• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

የአቦይ ስብሃት ነጋ የሙስና ወጎች

January 15, 2017 07:42 pm by Editor 2 Comments

በአሜሪካ ሃገር፤ አንድ ባለስልጣን በሙስና ሲባልግ እስር ቤት ይገባል። በፊሊፒንስ አንድ ባልስልጣን የሙስና ወንጀል ቢፈጽም አሜሪካ ይገባል። የኛ ሃገር ባለግዜ ግን ሙስና ሲሰራ አሜሪካ እየተመላለሰ ይነግዳል። ለግዜው ልዩነቱ የዚህን ያህል ነው። ገለልተኛ የፍትህ አካል ባለበት ሃገር፤ ሙስና አፍ አውጥቶ አይናገርም፣ እግር አውጥቶም አይራመድም።

አዲሱ ቀልድ፤ “ሙስና አለ፣ ማስረጃ የለም!”

በያዝነው “ጥልቅ ተሃድሶ” ዘመን ሙስና ለሁለት ተከፍሎ እንዲታይ ተደርጓል። ማስረጃ ያለው ዘረፋ እና ማስረጃ የሌለው ዘረፋ። ልክ እንደ ግብር አከፋፈል። ግብር ከፋይ “ሀ” እና ግብር ከፋይ “ለ”። ምድቡ በዘረፋው መጠን እና በባለስልጣኑ ጉልበት ይወሰናል።  የዘረፋው መጠን ከአስር ሺህ በር በታች ከሆነ እና ዘራፊው የድል አጥቢያ ታጋይ ከሆነ ማስረጃ ያለው፣ ሙስና ምድብ “ሀ” ይሆናል። መጠኑ ከአስር ሚሊዮን በላይ ከሆነ ደግሞ ሙስና ምድብ “ለ” ተብሏል። ይህ አይነኬው ምድብ “ማስረጃ የሌለው ዘረፋ” መሆኑ ነው። አቅመ-ቢሱ ጠቅላይ ሚኒስትር በብሄራዊ ቴሌቪዥን ቀርበው የነገሩን ከዚህ እውነታ የተለየ አልነበረም። የህወሃት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት፣ የፖሊት ቢሮ እና ምክትል ሚኒስትሮች ከአይነኬዎቹ ጎራ ይመደባሉ። የ4 ሺ ብር ደሞዝተኛ፤ ጀነራል የ10 ሚሊየን ብር ቪላ አሰርቶ ሲያከራይ በግላጭ እየታየ፣ “ማስረጃ የለም” ብሎ ማለፍ የሚያሳምን አይሆንም። የእያንዳንዱ ዘረፋ ማስረጃ፤ እዚያው አፍንጫቸው ላይ ነው ያለው። ግና የሚወሰነው በባለስልጣኑ ጉልበት መጠን ነው። ምድብ “ለ”ዎችን ለመድፈር መሞከር ራሱ በሙስና ያስቀፈድዳል። ጸረ-ሙስና የሚባለውም ድርጀት የተፈጠረው ለእነሱ እና በእነሱው በመሆኑ የሚበየነውም የተገመደለ ፍርድ ነው።

ከ83 ሚሊዮን ብር በላይ የዘረፉትን ባለስልጣን ያጋለጡት አቶ ተስፋዬ ኢሬሣ፤ እስካሁን በተሰወሩ ባለ ግዜዎች ተገድለዋል። አቶ ተስፋዬ ከመገደላቸው በፊት ለጸረ-ሙስና ኮሚሽን የምስክርነት ቃላቸውን ለመስጠት ከኮሚሽነሩ አሊ ሱሌማን ጋር ቀጠሮ ይዘው ነበር። ገዳዮቹ እኝህን ባለ ሃቅ፣ አሊ ሱሌማን ጋር እንኳን እንዲነጋገሩ እድል አልሰጧቸውም። የምህዳር ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁም፣ በመንበረ ፓትሪያርክ ቅድስት ማርያም ገዳም ላይ የነበረውን የገንዘብና የንብረት ሙስና  የሚያጋልጥ ዜና በመስራቱ በከባድ የስም ማጥፋት ተወንጅሎ እስር ቤት ተወርውሯል።… አያሌ ጌታቸው ወርቁዎች፣ ብዙ ሳይታወቁ የተገደሉ ተስፋዬዎች አሉ።

