ጠቅላላ ወጪው 475 ሚሊዮን ዶላር እንደሆነ የተነገረለት የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር በብልሽት ምክንያት ግማሽ ያህል ባቡሮቹ እንደማይሰሩ ተነገረ፡፡ የባቡሩ ፕሮጀክት ከመጠናቀቁ በፊት ሥራው እንዲጀመር ህወሃት/ኢህአዴግ ግፊት አድርጎ ነበር፤ የቀላል ባቡር ፕሮጀክት የፖለቲካ ውሳኔ ነው፤ ቀላል ባቡሩ “እየቀለለ ነው” ተብሏል፡፡
ማክሰኞ ዕለት የተሰማው ሸገር ሬዲዮ ስማቸውና ድምጻቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ መረጃ አቀባዮቼ አደረሱኝ ባለው መሠረት ከተጀመረ ዓመት ያልሞላው የአዲስ አበባ የቀላል ባቡር ሥራ “እየቀለለ” መሆኑን ተናግሯል፡፡ ለአገልግሎት ከተመደቡት 41 ባቡሮች ውስጥ በሥራ ላይ የሚገኙት 28ቱ ብቻ መሆናቸውን መረጃ አቀባዮቹን ጠቅሶ ሬዲዮው አስረድቷል፡፡ ሃያ አንዱ ባቡሮች በብልሽት ምክንያት አብዛኛውን ጊዜያቸውን የሚሳልፉት በጥገና እንደሆነ፤ የመለዋወጫ ችግር ደግሞ ይበልጥ ሁኔታውን እንዳባባሰውና ለዚህም ተጠያቂው ኃላፊነቱን የፈረመው የቻይናው ኩባንያ ሲኤንአር መሆኑን አክሎ አስታውቋል፡፡
በጉዳዩ ላይ የተምታታ ምላሽ የሰጡት የህወሃት/ኢህአዴግ ሹመኛ ደረጀ ተፈራ 21ዱ ባቡሮች አገልግሎት እንደማይሰጡ አልካዱም፡፡ ግን የቆሙት ባቡሮች ምክንያታቸው ብልሽት ብቻ ሳይሆን ለመጠባበቂ ነው በማለት ከተናገሩ በኋላ ብልሽት ያለባቸውን ደግሞ ህወሃት/ኢህአዴግ ለሰው ህይወት በጣም የሚያስብና የሚጠነቀቅ በመሆኑ ለአገልግሎት እንዳይወጡ ማድረጉን አስታውቀዋል፡፡
ሹመኛው አክለውም ባቡሮቹ የማይሠሩት የተጠቃሚ ቁጥር በሚያንስበት ጊዜ እንዲሁም የኤሌክትሪክ አቅርቦት በማይኖርበት ወቅት መሆኑን አልሸሸጉም፡፡ “ለመጠባበቂያ ነው የቆሙት” በማለት አስቀድመው የሰጡትን ሃሳብ በመቃወምም የባቡሩ ተጠቃሚ ብዙ እንደሆነና አቅርቦቱና ፍላጎቱ ባለመመጣጠኑ ባቡሮቹ ከመጠን በላይ በመሥራታቸው ለጥገና መጋለጣቸውን ተናግረዋል፡፡ የተሳፋሪውን መጠንም ሲገልጹ “የሚጠቀመው ሰው በጣም ብዙ ነው” ያሉት ሹም “ባቡሩ ቶሎ ወደ አገልግሎት እንዲገባ ግፊት እንደነበር” በመናገር የግፊቱ እና የችኮላው መንስዔ የህዝቡ ፍላጎት እና “የእኛ ግፊት” ነበር በማለት ዋንኛው ተጽዕኖ “ሌጋሲ፤ ውርስ፤ ህዳሴ፤ የሙት መንፈስ፤ …” መሆኑን ከመጥቀስ በመቆጠብ በደምሳሳው አልፈውታል፡፡
ሬዲዮው ባገኘው መረጃ መሠረት የባቡሩ ውል ከቻናው ሲኤንአር ኩባንያ ጋር ሲፈረም የህወሃት ሹሞች ኩባንያው መለዋወጫም እንዲያቀርብ በስምምነቱ ላይ ኩባንያውን አለማስፈረማቸው እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡ ምናልባት እንደ ውጫሌ ውል የቻይንኛውና የአማርኛው (ወይም የህወሃት ሰዎች እንዲገባቸው የተጻፈበት ቋንቋ) ቅጂ ካልተለያየ በስተቀር እንዲህ ዓይነቱ እጅግ በርካታ ገንዘብ የፈሰሰበት ፕሮጀክት ላይ የመለዋወጫ ዕቃ ውል መፈጸም ለጥያቄ የሚቀርብ አይደለም በማለት አስተያየት ሰጪዎች ይናገራሉ፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ የባቡር ኮርፖሬሽኑ ለጥገና ብሎ ያስቀመጠው ወይም የበጀተው አለመኖሩ የቀላል ባቡሩን ቅለት የሚሳይ ብቻ ሳይሆን በግልጽ የፖለቲካ ውሳኔ የተፈጸመ ፕሮጀክት ለመሆኑ አብሮ ይነገራል፡፡
ገና ከጅማሬው ታላቅ ገቢ ያስገኛል፤ የከተማዋን የትራንስፖርት ችግር ያስወግዳል፤ በአንድ ጉዞ ከ300 በላይ ተጓዦችን ያሳፍራል፤ በሰዓት 80ኪሜ መብረር ይችላል፤ ከምስራቅ አፍሪካ ብቸኛው ነው፤ በአፍሪካ ከሚጠቀሱት ሰባት የከተማ ባቡሮች የዘመነው ነው፤ … ተብሎ ከበሮ የተደለቀለትና ፈንዲሻ የተነሰነሰለት ቀላል ባቡር አንድ ዓመት ሳይሞላው እንዲህ እንደ ስሙ መቅለሉ የህወሃት/ኢህአዴግ ማንነት ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ነው በማለት አንድ የጎልጉል አስተያየት ሰጪ በላኩልን መልዕክት ላይ አስታውቀዋል፡፡
በአንድ ጀምበር ታላላቅ ፕሮጀክቶችን በመጀመር የታላቅነትን ነጋሪት እየመታ የሕዝብን ቀልብ ለመሳብ የሚፈልገው ህወሃት/ኢህአዴግ የከተማ ዜጎችን ቁም ስቅል እያሳየ ለከተማ ነዋሪዎች አስባለሁ ማለቱ አብሮ የማይሄድ እንደሆነ የሚናገሩ ወገኖች፤ በርግጥ ህወሃት/ኢህአዴግ ለከተማው ህዝብ የሚያስብ ከሆነ በክረምት እመጫቶችን ሳይቀር ከጨቅላ ህጻናቶቻቸው ጋር ከደሳሳ ጎጇቸው ማፈናቀሉን ያቁም፤ በሞትና በህይወት ላይ ባለ በሽተኛ ማላገጡን ትቶ ለህክምና ነጻነት ይስጠው፤ … እነዚህን ቀላል ነገሮችን ያድርግልን በማለት አንድ የአዲስ አበባ ነዋሪ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
ከተዘረጋላቸው የሃዲድ መስመሮች እያፈተለኩ እንደሚወጡ የሚነገርላቸው ባቡሮች እንቅፋት እንዳመታቸው ሃዲዶቹ እንደሚጠረጉና በባቡር ቫዝሊንም (ግራሶ) እንደሚለሰልሱ ሬዲዮው ጨምሮ ተናግሯል፡፡
ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ®ንብረት ናቸው፡፡ ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (https://www.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን፡፡
gud says
Golgul eyekelele new
Anti Ethiopian news site .
gud says
You fools . You criticize everything ,then the public see u as clowns .
አሳፋሪዎች says
ምነው ኢሃድግም እንደ ባቡሮቹ ቢወላልቅልን ምን ነበረበት።
tesfai habte says
ለኢትዮጵያ ህዝቢ ለማታለል እጂ ለስራ እውነተኛ ወይም ለሃገር ግንባታ ተብሎ የተሰራ ኣለመሆኑ የተረጋገጠ ነው።
ሸመልስይማም says
መነዉ አንደ ሊቢያው መአመር ጋዳፊ ህወሀት ኢህአዴግ ቢፈራርስ ፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ደስታ ነበር ፡፡