• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

በመጨረሻም በግብጽ ነጻ ወጡ . . .

May 9, 2015 06:25 am by Editor Leave a Comment

* ሕንጻና መንገድንማ ቅኝ ገዥዎችም ሰርተዋል

የፌስቡክ አርበኛው ቴድሮስ አድሃኖም ቦሌ ሄደው ከሊብያ ነጻ የወጡ ዜጎችን ሲቀበሉ አየን።  እፊታቸው ላይ የማፈር ሳይሆን የጀግንነት ስሜት ይነበባል። አቀባበላቸውም 90 ደቂቃ በእንቴቤ የሚለውን ታሪክ ይመስላል። ኡጋንዳ ላይ የታገቱ ዜጎችዋን ለማስለቀቅ እስራኤል ያደረገችው ገድል። ቴድሮስ አድሃኖምም በኩራት እና በድል አድራጊነት ስሜት ነው ስደተኞቹን የተቀበሉት። መቼም ሼም የሚባል ነገር ከነሱ ዘንድ ጠፍቷል። በስራቸው ማፈር ሲገባቸው አይናቸውን በጨው እያጠቡ የሌላውን ድል እንደራስ ያጣጥሙታል። ህሊና  ያለው ሰው ያሳደዳቸውን እና በባእድ ነጻ የወጡ ዜጎቹን ሲመለከት ብርክ ነው የሚይዘው። አልገባቸው ይሆናል  እንጂ ክብራቸውን የሚቀንስ ማንነታቸውን የሚፈትን ድርጊት ነው። አስቀድመን በግብጽ መገናኛ ብዙሃን ዜናውን ባንሰማ ኖሮ ደግሞ ሌላ ታሪክ ይነግሩን  እንደነበር ጥርጥር የለውም።

ሁኔታቸው አባት እና እናቱን በግፍ ገድሎ ፍርድ ቤት የቀረበውን አይነደረቅ ያስታውሰናል።  ወንጀል መፈጸሙን ያመነው ይህ ጎረምሳ የፍርድ ማቅለያ እንዲናገር በመሃል ዳኛው በተጠየቀ ግዜ እንዲህ አለ። “ያው አባት እና እናት ስለሌለኝ፤ ለወላጅ አልባ ልጆች እንደሚደረገው ልዩ እንክብካቤ ያስፈልገኛል።”

በአለም-ዓቀፍ መገናኛ ብዙሃን እንደሰማነው እነዚህን ዜጎች ነጻ ያወጣችው ግብጽ ናት። ከአይሲስ ጥርስ ወጥተው ግብጽ ምድርን ሲረግጡ አቀባበል የተደረገላቸው በሚኒስትር ደረጃ ሳይሆን በርዕሰብሄር ደረጃ ነው።  ከአውሮፕላን ሲውርዱም የግብጽን ባንዲራ እያውለበለቡ ነበር። አዲስ አበባ ላይ ግን ባንዲራ አልያዙም።  ይህም ትልቅ ትርጉም አለው።  ባንዲራ የአገር ክብርና ፍቅር ነው።  የህዝብ አንድነት እና ትሰስር በባንዲራ ይገለጻል። አንገት ላለው፤ አንገቱን የሚያስደፋ እውነታ!

በግብጽ መከላከያ ሃይል ነጻ የወጡት እነዚህ 27 ኢትዮጵያውያን ካይሮ ሲደርሱ የግብጹ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ አል ሲሲ ፕሬዝዳንታዊ  አቀባበል አድርገውላቸዋል። ቅድምያ ለሰብአዊ  ፍጡር  ክብርን ከመስጠት የሚመነጭ ተግባር ነው። ትልቅ የፖለቲካ ትርፍ ቢያገኙበትም ይገባቸዋል። ክቡር የሆነን ሰው ነብስ አትርፈዋልና ይህ ለኛ ትልቅ ትርጉም ነው የሚሰጠን። መልካም ስራ ለክፉ ቀን ስንቅ ነው።