ስር የሰደደው የህወሃት ሙስና፣ ዛሬ  ከዜጎች ንብረት እና ከመሬት ዝርፍያ አልፎ በቤተጸሎት ውስጥም ዘው ብሎ ገብቷል። ከሚጓዝበት ከፍተኛ ፍጥነት አንጻር በዓአብያተ-ክርስትያናት እየተስፋፋ መሄዱ ብዙ አያስደንቅም። “ኃይለኛ” የሚል ስያሜ የተሰጠው የቁሉቢ ገብርኤል ዘረፋ እንደ ምሳሌ የሚጠቀስ ነው። ከመዕመናን በተደጋጋሚ የቀረበው የ30 ሚሊዮን የሙስና አቤቱታ ተለባብሶ እንዲያልፍ የጸረ-ሙስናው ቢሮ ትልቁን ስራ ሚና ተጫውቷል።

ለፖለቲካው ትኩሳት ማባረጃ ሰሞኑን የተሞከረው የሃይለማርያም ደሳለኝ የሙስና ተረት-ተረት ምላሹ ዝምታ መሆኑም፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዝም ብለው ጉንጭ አልፋ ቃላት እንዳባከኑ መገመት አያድግትም። በዝምታ ውስጥ ያለው ጩሀት ግን ሳያስፈራ አልቀረም። እየተካሄደ ስላለው ነገር ሁሉ ብቸኛው መንገድ ዝምታ ነውና ያስፈራል። ጸጥ ባለ በዚህ ባህር ውስጥ ትናንሽ እና ትላልቅ አሳዎች እንደልባቸው ይዋኛሉ።

የቀድሞ የህወሃት አመራር አባል የነበሩት አቶ ገብሩ አሥራት “ሉዓላዊነትና ዴሞክራሲ በኢትዮጵያ” በሚለው መፅሐፋቸው ስለ ሙስናው ሲጠቅሱ፤ “…መርማሪ አቋቁመን ሥር ሰዷል የተባለውን ሙስና ስንመረምር የት እንደገባ የማይታወቅ 5 ሚሊዮን ብር ተገኘ።  ለዝርፍያው ተጠያቂዎቹም ግርማይ ካህሳይ የሚባል ሒሳብ ሰራተኛ እና ተክለ ወይኒ ነበሩ። … ይህ በሆነ ግዜ ተክለ ወይኒ ተነስቶ ‘ይህ ኮራፕሽን እያላችሁ የምታደርጉት ምርመራ ትክክል አይደለም፤ የተከሰተው ችግር የአሰራር ግድፈት እንጂ ሙስና አይደለም፤ እያንዳንዱ የህወሀት አመራር አባል ቢፈተሽ ተመሳሳይ ግድፈት ሊገኝበት ይችላል። … ዓባይ ፀሐዬ ደግሞ ከሁሉም የባሰ ሙሰኛ እንጂ ሙስናን ሊታገል የሚችል ሰው አይደለም'” ማለቱን ጠቅሰዋል።

በኢህአዲግኛ ቋንቋ የሚሊዮኖች ዘረፋ፤ ሲተረጎም የአስተዳደር ብልሹነት ሳይሆን ይልቁንም አነስተኛ የአሰራር ጉድፈት ነው። ይህንን ጥቂት ጉድፈት ደግሞ የማይሰራው የህወሃት ሰው የለም ነው እያሉን ያሉት። ለዚህ “ከገለባ የቀለለ” ጥፋት ታዲያ ከሳሽም፣ ተከሳሽም ሆነ ዳኛው አንድ አካል ነው።

ታላቁ መጽሃፍ እንዲህ ይለናል፤

“…ጻፎችና ፈሪሳውያንም በምንዝር የተያዘችን ሴት ወደ እርሱ አመጡ። በመካከልም እርሱዋን አቁመው።  ‘መምህር ሆይ፥ ይህች ሴት ስታመነዝር ተገኝታ ተያዘች። ሙሴም እንደነዚህ ያሉት እንዲወገሩ በሕግ አዘዘን፤ አንተስ ስለ እርስዋ ምን ትላለህ?’  አሉት። …. መላልሰው በጠየቁት ጊዜ ግን ቀና ብሎ። ከእናንተ ኃጢአት የሌለበት አስቀድሞ በድንጋይ ይውገራት አላቸው።”

እነሆ አቦይ ስብሃት ነጋ ስለ ሙስና ይነግሩናል። ደጋግመው ይነግሩናል። ሙሰኞች መጥፋት አለባቸውም ይሉናል። ሙሴ በአዖሪት እንዳዘዘው ሁሉ “ታላቁ መሪ” ስኳር ያሉትን የኪራይ ሰብሳቢነት ቫይረስ ለማጥፋት – የሌባው እጅ ይቆረጥ ብለዋል።  ትእዛዙ ተፈጻሚ አይሆንም እንጂ፣ ቢሆንማ ኖሮ የመጀመርያዋ ሰለባ  “ቀዳሚዋ እመቤት” ነበሩ። ፉከራው ካንገት በላይ በይሆን ኖሮ የሁሉም ህወሃት ሰዎቸ እጅ ዱሽ በሆነ ነበር።

ታዲያ ከሃጥያቱ ያልጸዳ ከየት ተገኝቶ የመጀመሪያውን ድንጋይ ይወርውር?

“ዝምታ ወርቅ ነው” እንዲሉ አቦይ ስብሃት ከአንገት በላይ ከሚቀባጥሩ ይልቅ እንደው ዝም ቢሉ ያምርባቸዋል።

የአቶ ስብሀት ነጋ ልጅ ተከስተ ስብሀት ነጋ፤ ግዙፉን የጎተራ አደባባይ ለአምስት አመት ኮንትራት በ600 ሺህ ብር እንደወሰደው ፎርቹን ጋዜጣ ይፋ አድርጎታል። የ“አክሊል ክሬቲቭ ኤጄንሲ” ባለቤት የሆነው ተከስተ ስብሀት ነጋ፤ በአካባቢው ያለን 4000 ስኩዌር ኪሎ ሜትር፣ በቢሊዮኖች የሚገመት መሬት እንደ ስጦታ ነው የወሰደው። ልጃቸው X-5  (አሁን ኤክስ አሙሽተ ተብሏል) ለወዳጆቹ በስጦታ እያበረከተ፣ አባቱ ሙሰኞችን እናጥፋ ሲሉ ይቀልዱብናል። “አባቱ ዳኛ ልጁ ቀማኛ!…”

አቦይ ስብሃት ነጋ ደርሶ፣ አይኑን በጨው አጥቦ ኢትዮጵያ እንዴት በሙስና እንደምትፈራርስ ጋዜጣዊ መግለጫም ይሰጣል። ከጥፋቱ ድፍረቱ። የዚህን አዛውንት የሙስና መረብ ያጋለጠ አንድ ጥናታዊ ጽህፍ ስለ ስብሃት ነጋ ዘረፋ ሌላም የሚነግረን ነገር አለ። ህልቆ መሳፍርት ከሆኑት ዘረፋዎች ጥቂቶቹን ብቻ ለመጥቀስ፤

አድማስ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ባለቤት አቶ ይብራህ፣ የአቶ ስብሃት የአክስት ልጅ ነው። ይህ ሰው ያለ አንድ መነሻ ካፒታል በአዲስ አበባ በሁለት ቦታዎች አድማስ በሚል 16 ካምፓሶች ያሉት ኮሌጅ ከፍቷል። ኮ/ል በላይ ነጋ ደግሞ የአቶ ስብሃት ወንድም ናቸው። እኝህ ሰው ከወንድማቸው ባገኙት የህዝብ ገንዘብ በአዲስ አበባ፣ በመቀሌ እና በዓድዋ የዘመናዊ ፎቅ ባለቤት ለመሆን በቅተዋል። ከዜሮ ተነስተው በብርሃን ፍጥነት የመጠቁት የኮ/ል በላይ ነጋ ሃብት በዚህ አያበቃም። በጋምቤላም የሰፊ እርሻ ቦታ “ኢንቨስተር” በመሆን የሜካናይዝድ ግብርና ኩባንያ ባለሃብት ሆነዋል። እኚህ ቢሊዮነር በቃሊቲም ግዙፍ ኩባንያ ገንብተው ነበር። ግን ምን ያደርጋል ዘረፋውን ገና ሳያጣትሙት ሞት ነጠቃቸው። ነብስ ይማር! አቶ በላይ ነጋ ሲሞቱ፣ ወይዘሮ ቅዱሳን ነጋ ሃብቱን በውርስ ተረክባዋለች። … እንዲህ እያልን ስንዘረዝር ብንወል የዘረፋው ተሳታፊዎች ቁጥር አንድ መጽሃፍ ይሞላል።

