
የበርሊን ግንብ ከፈረሰ ከጥቂት ሳምንታት በኋላ በዲሴምበር 5, 1989 ዓ.ም. በምስራቅ ጀርመኗ የድሬዝደን ከተማ ነዋሪው በነቂስ ወደ ጎዳና ወጥቶ ተቃውሞ በመንግስት ላይ እያሰማ ነበር። የተቃውሞው ኃይል እየበረታ ሲመጣ ህዝቡ ወደ አንድ ህንፃ መትመም ጀመረ። ላለፉት 40 ዓመታት የራሱን ህዝብ መተንፈሻ በማሳጣት ከፍተኛ አፈና ያደርግ ወደነበረው የደህንነቱ መስሪያ ቤት፥ወደ ”ሽታዚ” ተብሎ ወደሚጠራው መስሪያ ቤት።
ጥቂት ወጣቶች ግን የሽታዚን ቢሮ ሰብሮ ከገባው ህዝብ በመነጠል በጥቂት ሜትሮች ርቀት ወደሚገኝ አንድ ህንጻ አመሩ።የወጣቶቹ ወደ ህንፃው እየተጠጉ መምጣት ያሳሰበው የጥበቃ ሰራተኛ በፍጥነት ወደ ውስጥ ዘልቆ በመግባት አንድ ቀጭን እና አጭር የሆነን የ37 ዓመት ሰው አስከትሎ ወደተሰበሰቡት ሰዎች አመራ። ያም ቀጭኑ ሰው ጥርት ባለ ጀርመንኛ ”ይህ ህንፃ የሶቭየት ህብረት መንግስት ንብረት ነው፤ወደ ውስጥ ለመግባት ከሞከራችሁ ጠባቂዎቹ እንዲተኩሱ ትዕዛዝ ተሰጥቷቸዋል” በሚል ማስፈራሪያ ከህንፃው በር እንዲሄዱ ካደረገ በኋላ ወደ ውስጥ ተመልሶ በመግባት በድሬዝደን ከተማ ወደሚገኘው የሶቭየት ጦር ዋና መምሪያ ስልክ በመደወል ”የኬጂቢ /የሶቭየት የስለላ ተቋም/ ህንፃ በነዋሪዎች ሊወረር ስለሆነ ለጥበቃ የታንከኛ ጦር ላኩልን” ብሎ ተናገረ። ይሁን እንጂ ስልኩን የተቀበለው ሰው ”ከሞስኮ ትዕዛዝ ካልተሰጠ ምንም አይነት እንቅስቃሴ እንዳናደርግ ታዘናል።ሞስኮ ግን ፀጥ ብላለች” በማለት ምላሽ ሰጠ።
ከ17 አመት በኋላ በ2006 ዓ.ም. ያ ቀጭኑ የኬጂቢ ሰላይ በድሬዝደን ከተማ ተገኝቶ ያኔ ስለነበረው ሁኔታ ሲናገር፡- ”ስልክ የደውልኩለት የጦር መሪ ‘ሞስኮ ግን ፀጥ ብላለች’ የሚለውን ሲነግረኝ ሶቭየት በማይድን ህመም ተይዛ እየሞተች ነው ብዬ በህንፃው የነበሩትን ሰራተኞች በፍጥነት ከህንፃው እንዲለቁ ካደረግሁ በኋላ የነበሩትን ዶክመንቶች እና የስለላ ቁሳቁሶች አቃጥዬ ህንፃውን የዛን ቀን ምሽት ለመጨረሻ ጊዜ ለቅቄ ወደ ራሽያዋ ሴንት ፒተርስበርግ ከተማ ሄድኩ” ነበር ያለው የያኔው ሰላይ፥የዛሬው ሀገር መሪ ቭላድሚር ቭላድሚሮቪች ፑቲን።
በርግጥ ይህንን ፅሁፍ መነሻ አድርጌ የወሰድኩት አንድ ወዳጄ በማህበራዊ ሚድያ መልክት መቀባበያ በኩል እንዳነባት ከጋበዘኝ ፅሁፍ ላይ ነዉ። ይህንን ፅሁፍ ሳነብ የሞስኮ ዝምታና የማይድን ጋንግሪን የተጋባዉ አካል በሀገሬ ምድር በመገኘቱና የዝምታው የጥፋት አፅናፍ እሩቅ መሆኑ ሲታየኝ ድሬዝደን ከተማ የትደረገዉ የቴሌግራፍ ጥሪ በዚህች ሰዓት ጣናን በተመለከተ አየተደረገ ያለዉ የድጋፍና ትብብር ጥያቄን ደግሜ እንዳስብ ቢያደርገኝ መፃፍያ ቀለሜን ሰደርኩና የሚከተለዉን እንድከጥትብ ሆንኩ… ሞስኮ ግን ዝም ብላለች…..
የብዙ ሺህ አመታት የታሪክ ድርሳናት መጀመሪያ ገፅ የሆነ፣ በብዝሃ ሕይወት ስብጥሩ የአለማት ጠበብትን ያማለለ፣ በመሃሉና ዳርቻዉ ከ30 በላይ የሚሆኑ ዘመን ጠገብ የሆኑ ገዳማት እንዲሁም በብዙ ቢልዮን ብር ዋጋ ተመን ያላቸዉ ውድና ክቡር ቅርሶች መገኛ ፣ የአፍሪካችን አማላይ ከተማ መሰረት የሆነ፣ መጠሪያው አጭር ግብሩ ግን ብዙ የሆነ ለፈርኦኖች ገፅ በረከት ለአገር አድባር ለባዕድ ሲሳይ የሆነዉ የግዮን ወንዝ የስንብት መጀመሪያ ፣ የገነት ነፋስ መንፈሻ የሆነዉ አንጡረ ሀብታቺን ጣና ሀይቅ ለወትሮ ከፊቱ ተለይቶ የማያዉቀዉ የእንኳን ደህና መጣችሁ ፈገግታዉ እንደ ሐምሌ ክረምት ጨፍግጓል አካባቢዉን ከበዉ ከሚያጅቡት ሆይሆይታዎች ይልቅ የወደፊት ዕጣ ፈንታዉ አሳስቦታል የክልሉ እንዲሁም የሀገሩ መንገስት አመድ አፋሽ ሲያደርገዉ መመልከቱ በትዝታ ወደሁዋላ ተመልሶ የአፄ ዳዊት ፣ የአፄ ዘርዓ ያዕቆብ ፣ የአፄ ሱስንዮስና ፣ የነአፄ ፋሲል ደግነትና የስስት አይን እያስታወሰ የዜማው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ በጣና ቆይታዉ ያዜምለት የነበረዉን ዜማ ዳግም መስማት እየተመኘ ይቆዝማል። ጣና ስጋት ዉጦታል፤ እነዛን የብዙ ሺ ዘመን ታሪክ ባለቤቶቹን ደሴቶች ከነታሪካቸዉ ደከመኝ ሳይል ጥንቅቅ አድርጎ ለስንት ዘመን ተሽክሞ የቆየ ጉልበት ዛሬ ለእንቧጭ አረም መንበርከኩን ይህ አረም ላለፉት ስድስ አመታት እንደ መጥፎ ቁስል ሲመዘምዘዉ ከርሞ ዛሬ እንደረታው ሲያስበዉ፤ በዚህ ከቀጠለ እጣፈንታዉ እንደነ ሀሮማያ ሀይቅ መሆኑን ሲያስታዉስ፣ ቀጣይ ትዉልድ የነበረ ገርማ ሞገሱን ሳይሆን ደረቅ መሬቱንና ባዶ ታሪኩን እንደሚወርስ ሲያስብ ጣናን ስጋት ይወርሰዋል። ዙርያዉን ስጋ እንዳገኘ ጉንዳን የከበቡት ሆቴሎችና መዝናኛዎች እንዲሁም የእርሻ መሬቶች ለችግሩ መባባስ ዋነኛ ምንጭ መሆናቸዉን ሲያስብ እሱን ከበዉ እሱን መከታ አድርገዉ እንደ አልቅት ዉስጡን ሲመጡት እነሱ ሲያድጉና ጡንቻ ሲያወጡ መታመሙን እንኩኳን እያዩ ለጥየቃ ብቅ አለማለታቸዉን ሲያይ አብዝቶ ዉስጡ ይከፋል ይራገማል።
መነሻዉን በሰሜንና በደቡብ አሜሪካ አድርጎ በ1803 እ.ኤ.ዓ ብቅ ያለዉ በሳይንሳዊ ስም አጠራሩ (Water hyacinth) ወይም በተለምዶ አጠራሩ ወተር-ዊድ በመባል የሚታወቀዉ የዉሃ ላይ አረም በተለያዩ አለማት በተለይም በላቲን አሜሪካ የሚገኙ ሐይቆችና ተፋሰሶች ዙርያ በመብቀል የአካባቢውን ብዝሃ-ሕይወት ስርጭትና እድገት ላይ ከፍተኛ እክል በመፍጠር እንዲሁም በአካባቢዎቹ የወባና ሌሎች ተዛማች ችግር መንስኤ በመሆን እንዲሁም ከፍታኛ ደረጃ የመራባት ባህርይው ሃይቆችንና አካባቢዉን በመዉረርና በከፍተኛ ደርጃ በመዛመት በአካባቢዉ የዉሃ ተፋሰሶችን ሂደት በመገደብ እንዲሁም በበቀለበት አካባቢ ያለዉን ዉሃ በከፍተኛ ደረጃ እንዲደርቅ በማድረግ የተፈጥሮ ስጋት መሆን ከጀመረ ዘመናት ተቆጥረዋል። ይህ አደገኛ አረም የመዛመት አቅሙ ከፍተኛ ሲሆን በተለያየ መንገድ ከሀገር ሀገር ሲሻገር በመቆየት ዘግየት ብሎም ቢሆን አህጉራችንን በመጎብኘት የአስዋን ግድብን በተለይም ከአፍሪካ በትልቀቱ ተወዳዳሪ የማይገኝለትን ቪክቶርያ ሀይቅ ላይ ከፍተኛ የሚባል ደረጃ ተዛምቶ የነበረ ቢሆንም የሀገሪቱ መንግሥታቶች እንዲሁም የሚመለከታቸዉ አካላቶች ተገቢዉን ክትትልና ግዜውን የጠበቀ እርምጃ በመዉሰዳቸዉ በቁጥጥር ስር ሊያዉሉት ችለዋል። ታድያ ይህ አረም በነዚህ ሀገር መንግሥታት ብርታት በቁጥጥር ስር ዉሎ አደጋ ከመሆን መዳን ቢቻልም ወደተለያዩ ሃገራት የመዛመት እድሉን ግን አልነፈጉትም።
በርግጥ የዚህ አረም የመዛመቻዉ ብዙ ጥያቄን የሚያስነሳ ቢሆንም ወደሃገራቺን ከመግገባት ያገደዉ ነገር የለም ይህ አረም ከዚህ ቀደም በነ ዝዋይ፣ አዋሽ እንዲሁም አባ ሳሙኤል ሃይቆች ላይ ተከስቶ የነበረ ቢሆንም በጊዜዉ በተደረገ ርብረብ መቆጣጠር ተችሏል ሆኖም ከዛሬ ስድስት ዓመት በፊት በጣና ሀይቅ ዙርያ ምንጩ ባልታወቀ ምክንያት እንደተከሰተ የተለያዩ ጥናቶች ያመለክታሉ ይህንንም ተከትሎ በአካባቢዉ ባሉ ነዋሪዎችና ገበሬ ማህበራት ጉትጎታ በአካባቢዉ የሚገኙ ዩንቨርስቲ ተመራማሪዎች ከዩኔስኮና የተለያዩ የርዳታ ተቋማት ድጋፍ ከ2011 – 2015 አ.ም ድረስ የተደረጉ ተከታታይ ጥናቶች አደጋዉንና ያለበትን ደረጃ፣ መወሰድ ያለበት አማራጭ እርምጃ ጭምር ለሚመለከተዉ አካል ቢያቀርቡም እነዚህ ጥናቶች ለተመራማሪዎቹ የቀን አበል ከማስገኘት ዉጪ ዉጤት አምጥጠዉ መፍትሄ መሆን አልቻሉም። በዋናነት ጉዳዩ የሚመለከተዉ የልሉ መስተዳደር (ብአዴን) ለችግሩ አፋጣኝ መልስ ከመስጠት ይልቅ የፖለቲካ ጥቅም ለማግኘት ከላይኞቹ ጋር እንበር ተጋዳላይ መደለቁን ተያይዞታል።
የፌደራል መንግስትም ቢሆን እንኳን ለሀይቅ በአስር ሚሊዮን ለሚቆጠሩ በእርሃብ አለንጋ ለምጠበሱ ኢትዮጵያዉያኖች ደንታ ሳይሰጠዉ ለተመፅዋች የመጣዉን የአርዳታ እህል መልሶ ለመሸጥ ገበያ በማፈላለግ ከዛም በመደራደርና በመሸጥ መወጠሩን የሞተ አህያ ጅብ አይፈራም (Dead donkeys fear no hyenas) የሚለዉ ዘጋቢ ፊልም በመረጃ እንካችሁ የዘራፍያችሁ ሰባዊነት ጥግ ካለን ሰነባብቷል። እርግጥ ነዉ የህዝብን ይሁንታ አግኝቶ ባሳለፍነዉ ምርጫ መቶ ከመቶ ደፍኖ የተመረጠዉ ፀሐዩ መንግስታችን የሀገሪቱ አንደኛ ዜጋ ለሆኑ ማህበረሰቦች የኢንዱስትሪ መንደር ግንባታ ላይ ሙሉ ግዜዉን አዉሎታል ትንሽ የተረፈችዉንም ለዛዉ ምረቃ ተጠቅሞባታል ከዚያም ሲያልፍ እነ ተከዜን የሃይድሮ ኃይል ማመንጫ ግብአት እንዲሆኑ ያሰራቸዉ ግዙፍ ሰዉ ሰራሽ ሃይቆች በአማራጭነት ሻጥ ማድረጉ ልቡን አደንድኖታል። “የአክሱም ሃዉልት ለወላይታ ሕዝብ ምኑ ነዉ” እንዲሉ ባለራእዩ መሪያችን።
ወደቁምነገሩ ስመለስ ላለፉት ስድስት አመታት በአካባቢዉ የሰፈሩ የቀበሌ ገበሬ ማህበራት በደቦ በመዉጣት በባህላዊ መንገድ የሞት ሽርት ትግል ሲያደርጉ ቢቆዩም አሁን ግን ከቁጥጥር ዉጪ በመዉጣት በሐይቁ ላይ የሕልኡና አደጋ እንዲያዣብብ አድርጉአል። በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲሉ የባህርዳር ከተማ የፍሳሽ ቁሽሻ ያለምንም ጥንቃቄ ወደ ሀይቁ እንዲፈስ መደረጉ ለዚህም የከትማዋ አስተዳደር ከዛም ሲያልፍ ክልሉ መንግስት የምወስዱት አፋጣኝ ምላሽ ወይንም መፍትሄ አለመኖሩን ችግሩን ተደራራቢ ከማድረጉም በተጨማሪ ለችግሮቹ መፍትሄ ለመስጠት የሚመለከተዉ አካል ያምያሳየዉ ተነሳሽነትና ፍላጎት አለመኖር። የችግሮቹን መንስኤ በሌላ መነፅር እንድናይ ያስገድደናል።
“የስልክ ኦፕሬተሩ ምላሽ ከሞስኮ ትዕዛዝ ካልተሰጠ ምንም አይነት እንቅስቃሴ እንዳናደርግ ታዘናል (ብአዴን)። ሞስኮ ግን ፀጥ ብላለች” በማለት ምላሽ ሰጠ”
አንዳለመታደል ሆነና በሀገራቺን እየተከሰቱ ያሉ ዘረፈ ብዙ ችግሮች ቀን ተቀን እየጨመሩ በአይነት እና በብዛት ቁጥራቸዉና ጥፋታቸዉ እየጨመረ አሁን ካልንበት ፈጣን ምላሽን የሚሹ ጉዳዮች ዉስጥ ተጥለን በሀገሪቱ ዉስጥ የተንሰራፋዉ ዘርፈ ብዙ ችግር በየዓመቱ በደብል ዲጅት እያደገ መቶ ፣ የኢትዮጵያ ሀገራችን የመጪ ዕጣ ፈንታን እንዲሁም የእሽቁልቁሎሽ ላይ እንገኛለን ጣና ሀይቅ ልይ የትጋረጠዉ አደጋም የነዚህ ዘርፈ ብዙ የችግር ድርቶዎች አንዱ ማሳያ ነዉ።
ጣና ለቀጣዩ ትዉልድ የምናወርሰዉ የጣናን በዉስጡ ያሉት ቅርሶቹን፣ ተፈጥሮ የለገሰችዉን ዉበቱን፣ በሐይቁ ዉስጥ የዳበሩ ባህሎቹንና፣ የእምነት ሃብቶችን ሳይሆን ነበር የሚል ታሪክን እንዳይሆን ይህን የሀገር ሀብት የሆነን የግዮን ወንዝ መነሻ፣ የገነት ተምሳሌት፣ የዉበት መገለጫ የገነት በር የባለለት የተፈጥሮ በረከትታችን በኢትዮጵያ ዉስጥ በዚህም ትዉልድ ኖሮ ቀጣይ ሀገር ተረካቢ የመጭዉ ዘመን የሀገርና የዓለም ተስፋዎች ለሆኑ ልጅ ልጆቻቺን ተወቃሽ እንዳንሆን ከወዲሁ የተጋረጠበትን አደጋ ለመአስወገድ የተግባር ስራዉን መጀመር ሃገራዊ ግዴታችን ከመሆኑም በላይ የሞራልም የማንነት ጥያቄም ነዉ!
“ጣና ለወላይታ፣ ለሐረሪ፣ ለአፋሩ፣ ለሱማልያዉ፣ ለኦሮሞሞዉ፣ ለከንባታዉ፣ ለአማራዉ እንዲሁም ለሌሎች ኢትዮጵያውያኖች ተፈጥሮ የለገሰቻቸዉ በጋራ የምያጌጥጡት ሃብታቸዉ ንብረታቸዉ ነዉ”
ከዚህም በተጨማሪ ሰዉ ሰራሽ የሆኑትንና ሃይቁን በከፍተኛ ደረጃ እየበከሉት ካሉት ችግሮች አላቆ ጤናማነቱን በመበአስተማማኝ ሁኔታ መመለስና ተፈጥሮአዊ ይዘቱን ማስጠበቅ ከተቻለ የብዝሃ ሕይወት ስብትሩን ወደነበረበት ይዞታ በመመለስ ሃገራዊ ሃብትን ከማስጠበቅም በተጨማሪ በቱሪዝም መስኩም የሚገኘዉን የገቢ መጠን ከፍ በማድረግ ሀገራችን ከጭስ አልባዉ ኢንዱስትሪ ልታገኝ የሚገባትን የዉጭ ምንዛሬ ከፍ በማድረግ የራሱን ጉልህ ሚና ከመጫወጡም በላይ ከሐይቁ የሚገኘዉን 1,400 ቶን አሳ በላይ አመታዊ ምርትን በማዘመንና ሕጋዊ ቅርፅ በማስያዝ የምርት መጠኑን 10 እጥፍ በማሳደግ ለንግድ ማህበራት ፣ ለአካባቢዉ ማህበረሰብና ለአጎራባች ከተሞች የገቢና የምግብ ምንጭ በመሆን ዘርፈ ብዙ ጥቅሙን ከፍ ማድረግ ይቻላል ከዛም ካለፍን ጣናን በአግባቡ በመጠቀም የሃድሮ ፖወር ማምንጫ በመሆን የችግሮች መፍትሄ ምንጭ በመሆን ጥቅሙን ማብዛትና ማተለቅም የሚቻልበት ዕድል ሰፊ መሆኑን ልብ ይሏል።
ጣና ታሪክም ነዉ፣ ጣና ተፈጥሮም ነዉ፣ ጣና ሕልዑናም ነዉ፣ ጣና ፖለቲካም ነዉ፣ ጣና እምነትም ነው በአጠቃላይ ጣና ለሀገራቺን ሕዝብ የሕልዑናችን መሰረት ነዉ!! ጣና በጋራ እንታደገዉ የሚለዉ ሃገራዊ ጥሪዬ ነዉ!! ይህንን የሀገር ሃብትና ቅርስ ለማዳን አዋቂ ወይንም ተመራማሪ መሆን ሳይሆን ሀገር ወዳድነት የሚለዉ ቀላል መስፈርት በቂ ይመስለኛል። ታድያ ይህ መስፈርት ባለ ብዙ ታሪክና የተፈትሮ ሃብት ባለቤት የሆነችዉን ሀገርንና የማይሞላ ቀዳዳ ኪስን መለየት የተሳናቸዉን የታሪክ አተላዎችን እንዲሁም በሰዉ ሕይወት የደም ዋጋ ነፃነትንና ሃገርን ለመረከብ የምያቆበቁቡ የሞራል ድኩማኖችን፤ የሀገርን ችግርና ሰንኮፍ በሌላዉ ሰዉ ድካምና ጥረት ተወግዶ ከችግርና ሰንኮፍ የፀዳች ሀገር ላይ ለመኖር የሚመኙ እራስ ወዳድ የቀን ሕልመኞችን አያካትትም።
መብራቱ – ከስዊድን (soranet2011@gmail.com)
“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡
Leave a Reply