አዲስ አበባ ሲገቡ ግን ሃይለማርያም ደሳለኝ ሊቀበሏቸው አልቻሉም። ምክንያቱም ግልጽ ነው። ለሳቸው ያለገደብ የተሰጠው ስልጣን  ተቃዋሚዎችን እና ዲያስፖራውን መሳደብ ብቻ ነው። ምናልባትም ለኚህ አሻንጉሊት ዋነኛው ችግር አይሲስ ሳይሆን አሜሪካ ላይ የተነሳው አልሻባብ ነው። አሜሪካ ባሸተተች የኛዎቹ ያስነጥሳቸዋል። ለዚህ የአሜሪካ ቆሻሻ ጦርነት የኢትዮጵያን ወታደር ለመላክ አላንገራገሩም። የኛ ወገን እንደ ከብት ሲታረድ ግን የመረጡት ብሄራዊ የሃዘን ቀን ማወጅ፣ ከንፈር መምጠጥ፤ ሻማና ጧፍ ማቃጠል …።

ምክንያቱ እነሱ እንደሚሉት የድንበር መዋሰን ጉዳይ አይደለም። ይህ ቢሆን አሜሪካ ሽብርተናን ለመውጋት አፍጋኒስታን ወይንም ሶርያ አያዋስናትም። መውረር ባስፈለጋት ግዜ ፓናማንም ግሪናዳንም ወርራለች። ሶማልያ ላይ ከሰፈረው ሰራዊት ስንቱ እንደሞተ በፓርላማ  ሲጠየቁ የቀድሞው ጠቅላይ ሚንስትር ሲመልሱ፤ “ይህ ጉዳይ እናንተን አይመለከትም!” ነበር ያሉት። የፓርላማ አባላት ይህንን ወሳኝ ጉዳይ የማወቅ መብት ከሌላቸው ታዲያ ለማን ነበር ሪፖርቱ የሚቀርበው? ለአሜሪካ?

አለም ስለ አይሲስ ጭፍጨፋ ሲጨነቅ፣  እነሱ ግን ምርጫው ነው እንቅልፍ የነሳቸው። እናም በዜጋው ሰቆቃ ሳይሆን በሰላማያዊ ፓርቲ  ላይ ተጠምደዋል። አይሲስን ከመዋጋት ሰማያዊ ፓርቲን ማጥፋት ይመርጣሉ። የመከላከያ ሰራዊቱ አንበሳነት በሃገር ውስጥ ብቻ መሆኑን አስመስክሯል። በዜጋው ላይ ኮማንዶ ሲለማመድ አሳዩን።

ለእነሱ  ሽብርተንኛ አይሲስ ሳይሆን ጋዜጠኛ ነው። የጸረ-ሽብር አዋጅ አውጥተው ጋዜጠኛ እና ተቃዋሚዎችችን ያፍኑበታል። ሽብርተኛው ዜጋዋ ሳይሆን አይሲስ እንደሆነ ግብጽ ትምህርት የሰጠቻቸው ይመስላል። ከራስዋም አልፋ እኛኑ ስትታደግ አየን።

በዚህ ሰሞን የቴድሮስ አድሃኖም ፌስ ቡክ ገጽ ተጨናንቆ ነው የሰነበተው። የስደት ቀውሱ ያመጣውን ችግር ይዞ ትንሽ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት የሚደረግ ጥረት መሆኑ ነው።  የኝህ ሰው ስራ ጨርሶውኑ በፌስ ቡክ ላይ ሆኗል ያስብላል። ጨጓራው የተቃጠለ ዜጋም ይህንኑ ገጽ የንዴቱ ማብረጃ አድርጎታል።

በሳምንቱ መጀመርያ ላይ አይቴ ቴድሮስ እንዲህ ብለው ጽፈዋል። “የመጀመሪያ ዙር ከሊብያ ተመላሽ ወገኖች አዲስ አበባ ገብተዋል። መንግስት ጥረቱን አጠናክሮ ይቀጥላል።”

ታዲያ ሚኒስትሩ እንዲህ ይበሉ እንጂ እነዚህ ወገኖች ሲገቡም ሆነ አቀባበል ሲደረግላቸውም አልታየም። እውነት ነው በኢትዮጵያዊነታቸው ሳይሆን በዘር እየተለኩ፣ ለገዢው ፓርቲ ቅርብ የሆኑ፣ ወዘተ በሱዳን በኩል እንዲገቡ መደረጉ ተሰምቷል።