ድንቅ ነው። “ኢህአዴግ ሙሰኞችን ካልከሰሰ አገሪቷ ወደ ብተና ማምራቷ አይቀርም!” ይላሉ ስብሃት ነጋ ምንም ሳይሳቀቁ። በልባቸው ግን እየሳቁ!  እኚህ ሰው ስለ ሙስና አስከፊነት የመናገሩን ሞራል ከየት እንዳመጡት እንጃ። ያንን ሁሉ ጉድ በአናታቸው ላይ ተሸክመው እንደው ዝም ቢሉስ ምን አለበት? አበው እንዲህ ይመክራሉ “የምታወጣቸው ቃላት ከዝምታ የተሻሉ መሆናቸውን ስታውቅ ብቻ ተናገር።” አቶ ስብሀት ነጋ በአንድ ወቅት፤ “በኢትዮጵያ በተጨባጭ ያለው ሙስናን ለማጥፋት ፍላጎት እንጂ የፖለቲካ ቁርጠኝነት ብሎ ነገር የለም” ብለውም ነበር። ይህ አባባል ግማሽ እውነታ አለው። በእርግጥ ፍላጎቱም ቁርጠኝነቱም ቢኖር ኖሮ አቦይ ስብሃት ከአይቴ ነጋ ገብረ-እግዚአብሔር ጋር መኖርያቸው በከርቸሌ ይሆን ነበር። አንዳንዴ ጸረ-ሙስና የሚሉት ድርጅታቸውን አፈንጋጮችን (ትናንሽ አሳዎችን) ለመምቻ ይጠቀሙበታል።

“ዶክተር” አቦይ ስብሃት አደባባይ እየወጡ በተናገሩ ቁጥር፣ በሳቸው ሳምባ የሚተነፍሱት ሃይለማርያም ደሳለኝም በ”አይቅርብኝ” አፋቸውን ሞልተው ስለሙስና ይናገራሉ።

እርግጥ ነው። የመንግስታዊ ሌብነቱ ደረጃ ጥግ ላይ ደርሷል። እየዘረፉ ደግሞ ህዝብን ባይገድሉ ምን ነበረበት? ከዘረፋው የከፋ ሌላ ትልቅ ወንጀል አለ። ከህዝቡ ህሊና ከቶውንም ሊጠፋ የማይችል ወንጀል። በቀን እስከ አምስት መቶ ህዝብ የሚገደልበት ወንጀል። በመቶ ሺህ የሚጠጉ ዜጎች በፈረቃ የሚታሰሩበት እና የሚሰቃዩበት ወንጀል።  ዘርፈውም፣ ገድለውም፣ አስረውም መዝለቅ እንደሚችሉ የተማመኑ ይመስላል። ግን ለውጥ የተፈጥሮ ህግ ነውና መምጣቱ አይቀሬ ነው። የግዜ ጉዳይ እንጂ ከፍትህ አያመልጡም።

ግዜ የሰጠው ቅል ድንጋይ ይሰብራል ነውና፣ ግዜው ደርሶ እስኪወድቁ ድረስ እነሆ በ”ማስረጃ የለም!” ዘፈን ይጨፍራሉ።

ክንፉ አሰፋ


“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Left Column

Reader Interactions

Comments

  1. Deregu Temelese says

    January 31, 2017 10:53 am at 10:53 am

    የጎጃም ሀዘን እና አጼ ዮሀንስ የመተማ ዘመቻ
    አጼ ዮሀንስ ደርቦሾችን ልክ ለማስገባት ወደ መተማ ከመዝመታቸው በፊት ጎጃምን ወረው ጦራቸው የህዘቡን ቤቶች አቃጥሏል፣ ሴቶችን ደፍሯል፣ከብቶችን አርዷል፣ ነድቷል፣ የጎጃም ገበሬ በወዙ እና በላቡ ያፈራውን ሀብትና ንብረት በማጣቱ አምርሮ አዝኗል፡፡
    በዚህም ምክንያት የጎጃም ህዝብ ሀዘኑን እንደሚከተለው በስንኝ ቋጥሯል፡፡
    በሰላም ከመጡ ዮሀንስ ከመተማ፣
    ጎጃም ማተብ የለው እግዜርም የለማ፡፡
    ደርቡሾች የጎጃም ህዝብ ሀዘንም ረድቷቸው የአጼ ዮሀንስን ገድለውና አንገት ቆረጠው መውሰዳቸው በታሪክ ተጽፏል፡፡
    ታሪክ ራስን ይደግማል
    የወቅቱ የአጼ ዮሀንስ ልጆች ( ህወሀቶች) ኢትዮጵያውያንን እየገደሉና እየዘረፉ ነው፡፡
    1/ ብአዴን የሚባል ለሆዳቸው ያደሩና ወገናቸውን የካዱ ባንዳዎችን አደራጅተው በቀጥታ ሳይሆን በተዘዋዋሪ እና በረቀቀ መንገድ ጎንደርን እና ጎጃምን እየዘረፉ ነው፡፡ የነገ አገር ገንቢ ወጣቶችንም እየጨፈጨፉ ነው፡፡ ከ2.5 ሚሊዮን በላይ የአማራ ህዝብ በተለያዩ ስልቶች እንደአጠፉ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሳይቀር ተነስቶ ራሳቸውም ተጨቃጭቀወበታል፡፡ ከስልቶቹም መካከል የኤድስ ህሙማንን ከሠራዊቱ ሰብስቦ በብር ሸለቆ በማስፈር፣ ትገሬ የሆኑ የጤና ባለሙያዎችን በአማራ ክልል ገጠሮች በማሰማራት ሴቶች ለህክምና ሲሄዱ መሀን የሚያደርጉ መድሀኒቶችን በመውጋት፣ በበደኖ፣ በወተር፣ በሊማሊሞ፣ በሀረር፣ በባህርዳር በጥይት እና ከእነ ህይወታቸው በመቅበር ገድለዋል፡፡
    2/ የወቅቱ የዮሀንስ ልጆች የጋምቤላን መሬት በኢንቬስትመንት ሰበብ ለመውረር ከ420 በላይ አኝዋኮችን በጠራራ ጸሀይ ገድለዋል ነባር ነዋሪዎችንም አፈናቅለዋል፡፡
    3/ ከ 700 ሺ በላይ ሶማሌዎችን የኦጋዴን ነጻ አውጭ ድርጅትን ትደግፋላችሁ በማለት በተለያዩ ጊዚያት በጅምላ እንደገደሉ ከ800 ሺ ህዝብ በላይ መኖሪያ ቀየውን ጥሎ እንደተፈናቀለ የፌዴራል ፖሊስ አባል ሆኖ ሥርዓቱን ያገለገለው እና የኢሳ ጎሳ ተወላጅ የሆነ ሻለቃ አሊ የተባለ ለአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ በ21/ 04/ 2009 ማጋለጡ እና በ20/05 /2009 ደግሞ የክልሉ ሆድ አደር ባለስልጣን ለማስተባበል መሞከሩ ይታወቃል፡፡ በአጠቃላይ ወያኔ እየተከተለ ያለው የመግደል እና የመዝረፍ ፖሊሲ ሀይ ባይ ያጣ እና ዳፈው ለልጅ ልጅ የሚተርፍ እየሆነ ነው፡፡

    Reply
  2. dergu temelese says

    February 4, 2017 08:27 am at 8:27 am

    Whether called democratic or by any other adjective, nationalism is basically a negative consciousness. It is selfish, isolationist, and destabilizing. It is driven more by resentment or arrogance than love, respect and mutual interest. Amhara nationalism is wrong for Amharas and Ethiopia. Oromo nationalism is wrong for Oromos and Ethiopia. In fact, Ethiopian nationalism is wrong for Ethiopia!

