• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ቤት መኖሩን እንመን፤ ከዚያ እንግባ!

March 1, 2013 08:52 am by Editor 1 Comment

በአውሮጳውያኑ አቆጣጠር በ1960ዎቹ በአሜሪካ የተካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ጠንካራ ፉክክር የተደረገበት ነበር፡፡ ጆን ኤፍ ኬኔዲና ሪቻርድ ኒክሰን እጅግ ከፍተኛ ውድድር ካደረጉ በኋላ ኬኔዲ አሸነፉና ሥልጣኑን ተቆናጠጡ፤ ኒክሰን የሽንፈትን ጽዋ ጠጡ፡፡

ከኒክሰን ደጋፊዎች መካከል ቀዳሚ የነበረው የፊልም ተዋናይ ጆን ዌይን ነበር፡፡ የካው ቦይ ጫማውን አጥልቆ፤ ፈረሱ እየጋለበ፤ ሽጉጡ እያሽከረከረ፤ ጠላቶቹ በፊልም ይረፈርፍ የነበረው ጆን ዌይን ከሚከተለው የጸና የፖለቲካ አመለካከት አኳያ ሪቻርድ ኒክሰንን በመደገፍ ለማሸነፍ እንዲችሉ የተቻለውን እገዛ ያደረገ ነበር፡፡ ሆኖም ያሰበው አልተሳካም፤ የተመኘው መሪ ነጩ ቤተመንግሥት አልገባም፤ በሕገመንግሥቱ መሠረትም የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ አልሆነም፡፡ ጆን ዌይን ኬኔዲ ማሸነፋቸውን በተረዳ ጊዜ ግን አገር ወዳድነቱንና አርበኝነቱን በሚከተሉት ቃላት በመግለጽ በታሪክ ሲጠቀስ ይኖራል፡ “(ለኬኔዲ) ድምጼን አልሰጠሁም፤ ነገር ግን ፕሬዚዳንቴ ነው፤ መልካም ሥራ ይሰራል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡”

ለጆን ዌይን አሜሪካ ቤቱ ነች፡፡ እዚያ ቤት ውስጥ መግባትና መገኘት የመጀመሪያ ተግባሩ መሆኑን በማመኑ ድልን ብቻ ሳይሆን ሽንፈትንም በጸጋ ለመቀበል አልተቸገረም፡፡ ጉዳዩ የዴሞክራሲ ውጤት ነው ቢባልም ዴሞክራሲው ራሱ ሊኖር የቻለው ቤት በመኖሩና በነዋሪነት ለመታወቅ የሚፈልግ ሁሉ ቤት መኖሩን አምኖ እዚያ ሲገባ ነው፡፡ ከዚያ ድጋፉና ነቀፋው እንዲሁም ተቃውሞው በየፈርጁ ይስተናገዳል፤ የዴሞክራሲም ብቃት በየደረጃው ከፍ እያለ ይሄዳል፡፡

117ኛው የአድዋ በዓል ሰሞኑን ይከበራል፡፡ በዚህ በዓል ከኢትዮጵያውያን ሌላ አንዳንዴም በላቀ መልኩ የጥቁር ዘር ክብር ይጎናጸፋል፤ ይከብርማል፡፡ ከዚህ በዓል ጋር ተያይዘው የሚነሱ ዓቢይ ጉዳዮች አሉ፡፡ አብረው የሚጠቀሱ የጀግና ስሞችም አሉ – ወንድም ሴትም! ሁሉም ለጦር ሲዘምቱ በብሔር ወይም በጎሣ ወይም በቤተሰብ … ጠባብ አስተሳሰብ ሳይሆን በአገር ሉዓላዊነትና በንጉሥ ክብር እንደነበር ለማረጋገጥ በዚያን ዘመን መገኘትም ሆነ በጦርነቱ መሳተፍ አያስፈልግም፡፡ “አገር የወረረ ጠላት መጥቷል በተገኘው አጋጣሚ እና ዓቅም መባረር አለበት” የሚለው ሁሉንም በአንድ ዓላማ ያስተሳሰረ መሪ ሃሳብ ነበር፡፡ ለዚህም ነው ወንድ፣ ሴት፣ የጦር ባለሙያ፣ ገበሬ፣ … ጉንድሾች እንኳን ሳይቀሩ በድንጋይም ሆነ በዱላ ለመዋጋት የወጡት፡፡

እነዚህ ሁሉ ኢትዮጵያውያን አንድ ሃሳብና አንድ አስተሳሰብ ነበራቸው ለማለት አይቻልም፡፡ በሰላሙ ጊዜ በመደብ፣ በጾታ፣ በሃብት፣ በሥልጣን፣ … የተከፋፈሉ ነበሩ፡፡ የሥርዓቱ ተጠቃሚ የሆኑ ያሉበትን ያህል የተጎዱና ግፍ የደረሰባቸውም ቀላል ቁጥር አልነበራቸውም፡፡ የጣልያንን ወረራ ግን “የኔ ጉዳይ አይደለም” ወይም “እኔን አይመለከተኝም” አላሉም፡፡ “እኔ በደል የደረሰብኝና ግፍ የተቀበልኩ ስለሆነ ጣሊያን ወረራ ቢያደር ባያደርግ የኔ ጉዳይ አይደለም” በማለት ምላሽ ከመስጠት ተቆጥበው አልተቀመጡም፡፡ እርስበርስ ለመጨቃጨቅና መብትንም ለማስከበር እንዲሁም ምኒልክንም ቢሆን “ንጉሤ አይደለህም” ለማለት መጀመሪያ አገር መኖር እንዳለባት ብልሆቹ አባቶቻችን ተረድተው ነበር፡፡ መጀመሪያ በቤት መኖር አምነው ስለነበር እዚያው ቤት ውስጥ ገብተው ነበር፡፡

ከአድዋም በኋላ በአገራችን በተከሰቱ የውጪ ወረራዎች ህይወታቸውን የሰዉና የሚገባቸውን ክፍያ ሳያገኙ የቀሩ እጅግ በርካታዎች ናቸው፡፡ ባንዳዎች ንጉሡ ባደላደሉላቸው የሥልጣን ኮርቻ ላይ ሲሳፈሩ ሁኔታውን እናየንጉሡን አካሄድ የተወሰኑ ቢቃወሙም ኢትዮጵያ ቤታቸውን ግን አልካዱም፡፡ ወይም አገራቸውን ለወራሪ አሳልፈው አልሰጡም፡፡ ዓይን ያወጣ በደል ተፈጽሞባቸውም እንኳን ጣሊያን ተመልሶ ቢመጣ ወይም ሌላ ወራሪ ኢትዮጵያን ለመንካት ቢቃጣ እንደገና በንጉሡ አዝማችነት ህይወታቸውን ለመሰዋት እንደሚወጡ ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ ምክንያቱም ምኒልክም ሆኑ ኃይለሥላሴ ንጉሦቻቸው ባይሆኑም ኢትዮጵያ ግን አገራቸው ናት! ቤታቸው ነች!

ከእነዚህ ትውልድ በኋላ የመጣውና እስካሁን መቀመጫ መርገጫው የተሳከረበት የእኛ ትውልድ በበርካታ ውጣውረዶች ውስጥ አልፏል፡፡ በመሆኑም አገሩንና ሊያራምድ የሚፈልገውን የፖለቲካ ዓላማ ነጣጥሎ ለማየት ያቃተው ከመሆኑ የተነሳ በ1970ዎቹ በተከሰተው የሱማሌ ጦርነት ጊዜ እንደሆነው አንዴ የውጪ ወራሪ ሲደግፍ ሌላ ጊዜ ደግሞ በነጻአውጪ ግምባርነት ተደራጅቶ ጎሣውን “አገር” ለማድረግ መከራውን ሲያይ አራት ዓስርተ ዓመታት አልፈዋል፡፡

አገርና የፖለቲካ ዓላማ የተለያዩ መሆናቸውን ማስረዳት አንሻም፡፡ ፖለቲካ ውስጥ የገቡ በሙሉ ይህንን ያስተውሉታል ብለን እናምናለን፡፡ ከፖለቲከኞች አልፎም የኢትዮጵያ ሕዝብም ይህንን በውል የሚያስተውለው ነው፡፡ ሆኖም ይህ አገርን ከሁሉ በላይ አስበልጦ የማየት ሁኔታ ፖለቲካውን በተቆጣጠሩት ዘንድ እየደበዘዘ ከመምጣቱ የተነሳ ከመጣው ጋር መንጎድ ፈሊጥ ሆኗል፡፡ ህዝብንም በዚሁ የጭፍን መንገድ መምራት የትግል ስትራቴጂ ተደርጎ ተወስዷል፡፡ ግን አልሠራም! ወደፊትም አይሠራም!

ኢትዮጵያ ጠላት አይደለችም፡፡ ሰንደቅ ዓላማዋም ጨቋኝ አይደለም፡፡ አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ ከኢትዮጵያ አልፎ የአፍሪካና የመላው ጥቁር ሕዝብ በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ መለያ ሆኗል፡፡ ይህም የሆነው በአድዋ ድል ነው! አጼ ምኒልክን ንጉሣችን እንዲሆኑ አልመረጥናቸውም፤ ምርጫውም አልነበረም፡፡ የአድዋን ጦርነት ግን መርተዋል፡፡ በእርሳቸውና በሌሎች እጅግ ቆራጥ በሆኑ ኢትዮጵያውያን መስዋዕትነት ምክንያት “… አበሻ ግብሩ እንቁላል” ከመሆን ድኗል፡፡ ድሉ የኢትዮጵያ ነው፤ ሲቀጥልም የአዝማቹና የዘማቹ፡፡ ጦርነቱ በኢትዮጵያ ሽንፈት ቢጠናቀቅ ኖሮ ምኒልክን “አዋርደን” በታሪክ ከመጥቀስ አንቆጠብም ነበር፡፡

ባለፈው ምርጫ በዘርና ጎሣ ተከፋፍለው ደም ለመፋሰስ የበቁት ኬንያውያን ልዩነታቸው እንዳለ ሆኖ ሰሞኑን በተከናወነው ምርጫ ግን “ሁላችንም ራሳችንን ኬንያውያን ብለን በመጥራት እንኮራለን” ሲሉ የሰማን ጊዜ እኛስ የአመለካከት ልዩነታችን እንዳለ ሆኖ፤ ሁሉ ቀርቶ ታላላቅ ድሎቻችን ላይ ከፖለቲካና ግላዊ አመለካከት በላይ በመሆን “ኢትዮጵያውያን ብለን ራሳችንን በመጥራታችን ኩሩዎች ነን የምንል” በማለት እንድንጠይቅ ተገደድን፡፡ አውሮጳውያን በቅኝ ከያዙትና ለመያዝ ካሰቧቸው አገሮች የዘረፉትን “የ … ሙዚየም” እያሉ እንደራሳቸው ቅርስ ሲያሳዩና በየአደባባይ እያቆሙ ለትዕይንት ሲያበቁ እኛ ግን ዓይናችን ሥር ያለውን የራሳችን ለማድረግ አቅቶናል፡፡ ቤታችን አልገባንም፤ ምክንያቱም ቤት እንዳለን ከልብ አላመንንም!

ስለዚህ ከሁላችንም የሚጠበቅ የሞራል ግዴታ አለ ብለን እናምናለን፤ ከሁሉም ማለት ከኦሮሞው፣ ከአማራው፣ ከትግሬው፣ ከወላይታው፣ ከኦጋዴኑ፣ ከአኙዋኩ፣ ከጉራጌው፣ … ከሰማኒያ በላይ ከሆኑት የኢትዮጵያ የዘር፣ የጎሣ፣ … ክፍሎች የሚጠበቅ! “ምኒልክ የመረጥኩት ንጉሥ አይደለም፤ በደልም ፈጽሞብኛል ግን የአድዋ ጦርነትን መርቶ ድል ሰጥቶኛል፤ ይህ ድል የኔም ድል ነው” የሚል የሰውነትና የሞራል ፈተና ወድቆብናልና እንወጣው፤ በቁርጠኝነት እንለፈው፡፡ መራራ ቢሆንም እንቀበለው እውነት ነውና፤ ቢጎመዝዝም እንጠጣውና የኅሊና ልዕልና እንጎናጸፍ የሚረዳን ሐቅ ነውና፡፡ ከዚያ ለወገናችን በደል መታገል፤ መሟገት ይቀለናል፡፡ ምክንያቱም የራሳችንን የኅሊና ፈተና አልፈናልና፡፡ አለበለዚያ ግን “የአድዋ ድል ለ… ሕዝብ ምኑ ነው?” በሚለው አባዜ መጓዝ ከውድቀትና ውርደት በስተቀር የትም አላደረሰንም፤ አያደርሰንም፡፡ ከሁሉ በፊት ቤት መኖሩን እንመን፤ ከዚያም እንግባ!

(ፎቶ፡ Eric Lafforgue)

Filed Under: Editorial Tagged With: Left Column

Reader Interactions

Comments

  1. bek says

    March 1, 2013 02:01 pm at 2:01 pm

    This is true. I accept it !!!

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

Recent Posts

  • የመካነ ኢየሱስ ሕንጻ የጠራራ ፀሐይ ወግና “የብሌን ሠራዊት” በችሎት ደጃፍ August 5, 2026 02:35 am
  • ለሱዳንና ኤርትራ ሲከራከሩ የነበሩት አበባው ባለመመረጣቸው “በጣም ተድጃለሁ” አሉ June 26, 2026 12:29 am
  • “ትህነግ ወደ ዓለምአቀፍ ወንጀለኛነትና አሸባሪነት እየተምዘገዘገ ነው” June 25, 2026 01:00 am
  • አሜሪካ በሕገወጡ ትህነግ አመራሮች ላይ ጠንካራ የቪዛ እገዳ ጣለ June 18, 2026 10:29 am
  • እንደ ሌሊት ወፏ የሚንቀሳቀሰው ኢህአፓ/ትብብር   June 18, 2026 09:36 am
  • የታርጋ ጫጫታ June 15, 2026 05:16 pm
  • ፋንታኹን ዋቄ ከአሜሪካ የሃይማኖት እልቂት አወጁ June 15, 2026 02:12 am
  • ሕገወጡ ትህነግ ወጣቶችን ለዳግም ዕልቂት እያሰናዳ ለፈረንጆች “ኢትዮጵያን አውግዙልኝ” እያለ ነው June 11, 2026 12:57 am
  • በሐዘንና ግልፅ ደብዳቤ ስም የተሸፈነ የድህረ ምርጫ ሀገር የማተራመስ ስትራቴጂ June 10, 2026 12:19 am
  • የጽምዶ ልክፍት June 9, 2026 12:49 am
  • ገዳዩ ማነው? አስገዳዩስ ማነው? June 5, 2026 02:37 pm
  • ጽንፈኝነት ግን በኢትዮጵያ ምድር ፈጽሞ ቦታ የለውም! June 5, 2026 01:47 pm
  • የትብብሩ “ብናሸንፍም ፓርላማ አንገባም” መግለጫ “ወንበር ስታጡ ነው” የሚል ከፍተኛ ተቃውሞ አስነሳ June 4, 2026 12:04 am
  • አዲሱ የትራምፕ የምርጫ መመሪያ፡ የአሜሪካ ዲፕሎማቶችን አፍ ያስዘጋ፤ ተቃዋሚዎች ተስፋ ያስቆረጠ June 3, 2026 08:50 pm
  • “ኢህአፓ ከምርጫው በኋላ ይሰነጠቃል” May 29, 2026 07:07 pm
  • ሪፖርተር፡ “ስውር ተልዕኮ” – በከባድ ወንጀል ሊከሰስ May 6, 2026 11:55 pm
  • የፋኖ ኃይል በደረሰበት ጉዳት ሃምሳ ሺህ የሚጠጋ ትጥቅ ጥሎ ጠፋ April 29, 2026 02:27 pm
  • አዲሱ የቴድሮስ ካሳሁን 888 ኮድ፤ እንደ 666?! April 15, 2026 05:53 am
  • ምኑ ነው ያሳቃችሁ፤ ያስደሰታችሁ? April 2, 2026 10:52 am
  • የጀዋር መሃመድ የፖለቲካ ማንነት እና የባዕዳን ተልዕኮ April 2, 2026 10:16 am
  • ከግብፅ በዳያስፖራ ትርምስ ጠማቂዎች በኩል ፋኖ ወደ አዲስ አበባ የላከው “ስጦታ” March 27, 2026 09:14 am
  • “ሰላማዊ ታጋዮቹ” እነ ልደቱ ከአራጁ ሸኔ ጋር ተጣምረዋል March 25, 2026 01:04 pm
  • ጸረ-ኢትዮጵያዊ የሆነው የሪፖርተር አዘጋገብ March 19, 2026 11:54 am
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ የኦሮሚያ የልማት ድርጅቶች March 18, 2026 10:48 am
Copyright © 2026 · Goolgule