ተስፋዬ ሁሴን የተባለ ወገን በዚያው ጽሁፍ ስር እንዲህ ሲል መለሰላቸው፣ “መቸስ ውሸትህ አያልቅ፣ በቀደም እለት የደቡብ አፍርካ ተመላሾች ብለህ ቀደድክ። ነገር ግን እዚህ ከደቡብ አፍርካ የገባ አንድም ስደተኛ ባልነበረበት፣ ተመላሾች ብለህ ስትዋሸን ዝም አልን። አሁን ደግሞ ከሊቢያ … መጥኔ ውሸትህን ለሚጋቱ አድርባዮች! ጊዜ እየጠበቅህ ብቻ የእንትን ተመላሾች በል። ነገ ደግሞ የሰማይ ቤት ተመላሾች እንደምትለን ተስፋ አደርጋለው። በውሸት፣ በፌዝ 24 ዓመት…”

ቴድሮስ አድሃኖም መጻፋቸውን ቀጠሉ፣ ስለ ሁለተኛው ዙር ተመላሾች። ዙቤር ኡስማን የተባለ መላሽ ደግሞ  “አገር የሌለው ሰው የሄደበት ሁሉ አገሩ ነው! ኢትዮዽያውያን ስደተኞች ከሊቢያ ወደ ግብፅ፤ የግብፅን ሰንደቅ ኣላማ እያውለበለቡ ሲወርዱ! ከሃበሻ ምድር ተሸርፋ “አገር” የሆነችው ግብፅ ዛሬ የእንጀራ እናታችን ሆነች!” ሲል ነበር ቁጭቱን የገለጸው።

እርግጥ ነው። ስልጣን ላይ ያለው ቡድን ለዜጋው ግድ አይሰጠውም። አንድ ኢትዮጵያዊ ይልቅ አንድ የህንድ ወይንም የሳዑዲ ዜጋ በሃገራችን ትልቅ ክብር አለው።  ከዜጋው ይልቅ ለባእዳን “ባለሃብቶች” ደህንነት የሚጨነቅ ስርዓት ነው። ሲጀመር ዜጋው ከሀገሩ እንዲሰደድ ያደረገው ብልሹ የሆነ ስርአቱ ነው። አርሶ አደሩችን ከቀያቸው እያፈናቀለ፣ ለም መሬታቸውን ለህንድ እና ሳዑዲ ባለሃብቶች በመናኛ ዋጋ በመቸበችብ የወጣቱን ተስፋ ገደለው። ወጣቱ አገር የለውም።  ለመኖር ሲል፣ ፍትህ ፍለጋ፣ ስራ ፍለጋ፣ እንጀራ ፍለጋ ይሰደዳል።

የአሜሪካ ድምጽ ራዲዮው አዲሱ አበበ ከሊቢያ ሁለት ስደተኞችን በስልክ አነጋግሮ ነበር። ሁለቱንም ወደሃገር ቤት መመለስ እንደሚፈልጉ ጠይቋቸው የሰጡት ምላሽ “መመለስ አንፈልግም!”  የሚል ነው። እነዚህ ወገኖች በሞት ጥላ ውስጥ ሆነው እንዲህ ማለታቸው በሀገር ቤት ያለው ችግር ምን ያህል የከፋ መሆኑን ይጠቁመናል።

ሰሞኑን በወገኖቻችን ላይ እየደረሰ ያለው ግፍ አዲስ አይደለም። የአይሲሱ ግድያ አለም አቀፍ ትኩረትን ሳበ እንጂ በሳዑዲ አረቢያ፣ በደቡብ ሱዳን፣ በኬንያ፣ በታንዛኒያ፣ በየመን፣ በደቡብ አፍሪካ፣ በእስራኤል ወዘተ ፍጹም ኢ-ሰብዓዊ የሆነ ድርጊት በዜጎቻችን ላይ ተፈፅሟል። ሴቶች እህቶቻችን በጎረምሶች ተደፍረዋል። በአሰቃቂ ሁኔታም ገድለዋል። ለዜጎቹ የሚከራከር አካል ባለመኖሩም የተናቅን ህዝብ አደርጎናል።

እስራኤል ሃገር በፈላሽ ሙራዎች ላይ እየደረሰ ያለውን የዘር መድልኦ አለም ሲያወግዘው የኛዎቹ ዝም ነው ያሉት። ባለፈው አመት ናይሮቢ ውስጥ ሰባ የሚሆኑ ኢትዮጵያውያን እየተለቀሙ ሲታፈሱ እና ሲታሰሩ  እዛ ያለው የኢትዮጵያ ኤምባሲ “ኬንያ ውስጥ ጉዳት የደረሰበት ሕጋዊ ዜጋ የለም” ሲል ነበር መልስ የሰጠው። ሊብያ በፈራረሰች ግዜ አፍሪካ ዜጎች በየኤምባሲያቸው ገብተው ሲጠለሉ ኢትዮጵያውያን መሄጃ አልነበራቸውም። በመጨረሻ ግን የናይጄሪያ ኤምባሲ ተቀብላ አስተናገደቻቸው።

አይሲስ ወደ የመን እየገባ መሆኑ በተሰማ ግዜ ሰይፉ ፋንታሁን አንድ ዘገባ አቅርቦ ነበር። በዘገባው ላይ የመን ያሉ ኢትዮጵያውያን መንግስት ከወሬ ያለፈ ምንም ነገር እንዳላደረገ ይናገራሉ። ይልቁንም ዓለምአቀፍ ሞዴልና ተዋናይ የሆነችው  የሐረር ወርቅ ጋሻው ስደተኛውን ለመርዳት የአቅሟን እያደረገች እንደሆነ ጋዜጠኛ ግሩም ተ/ሐይማኖት ተናግሯል።

በየመን እየታየ ያለውም ጉዳይ እርግጥ “ኢትዮጵያ መንግስት አላት ወይ?”..የሚለውን ጥያቄ የሚመልስ ነው። ጋዜጠኛው የመን ያለው የኢትዮጵያ ኤምባሲ “እንረዳቸዋለን ወይስ እናርዳቸዋለን?” ነው ያለው ሲል ባሰፈረው ጽሁፉ በዶቺቬሌ ቃላቸውን የሰጡት የኤምባሲው ቃል አቀባይ አቶ አምደሚካኤል ንግግር ኣሳፈሩን ይላል። “ኢትዮጵያዊያኑን እንረዳቸዋለን። ከአይ.ኦ.ኤም. ጋር በመተባበር ወደ ሀገር መመለስ የሚፈልጉትን እንመልሳለን”  ብለዋል። … ” አዎ ይረዳሉ ግን ኤምባሲ ውስጥ ላሉ ሰራተኞች ነው። . . . እኛን ግን እንረዳለን ማለት ፈልገው ሳይሆን እናርዳቸዋለን ማለታቸው ነው። ሲያርዱ እንጂ ሲረዱ መቼ ታይተው ነው።” ብሎ ነበር የጻፈው።

እውነታው ይህን ይመስላል። አንዳንድ የስርአቱ አጨብጫቢዎች ታዲያ ይህ እውነታ አይወጥላቸውም። ዜጋ እየተሰቃየ እነሱ ግን ስለ ህንጻ  ይነግሩናል፤ ስለ ታምራዊው 11 በመቶ የኢኮኖሚ እድገት ይሰብኩናል።  . . . ሕንጻና መንገድንማ ቅኝ ገዥዎችም ሰርተዋል። ለዚያውም እነሱ ከሚነግሩን የበለጠ።

ሕዝብ ደግሞ እያለ ያለው ፣  “ከህንጻ በፊት ነጻ!” እንሁን ነው! ሀገር ማለት መሬት አይደለም። ሃገር ማለት  ወንዙ፣ ተራራው፣ ሽንተረሩ፣ አደለም። ሃገር ማለት ሕዝቡ ነው። የህዝቡ ሰቆቃ ግድ የማይለው አካል መንግስት ሊሆን አይችልም።

ክንፉ አሰፋ

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Left Column

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የአማረ ሪፖርተር እያደረሰ ያለው የብሔራዊ ደኅንነት አደጋ January 22, 2026 01:56 am
  • የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የማርያምን ማዕረግ ዝቅ አደረገች December 12, 2025 09:27 pm
  • ኢህአፓ: ከነጭ ሽብር ወደ “አዲስ አበባ ትናገር” የጎዳና ሽብር? December 12, 2025 09:11 pm
  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am
  • Rusted screws, metal spikes and plastic rubbish: the horrific sexual violence used against Tigray’s women July 4, 2025 01:48 am
  • በሞርሞን ቤ/ክ ዕርዳታ የኪዳነምህረት ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ማምለኪያ ሥፍራ አገኘች July 2, 2025 01:28 pm
  • የበረከት ስምዖን “አየር ላይ ትዕይንት” አየር ላይ ተበተነ July 2, 2025 01:24 am
  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule