እንኳን በምድር ላይ ያለው ተጨባጭ ሁኔታ የስርነቀል ለውጥ አራማጅ ተቃዋሚ ፓርቲዎች አደረጃጀት የደረሰበት የእድገት ደረጃ እምብዛም የበሰለ ተስፋ ፈንጣቂ አለመሆኑን መመልከታችን ወደቲም ለማ ለማሸብረክና ሐገርን ከጥፋት ለመታደግ የመጣ ቅርብ እድል መሆኑን በማሰብ በተስፋ እንድንመለከተው ያደርገናል።
እንደማጠቃለያ
ይህንን አጭር ጽሁፍ ስሞነጫጭር ዶ/ር አብይ ቃለመሐላ አድርገው የተናገሩትን የመጀመሪያ ጠቅላይ ሚኒስትራዊ ንግግራቸውን ደጋግሜ አዳመጥኩ። ፓርቲያቸውን ኢህአዴግን ሲያመሰግኑ ለወያኔ ባለሐብቶችም በህዝብ አመጽ እንዳይዘረፉ ዋስትና ሲሰጡ ባዳምጥም ከለውጣቸው እስትራተጂነት ወይንም ከመሳሰሉ ቀጣይ ቅን መሰል ጉዞዎች በዘለለ መሰሪ ወይንም ግልብጥብጥ ያለ ሐይለማርያማዊ ስነምግባር የጎደለው ተላላኪነት አይመስልም። ከግል የቤተሰባቸው ትርክት፣ ከቀደም የኢትዮጵያ ታሪክ፣ ከዘረኝነት ጥላቻም ሆነ ለወደቁ ወጣት የለውጥ ተፋላሚዎች ይቅርታ አጠያየቅ ስመለከት በጣም ተመሰጥክ አትበሉኝና ይህ ነው የምለው እንከን አላገኝሁባቸውም።
ይልቁንም በቃላቶቻቸው ለቤተመንግስቱ ርቆ የነበረውን የከበረ ኢትዮጵያዊነት መንፈስ በድፍረት በመናገራቸው ቤተመንግስቱን የተጥናወተው ተጻራሪ ኢትዮጵያዊ መንፈስ እንዳይተናኮላቸው ሰጋሁ፥፥
እግዚአብሔር አኢትዮጵያን ይጠብቅ አሜን!
ከበቀለ ደገፋ (t.mesafint@gmail.com)
ሚያዝያ 2010 ዓ.ም.
“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ። ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ™ አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው።
Leave a Reply