• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ጠቅላይ ሚኒስትሩን ከራሳቸው ማዳን!

April 29, 2018 11:40 am by Editor Leave a Comment

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ ተስፋን-በጥንቃቄ (cautious optimism) ካነገቡት ሰዎች አንዱ ነኝ። የተስፋዬ መሠረቶች ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደ ሥልጣን የመጡበት መንገድ፣ የገቧቸው ቃልኪዳኖች እና አሁን የታየው መረጋጋት ናቸው። አሁን የታየው መረጋጋት ስል የቄሮዎች የአደባባይ ተቃውሞ መቆሙን ማለቴ አይደለም። ተቃዋሚዎችን እያሳደዱ መከታተል፣ ማዋከብ እና ማሰር ርቀን ሳንሔድ አምና ከነበረው አንፃር እንኳ ልዩነቱ የትየለሌ ነው። ለዚህ የራሴን ስሜት እና ተሞክሮ ነው በምሳሌነት የማቀርበው። በፊትም አሁንም ሐሳቤን በነጻነት እገልጻለሁ። ነገር ግን አምና እና ካቻምና ከያንዳንዱ ጽሑፎቼ/ንግግሮቼ ቀጥሎ እስር ይመጣል እያልኩ እየሰጋሁ ነበር የማደርገው። አሁን ምን ያክል ይዘልቃል የሚለው ቢያሰጋኝም እታሰራለሁ እያልኩ በየደቂቃው አልባትትም። በፊት ሲያስሩ፣ ሲያዋክቡ እና ሲከስሱ ከነበሩት አንዳንድ ኃላፊዎችም ጋር ባጋጣሚዎች አውርቻለሁ። ከላይ ለውጥ ያለ ሲመስል እነርሱም ከታች ይለወጣሉ። አንድ ከፍተኛ የፌዴራል ፖሊስ ኃላፊ የኛን እንቅስቃሴ “የበፊቱ አመራር እንደ ወንጀል ያየው ስለነበር ወንጀል ነበር። አሁን ግን እንደወንጀል አይታይም” ብለውኛል። ይህ ከሁሉም በላይ ደግሞ ሰዎች ላይ የተፈጠረው የ”ለውጥ መጥቷል” ስሜት እና የፍርሐት ማጣት ከተጠቀሙበት ለጠቅላይ ሚኒስትሩም ትልቅ ዕድል ነው። ሌላው ሌላው ሁሉ ለዘለቄታው ለመቅረፍ ረዥም የፖለቲካ እና የሥራ ባሕል አብዮት የሚፈልግ ፈርጀ ብዙ የሁላችንም ችግር ነው።

አሁን ስጋቴ ከግዜ ጋር የሚደረገው ፉክክር ነው። ጊዜ መጨቆኛ መዋቅሩን ለተቆጣጠሩት ጨቋኞችም፣ ባዶ እጃቸውን ለገጠሟቸው ተጨቋኞችም ዕኩል ነው የሚነጉደው። ማርቲን ሉተር ኪንግ (ትንሹ) “ጊዜ ከደጋጎች ይልቅ ክፉዎቹ የተሻለ የሚጠቀሙበት ይመስለኛል” ብሎ ጽፎ ነበር። ለዚህ ነው ማንም መጣ ሔደ ለመሪዎች ለውጥ ማስኬጃ በሚል ሰበብ አላግባብ ጊዜ መሸለም የማያስፈልገው። እውነተኛው ለውጥ በተቋማት ለውጥ እንጂ በሰዎች ለውጥ አይመጣምና!

የጠቅላይ ሚኒስትሩ ትልቁ ተልዕኮ የ2012ቱ የኢትዮጵያ አገር ዐቀፍ ምርጫ ነጻ እና ርትዓዊ እንዲሆን ማድረግ ነው ብዬ አምናለሁ። ነገር ግን ይህን “ብዙ መጠበቅ” ነው ብለውታል የኢትዮጵያን ጉዳይ በመተንተን የሚታወቁት ፈረንሳዊው ሬኒ ሊኾርት። እሳቸው እንደሚሉት ኢሕአዴግ የውስጥ ልዩነቱን ፈትቶ ሠላም ካላላገኘ፣ አገሪቱም ሠላም አታገኝም። ተረኩ የፓርቲውን መበተን ከኢትዮጵያ መበተን ጋር የሚያስተካክል ነው። የፓርቲው አባላት ሁሉንም ክልላዊ መዋቅሮች በተቆጣጠሩበት እንዲሁም አማራጭ የተደራጁ ኃይሎች በሌሉበት ሁኔታ ይህ አይሆንም የሚባል አይደለም። ነገር ግን ይህ የኢሕአዴግ ውስጣዊ ክፍፍል ተቀርፎ የሥልጣን መደላድል ከመጣ ሁሉም ነገር ወደነበረበት የጭቆና አዙሪት ይመለሳል የሚል ስጋት አለኝ።

የጠ/ሚኒስትሩ የሥልጣን ምንጭ ምንድን ነው?