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ጎርጎራ – የመጻዒው ዘመን ሙሽራ! የዉበት ፈርጥ! January 17, 2023 04:18 pm
  • ሁለተኛው መስቀል አደባባይ January 17, 2023 04:13 pm
  • በአቡዳቢ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን January 17, 2023 04:08 pm
  • በንፋስ ስልክ ላፍቶ ስምንት የመሬት ሌቦች ተያዙ January 16, 2023 11:36 am
  • ሺሻ ሲያስጨሱ በተገኙ ሆቴሎችና የምሽት ጭፈራ ቤቶች ላይ እርምጃ ተወሰደ January 16, 2023 08:50 am
  • በሐሰተኛ መታወቂያ የደኅንነት አባል ነን ብለው ሲያጭበረብሩ የነበሩ ተያዙ January 13, 2023 02:03 pm
  • ተሽከርካሪ ወንበር ለትግራይ – “ናይ ኣካል ጉዱኣት ተሽከርካሪ ዘለዎ ወንበር” January 12, 2023 07:17 pm
  • የአማራው ኩራት፣ የኢትዮጵያ ዘብ፣ የትህነግን ቅስም ሰባሪ! January 12, 2023 04:00 pm
  • በኢትዮጵያ ላይ የተጣሉ ማዕቀብ እና ሌሎች አስገዳጅ ሕጎች ሙሉ ለሙሉ ተሰረዙ January 12, 2023 01:52 pm
  • የቻይና ዕዳ ስረዛ “Payday Loan Diplomacy” ወይስ ኢትዮጵያን ያዳነ ተግባር? January 12, 2023 11:00 am
  • የአዲስ አበባ አስተዳደር ከቋንቋ ጋር በተያያዘ ውሳኔ አስተላለፈ January 12, 2023 10:46 am
  • “አምባሳደሩ” የቀድሞ ጌቶቻቸውን እንዲያቋቁሙ ተሾሙ January 11, 2023 03:47 pm
  • መከላከያ ሸኔን የሚዋጉ ሚሊሻዎችን አሠልጥኖ አስመረቀ January 10, 2023 05:37 pm
  • በሰባት ተጠርጣሪዎች ላይ ከባድ የሙስና ወንጀል ክስ ተመሰረተ January 10, 2023 03:36 pm
  • የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አቅጣጫ January 6, 2023 03:26 pm
  • “ከዕብሪቱ አስተንፍሰነዋል” – ኢሳያስ January 2, 2023 07:29 pm
  • [ኢትዮጵያን] “አስታክኮ ኤርትራን መውጋት ለሚፈልግ ኃይል አንተባበርም” January 2, 2023 07:11 pm
  • የ፰ ወር ሕጻንና ጨቅላ ወንዶች የሚደፈሩባት ትግራይ December 14, 2022 02:49 pm
  • “ሰውን ለመርዳት ሰው መሆን ብቻ በቂ ነው” የደጎች አውራ የመቄዶኒያው ቢንያም በለጠ December 14, 2022 09:59 am
  • “የሀብት ምዝገባ መረጃው ለሕዝብ ክፍት ይደረግ “ December 13, 2022 10:30 am
  • የኢትዮጵያ ዓለምአቀፋዊ የሌብነት ደረጃ December 13, 2022 09:42 am
  • ለብረት አቅላጮች ለመሸጥ በኤሌክትሪክ የብረት ማማዎች ስርቆት የ100 ሚሊዮን ብር ኪሳራ December 13, 2022 09:26 am
  • በትግራይ የሰላም ስምምነቱን መሠረት ያደረገ የሽግግር ፍትሕ እንደሚፈጸም ተገለጸ December 13, 2022 09:20 am
  • ከ30 ሚሊየን ብር በላይ በሚሆን ሌብነት የተከሰሱት የደኅንነት መ/ቤት ሠራተኞች ክስ ተመሰረተ December 13, 2022 09:06 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2023 · Goolgule