• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ብክነትና ምክነት

April 21, 2016 01:32 am by Editor Leave a Comment

በኢትዮጵያ ውስጥ ገንዘብ የሚያባክን ማን እንደሆነ እናውቃለን። ጊዜም የሚያባክነው ማን እንደሆነ ሳናውቅ አንቀርም። እንዲሁም ወንድና ሴት እንደየተፈጥሯቸው እንዳይወልዱ የሚያመክናቸው ምን እንደሆነ አሳምረን እናውቃለን። አንናገርም እንጂ። ምሁራንንስ የሚያባክንንና የሚያመክን ማነው? ጎበዝ ማለት ይህን የሚያውቅ ነው። እኔም ማወቅ የምፈልገው ያገሬን ምሁራን የሚያባክንብኝና የሚያመክንብኝ ማን እንደሆነ ነው።

ሰሞኑን ያዲስ አበባው መንግስት ቀለም ቀለም ሲሸተው ጊዜ እኔንም እንዲሁ ቀለም ቀለም ስለሸተተኝ ስለምሁራን ብንጫወት ምናለ ብዬ ለዛሬ ቁም ነገሬ እንዲሆን መረጥኩት፤ የኢትዮጵያ ምሁራን ጉዳይ፤ በተለይ ያቋማቸውና የጥቅማቸው ጉዳይ። በይበልጥ ደግሞ እንዲያው እንደዋዛ የመባከናቸው ነገር። ባክነዋል እንዴ? ካላችሁ መልሴ እንክት ነዋ!   የሚል ነው። ላስረዳ። የምናገረው ባሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ምድር ስላሉ ምሁራን መሆኑን ልብ በሉልኝ። የውጪዎቹማ  እንዲያው እንዳይቆጡኝ ድምፃችሁን ዝቅ አድርጋችሁ አንብቡልኝ እንጂ እነርሱማ የባከኑት ገና ዱሮ ካገር ከወጡበት እለት ጀምሮ ነው።

ታዲያ ምሁር ማነው? እስከ ስንተኛ ክፍል የተማረ ነው? ምናምን አትበሉኝ። ከመንግስት ጋር የሚያጣላ ጥያቄ አልወድም። በቃ ምሁር። ይገባችኋል። ለምሳሌ ባለፈው በአሜሪካ ድምፅ አማርኛው አገልግሎት ቀርበው በኢትዮጵያ ወቅታዊ ይዞታ ላይ አስተያየትና ትንተና የሰጡትን ከአዲስ አበባ ዩኒበርሲቲ የህግ፣ ሶሲዮሎጂና የፖለቲካ ትምህርት ምሁራን አይነት ማለት ነው። ስም አልጠራም።

ምሁራን በሰው ልጅ እድገት ታሪክ ውስጥ የተጫወቱትን ሚና መዘርዘር ጊዜ ስለሚፈጅ ብቻ ሳይሆን እኔም ስለማላውቀው አናነሳውም። ግን አለምን ለውጠዋል፤ አቅጣጫዋንም ወስነዋል፣ ሲባል ስለሰማሁ እኔም እንዲያ ብንል ዋስ ጥራ የሚለን ያለ አይመስለኝም። በተለይ ከ18ኛው መቶ ክፍለዘመን ጀምሮና ምናልባትም ከዚያም በፊት በየዘርፉ የተቀመሩት ሳይንሳዊ ንድፈሃሳቦችና ግኝቶች ሰውን ዛሬን እንዲመስል አድርገውታል። በተለይ በመንግስታዊ ያስተዳደር ጉዳይና የፖለቲካ ጥያቄዎች አቅጣጫ እንደየሀገሩ ተጨባጭ ሁኔታ አወንታዊም አሉታዊም ሚና ተጫውተዋል። ባንፃሩ ደግሞ ምንም ፋይዳ ያለው ስራ ሳያከናውኑ እንዲያውም ለክፉ ገዢዎች መሳሪያ አቀባይ ሆነው ያለፉበት ታሪክም ይኖር ይሆናል። መሰረታዊ ጥያቄው የቱ ሀገር በምን አኳኋን ተጠቀመባቸው የሚለው ነው። የት ባከኑ? የትስ መከኑ? በማለት መጠየቅ ማለት ነው። በኢትዮጵያ ፖለቲካ ምሁራን ጠቅመውናል? በፖለቲካው ምዳ ሚና ኖሯቸው ካልጠቀሙን ባክነዋል ማለት ነው። ምናልባትም መክነዋል።

በኔ አስተያየት በተለይ ባለፉት 40 የምጥ አመታት ምሁራንን ሳንጠቀምባቸው ባክነዋል። ያባከናቸውም መንግስት ነው፤ ያለውም የሄደውም። ደርግ ከፊሉን በመግደል ቀሪውን ደግሞ በውድም በግድም አባሪ በማድረግ እውቀታቸውን አባከነው። ብዙዎቹም የሀገራቸው ጉዳይ ሆዳቸውን እያመማቸውና አንጀታቸው እያረረ በምሁርነት ካባቸው ላይ መንግስታዊ መለዮ ደርበው ከእገሌ ጋር ወደፊት እንዲሉ ተገደዱ። ቀሪዎችም ሲያቀብጣቸው (ወይም ሲፈርድባቸው ማለት ይሻል ይሆናል) ለምን አሉና ተገደሉ። ባከኑ ማለት ይሄ አይደል? ወግነው የተረፉትም ተቃውመው የጠፉትም ያው ባክነዋል።

ዛሬስ? ዛሬም ቢሆን ታሪክ እምብዛም የተለወጠ አይመስልም። እንደመጥምቁ ዮሃንስ በበረሃ ያለሰሚ የሚጮኹ ሀቀኛ ምሁራን መኖራቸው ሳይካድ ብዙሃኑ ግን ወይ ለሆዱ ያለዚያም ለባለክንዱ አድሯል። ቀሪውም ጭልፊት እንዳየች ጫጡት በየተቋሙ ጎሬ አድፍጧል። የቀናውም ይብላኝልሽ ሀገሬ ብሎ ካገር ፈርጥጧል። እናም ሁሉም ባክነዋል።

ልማታዊ ምሁራኑ ሳይንስ፣ መንግስትና እድገት አንድም ሶስትም ናቸው በሚል ተጠምቀው 11 ሚሊዮን ህዝብ በርሃብ በሚያጣጥርባት ኢትዮጵያ 11 ጊዜ አድገናል ይሉናል። ማንም ሰው በማንነቱ መብት አለው የሚለውን የቀለም ትምህርት በላፒስ አጥፍተው ማንነት በሞት በሚያስቀጣባት ሀገር የብሄር መብት ተከበረ ይሉናል። ታዲያ ከዚህ በላይ ብክነትና ምክነት ከየት ይመጣል?

እዚህ ላይ መቼም አንተስ በኢህአዴግ አፍንጫ ስር ብትሆን ኖሮ ውዳሴ መንግስትን ከመድገም ሌላ ምን ታደርግ ነበር የሚል ተፈታታኝ አንባቢ መኖሩ አይቀርም። እኔም ባልሆን እውነቱን ተናግረው እመሸበት የሚያድሩ እውነተኛ የቀለም ልጆች መኖራቸውን አሌ የምንል አይመስለኝም። ያመኑበትን ተናግረው የለት እንጀራቸውን ያጡ ግን ደግሞ የቀለም ቃልኪዳናቸውን የጠበቁ ጀግና ምሁራን መኖራቸውን ዋቢ ጠቅሶ መከራከር ይቻላል። ሌላው ቢቀር የባለጊዜ ፖለቲከኞች ቃለአቀባይ በመሆን ሳይማር ባስተማረን ወገን ላይ ባላስተማረን ትምህርት በሃሰት ከምንፈርድ እሰየው ባያሰኝም እንኳን ጎመን በጤና ያሉትን ጎራ መቀላቀል ሳይሻል ይቀራል። ለነገሩ እሱም መፈቀዱ እርግጠኛ መሆን አይቻልም።

አንድ በንጉሱ ዘመን ሹመት የተሰጠው ሰው ሹመቱን አልፈለገው ኖሮ ንጉሱ ፊት ቀረበና እባክዎ ጃንሆይ፣ ሹመቱ ቀርቶብኝ አርሼ ልብላበት ቢላቸው፥ አይ ሞኝ፣ እሱንስ እኛ ስንፈቅድ አይደል? አሉት ይባላል። እውነት ይሁን አይሁን አላውቅም ግን ተናግሮም ሆነ ዝም ብሎ መኖር በዛሬይቱ ኢትዮጵያ እንዲህ ቀላል ምርጫ እንዳልሆነ እረዳለሁ። እናም ዝም ብሎ ከመጠቃት ዋሽቶ መጠቀም የሚል ፈታኝ እና ጨካኝ አቋም የሚወስዱ ምሁራን ቢኖሩ ልንፈርድባቸው አይገባም ካላችሁ ባላምንበትም ልስማማ እችላለሁ። ብቻ ቁም ነገሩ ሀሰት ተናግረው የተጠቀሙትም፣ ፈርተው ዝም ያሉትም መባከናቸው ነው።

ኢትዮጵያ ከሁለቱም አላተረፈችም። ሁሉንም አጥታለች።

ኢትዮጵያ እግዜር ያፅናሽ! አሜን?


“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Left Column

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am
  • Rusted screws, metal spikes and plastic rubbish: the horrific sexual violence used against Tigray’s women July 4, 2025 01:48 am
  • በሞርሞን ቤ/ክ ዕርዳታ የኪዳነምህረት ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ማምለኪያ ሥፍራ አገኘች July 2, 2025 01:28 pm
  • የበረከት ስምዖን “አየር ላይ ትዕይንት” አየር ላይ ተበተነ July 2, 2025 01:24 am
  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am
  • ከትግራይ ሾልኮ የወጣው ምሥጢራዊው ሰነድ ምንድነው? May 20, 2025 09:18 am
  • በደቡብ ጎንደር በጸዳሉ ደሴ የተመሩት 72 ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ May 19, 2025 02:24 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule