• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ይድረስ ለሰብአ ትግራይ

January 24, 2019 08:16 pm by Editor Leave a Comment

1) በመጀመሪያ ራሴን ላስተዋውቅ፤ የተወለድሁት አዲስ አበባ ስድስት ኪሎ አካባቢ ነው፤ ዘመኑም 1922 ዓ. ም. ነው፤ የአገዛዝ የመንግሥት ለውጥ የተደረገበት ዘመን ነበር፤ አባቴ አቶ ወልደ ማርያም እንዳለ (ከአንኮበር፣ ሸዋ)፣ እናቴ ወይዘሮ ይመኙሻል ዘውዴ (ከየጁ፣ ወሎ) ናቸው፤ ሚስቴ የነበረችው በአባትዋ ሸዋ (መርሐቤቴ) በእናትዋ ትግራይ (አድዋ፣ እንትጮ) ነች።

በሥራዬ አብዛኛው ዕድሜዬ ያለፈው በአስተማሪነት ነው፤ መጀመሪያ በእቴጌ መነን ትምህርት ቤት፣ በኋላ በዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ፣ ከዚያ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ሳስተምር ነበር፤ በአጼ ኃይለ ሥላሴ አገዛዝ በፓርላማ ተመርጬ ለአንድ ዓመት ያህል በመርማሪ ኮሚስዮን ሠርቻለሁ፤ ጡረታ ከወጣሁ በኋላ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤን አቋቁሜ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ስለ ሰብአዊ መብቶች ለማስተማር ሞክሬአለሁ፤ የመጨረሻ ሥራ የምለው በቅንጅት የፖሊቲካ ፓርቲ አባልነት ነው፤ ከዚያ በኋላ በመጻፍና በማሳተም ቆይቻለሁ፤

2) ከትግራይ ጋር የተዋወቅሁት በ1951 ነው፤ ክፉ ዘመን ነበረ፤ ገና ዕድሜዬ ሠላሳ ሳይሞላ በትግራይ የተመለከትሁት ስቃይና መከራ ልቤን ሰንጥቆ የገባ ነበር፤ በአገሬ በኢትዮጵያ፣ በወገኖቼ በኢትዮጵያውያን ላይ የተጫነውን አገዛዝና ግፈኛነነቱን የተረዳሁበትና ከማናቸውም አገዛዛ ጋር በተቃውሞ ለመቆም የወሰንሁበት ዓመት ነበር፤ ያን ሁኔታ አይቼ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ያለቀስሁበት ዓመት ነበር፤ በችጋር ለተጠቃው ሰብአ ትግራይ መፍትሔ ልዑል ራስ ሥዩም ለትግራይ አውራጃዎች በሙሉ በየቀኑ ጸሎት እንዲደረግ አዝዘው ነበር፤ አገዛዙ ከጊዜው የዓለም ሁኔታ ጋር መራራቁን የተገነዘብሁበት ዓመት ነበር፤ ሁለት የትምህርት ቤት ጓደኞቼን (ነፍሱን ይማረውና) መንገሻ ገብረ ሕይወትንና ኃይለ ሥላሴ በላይን አግኝቻቸው ያየሁትን አይተዋል፤ በዚያን ጊዜ ትግራይ አገሬ ነበር፤ የሰብአ ትግራይ ስቃይ የኔም ስቃይ ነበር፤ በሰብአ ትግራይ ላይ የደረሰው ችጋር የኢትዮጵያ ነበር፤ ስለዚህ የኔም ችጋር ሆኖ ተሰማኝ፤ በሕይወቴ ለመጀመሪያና ለመጨረሻ ጊዜ በመሳፍንትና መኳንንት ቤት እየዞርሁ ደጅ ጠናሁ፤ በዚያን ጊዜ የአዲስ አበባ ከንቲባ የነበሩት ደጃዝማች ዘውዴ ገብረ ሥላሴ “እኔን ትግሬ ስለሆነ ነው ይሉኛልና ተወኝ” ብለውኛል።

3) ከሀያ አምስትና ከሠላሳ ዓመታት በኋላ በጉዳዩ ላይ ሁለት መጽሐፎችን (Rural Vulnerability to Famine in Ethiopia: 1958—1977. Suffering Under God s Environment: A Vertical Study of the Predicament of Peasants in North-Central Ethiopia) እስክጽፍ ድረስ ችግሩ ከአእምሮዬም ከልቤም አልወጣም ነበር፤ ትግራይን ከአክሱም ጽዮንና ከያሬድ ለይቼ አላይም፤ ኤርትራን ከደብረ ቢዘንና ከዘርአይ ደረስ ለይቼ አላይም፤ የኔ ኢትዮጵያዊነት የሚፈልቀው ከነዚህ ምንጮች ነው፤ አውቀውም ይሁን ሳያውቁ ወያኔና ሻዕቢያ እነዚህን ምንጮች ለማደፍረስ ሞክረዋል፤ በተለይ በአለፉት አርባ ዓመታት ኢትዮጵያ በገዛ ልጆችዋ በጣም ደምታለች፤ ጥቂት ልጆችዋ በባዕድ ፍልስፍና ተመርዘው ኢትዮጵያውያንን ሁሉ ለመመረዝ ተደራጅተው ፍቅርን በጦር መሣሪያ፣ ኢትዮጵያዊነትን በዘር ለውጠው የታሪክ ቅርሳችንን ሊያሳጡን ሞክረው ነበር።

4) የምንጮቹን ጥራት ለመጠበቅ አዲስ ትግል ተጀምሯል፤ በፍቅርና ይቅር ለእግዚአብሄር በመባባል በሰላማዊ መንገድ ኢትዮጵያን ለማደስ አዲስ ትውልድ ተነሥቷል፤ ይህ ትውልድ ድምጽና የፖሊቲካ ኃይል ያገኘው ወያኔ ከሥልጣን ከመገለሉ በኋላ ነው፤ ከሥልጣን (ከአድራጊ-ፈጣሪነት) የወረዱት የወያኔ ባለሥልጣኖች የትግራይ ተወላጆች መሆናቸው በአለፉት ሀያ ሰባት ዓመታት በኢትዮጵያውያን (ሰብአ ትግራይን ጨምሮ) ላይ የደረሰውን ግፍ ሰብአ ትግራይ ሰርዘውታል ማለት ነው ወይስ የተፈጸመው ግፍ በጎሣ ሚዛን ታይቶ ተናቀ የሚሰረዝም የሚናቅም አይደለም፤ በዚያው በትግራይ ውስጥ ብዙ ግፍ እንደተፈጸመ የሚመሰክሩ የትግራይ ተወላጆች ሞልተዋል።

5) ግፍንና ግፈኛን ለማውገዝ የግፍ ተቀባዩ ወገን መሆን አስፈላጊ አይደለም፤ አእምሮና ኅሊና ያለው ሰው መሆን ብቻ በቂ ነው፤ ዛሬ የሰው ልጅ እንኳን ለሰውና ለእንስሳም በጣም የሚቀረቆርበትና ዘብ የሚያቆምበት ጊዜ ደርሰናል፤ ሰብአ ትግራይ እንዴት ከዚህ ውጭ ይሆናሉ? በአለፉት ሀያ ሰባት ዓመታት ውስጥ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ውስጥ ግፍ እንደሚካሄድ ሰብአ ትግራይ አላዩም አልሰሙም ለማለት ይቸግራል፤ በሌላ በኩል በወያኔ ዘረኛ አገዛዝ ሰብአ ትግራይ በሙሉ ተጠቃሚዎች ነበሩ የሚል ሐሜት አለ፤ ስለዚህም የግፍ አሳላፊዎች እንጂ የግፍ ተቀባዮች አልነበሩም የሚባለው ልክ ነው ልንል ነው፤ በበኩሌ ይህንን የመጨረሻውን አስተያየት ለመቀበል በጣም ያዳግተኛል፤ ለማንኛውም ሰብአ ትግራይ በቅርቡ እውነተኛ መልሱን እንደሚሰጡን እተማመናለሁ።

6) የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ባለሥልጣኖች ፍርድ ቤት የመቅረብ መብታቸው ሳይጠበቅላቸው በአስከፊ ሁኔታ እየተጨፈጨፉ አልቀዋል፤ የደርግ አባሎች በፈጸሙት ግፍ ተከስሰውና ተከራክረው ተፈረደባቸው፤ በምሕረት ወጡ፤ አሁን ደግሞ የወያኔ ባለሥልጣኖች ተራ ሆነ፤ የወያኔ ተራ ሲደረስ ትግሬነታቸው ተነሣ፤ ሁሉም የትግራይ ተወላጆች መሆናቸው ከተከሰሱበት ወንጀል አንዱ ይመስለኛል፤ ወያኔ የሥልጣን መሰላሉን ለመውጣት ትግሬነትን መሣሪያ አድርጎ እንደተጠቀመበት እውነት ነው፤ አሁን መውረድ ግዴታ ሲሆን የወጡበትን መሰላል መካድ አይቻልም፤ የወያኔ ባለሥልጣኖች ከአለፉት ሁለት አገዛዞች የሚለዩት በወያኔ ዘረኛነት ብቻ ይመስለኛል፤ ስለዚህም ዛሬ ለፍርድ የሚፈለጉት ትግሬዎች በመሆናቸው አይደለም፤ የሚፈለጉት ትግሬነትን የዘረኛነት ሥልጣን መሠረት አድርገው ፈጽመዋል በተባሉት ወንጀሎች ነው፤ ትግሬነት ከወያኔ ወንጀል ውጭ ነው፤ ፍርዱ በሥርዓት ከተካሄደ ከወያኔ ባለሥልጣኖች ጋር በወንጀል ተያይዘው የሚቆሙ የሌሎች ጎሣዎች አባሎች ይኖራሉ፤ የነሱ ድርሻ በፍርድ ካልታየ የዘር አድልዎ ተፈጸመ ለማለት እንችላለን፤ ይህ አድልዎ ሐቅ ቢሆንም የወያኔን ባለሥልጣኖች ወንጀል ወደትግሬነት አይለውጠውም፤ ስለማይለውጠውም አይሰርዘውም፤ ወንጀለኛነት ከትግሬነት ተለይቶ ብቻውን ይቆማል፤

7) ሰብአ ትግራይ አክሱም ጽዮንን አቅፎ የወንጀል ምሽግ መሆን አይችልም፤ ሰብአ ትግራይ አክሱም ጽዮን የዕርቅና ይቅር የመባባል መንፈሳዊ ኃይል እንጂ የወንጀለኞች ምሽግ እንደማትሆን ያውቃሉ፤ በኢትዮጵያውያን መሀከል አለመግባባት ሲከሰት በሰላማዊ መንገድ በንግግርና በክርክር፣ በውይይትና በምክክር መፍትሔ ማግኘት ከከፍተኛ ጥፋትና ደም መፋሰስ እንደሚያድን ይታመናል፤ ስለዚህም የሰብአ ትግራይ ምርጫ ከወንጀል ተነጥሎ ከአክሱም ጽዮን ጋር መቆም ነው።

ፕ/ር መስፍን ወልደ ማርያም
ታኅሣሥ 2011

(ምንጭ: Mesfin Wolde-Mariam Blog)

Print Friendly, PDF & Email

60

SHARES
Share on Facebook
Tweet
Follow us
Share
Share
Share
Share
Share

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የአየለ ጫሚሶ ቅንጅት ፈረሰ January 18, 2021 02:31 pm
  • ህወሓት ተሠረዘ!!! January 18, 2021 01:32 pm
  • ዓሲምባ፣ ሣልሳዊ ወያኔና ባይቶና ከመፍረሳቸው በፊት ማብራሪያ እንዲሰጡ ተነገራቸው January 18, 2021 01:00 pm
  • ቤተሰቦች አስከሬን መውሰድ እንደሚችሉ ተነገረ January 14, 2021 06:48 pm
  • ስብሃት፤ “ከሞትን ቆይተናል፤ … አሁን የቀብር ሥነ-ስርዓታችን” እየተፈጸመ ነው January 14, 2021 01:37 pm
  • “ተመልሰን እንነሳለን” ያሉት ህወሓቶች ተመልሰው ወደማይነሱበት ተሸኙ January 13, 2021 01:12 pm
  • አፋር ነፃ አውጪ (ኡጉጉሙን) ለመጠቀም የታቀደው የህወሃት ሤራ ከሽፏል January 13, 2021 01:10 pm
  • ህወሃትን ወደ ጅቡቲ ለማሻገር ሲሰሩ የነበሩ የአፋር ታጣቂዎች በሰላም ወደ ክልሉ ገቡ January 13, 2021 06:47 am
  • በታህሳስ ወር ብቻ ከ344 ሚሊየን ብር በላይ የኮንትሮባንድ ዕቃ ተያዘ January 13, 2021 06:10 am
  • የብልፅግና ፓርቲ ቀጣይ ፈተና ምን ሊሆን ይችላል? January 13, 2021 04:10 am
  • ለትምህርት እንዲሆነን January 11, 2021 01:20 pm
  • “ከተቀበሩበት የጃርት ጉድጓድ ነው ያወጣናቸው” መቶ አለቃ ስዩም ቱርቦ January 11, 2021 12:11 pm
  • የተደመሰሱና በቁጥጥር ሥር የዋሉ የወንበዴው አባላት ይፋ ሆነ January 7, 2021 01:16 pm
  • ዐቢይና መኮንኖቹ በመቀሌ፤ “ድሉ የመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው” December 13, 2020 02:36 pm
  • ወንበዴው ህወሓት ከ1.4 ትሪሊዮን ብር በላይ ዘርፎ በውጭ አገራት ባንኮች አስቀምጧል December 8, 2020 01:05 am
  • ማይካድራ – የትህነግ የዘር ማጥፋት ጥግ ቋሚ ምስክር December 8, 2020 12:57 am
  • የወልቃይት ጠገዴ እናቶች ሰቆቃ ሲታወስ December 8, 2020 12:50 am
  • የደብረጽዮን ዋሻ December 7, 2020 11:30 pm
  • ባለ ከዘራው ኮሎኔል December 7, 2020 05:15 pm
  • ሰላማዊ ሕይወት በማይጨው December 7, 2020 04:12 pm
  • ተጠርጣሪ የፌዴራልና የአዲስ አበባ ፖሊሶች የመያዣ ትዕዛዝ ወጣባቸው December 7, 2020 11:46 am
  • ከ3 ሺህ በላይ ተተኳሽ ጥይቶች በወልዲያ ጉምሩክ ሊያሳልፉ የሞከሩ 4 ግለሰቦች ተያዙ! December 7, 2020 11:18 am
  • ወንበዴዎቹ ይጠቀሙባቸው የነበሩ ተሽከርካሪዎችና የግል ሰነዶቻቸው ተያዙ December 7, 2020 10:50 am
  • ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ በሶማሌ ክልል ተመሠረተ December 7, 2020 10:31 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2021 · Goolgule