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ በኢሕአዴግ ውስጥ የተቃዋሚውን ቋንቋ በመናገር ነው ለሥልጣን የበቁት። በዝግ ስብሰባቸው ምን እንደተመከረ፣ ምን ዓይነት የማመቻመቻ ድርድር/ቃልኪዳን አድርገው አብላጫ ድምፅ ለማግኘት እንደቻሉ አናውቅም። ዞሮ ዞሮ መርጠው ለዚህ ያበቋቸው የኢሕአዴግ አባላት ናቸው። የቀድሞውን ጠቅላይ ሚኒስትር (ኃይለማርያም ደሳለኝ) ያለግዜያቸው እንዲለቁ፣ እሳቸውም ከኢሕአዴግ ባፈነገጠ አካሔድ የኢሕአዴግን ሥልጣን እንዲቆናጠጡ ያደረጋቸው ሕዝባዊ ተቃውሞ ነው። ስለዚህ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የሥልጣን ምንጭ ኢሕአዴግ እና ሕዝባዊ ተቃውሞዎች በጣምራ ነው።  ይህ በሥልጣን ዘመናቸው ሊሠሩ የሚችሉትን ማመላከቻ ነው። በርግጠኝነት ኢሕአዴግን ማፍረስ አይፈልጉም፤ ምናልባት ማደስ ግን ይፈልጋሉ። በምን ዓይነት መንገድ? ምናልባትም ሕዝባዊ ጥያቄዎችን በመመለስ። ተቃርኖው የሚጀምረው እዚህ ጋር ነው።

የኢሕአዴግ (አብዮታዊ ዴሞክራሲ) ትልቁ ችግር ሕዝባዊ ጥያቄዎችን በራሱ አውጥቶ፣ መልሱንም በራሱ መንገድ መስጠት ነው።  ዴሞክራሲ ደግሞ በተቃራኒው ሕዝብ ችግሩን እንዲናገር በመፍቀድ እና ችግሩን በመቀበል፣ መፍትሔው ከሕዝቡ ፍላጎት አኳያ እንዲመለስ ማድረግ ነው። ይህ ሕዝባዊ ቅቡልነት የሚያስገኝ አሠራር ግን የኢሕአዴግን ሕልውና አደጋ ላይ ሊጥልበት ይችላል። ስለዚህ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በልባቸው የያዙት፣ በቅንነት የተመራ የለውጥ ፍላጎት ካለ ይህንን ፈተና ለመጋፈጥ መዘጋጀት አለባቸው። የሕዝብ ጥያቄዎች መልስ ማግኘት ያለባቸው መልሶቹ ኢሕአዴግን ወደመቃብር የሚልኩት ቢሆንም እንኳን ነው። ይህ ግን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢስማሙባቸው እንኳ በዝግ መክረው ለመረጧቸው የኢሕአዴግ አባላት የሚያስማማቸው ይመስላችኋል? እኔን ያጠራጥረኛል።

በ2012 ነጻ እና ርትዓዊ ምርጫ ለማድረግ ከሚያስፈልጉት ነገሮች ውስጥ ዋነኛው ሜዳውን ለሁሉም ዕኩል ማደላደል እና ሁሉንም አካላት ማሳተፍ ነው። በርግጥ ምርጫ ቦርድ ያለበትን አድሎ ቀርፎ፣ ለማንም ወገንተኛ ባልሆኑና ልምዱና የትምህርት ዝግጅቱ ባላቸው ሰዎች ቢመራ አንድ ነገር ነው። ነገር ግን የፖሊስ እና ደኅንነት አካላት (ከሥልጣን ያዥው ውጪ ያሉት) ተወዳዳሪ ፓርቲዎች እና መራጮችን ማዋከብ ማቆም አለባቸው። የተሰደዱ ፖለቲከኞች እና የፖለቲካ ድርጅቶችም ተስፋ አስቆርጦ ያሰደዳቸው እና ነፍጥ ያስነሳቸው መንስዔ ተቀርፎ ወደ አገር ቤት እንዲመለሱ ዋስትና መስጠት የግድ ነው። ይህንን ለማድረግ በአንድ ወገን “ሁሉን ዐቀፍ ድርድር መደረግ አለበት” የሚል ሙግት አለ። የዚህ ሙግት ዋነኛ አራማጅ በቅርቡ ከእስር የተፈታው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ነው። በሌላ በኩል “ድርድሩ የግድ አያስፈልግም” የሚሉም ወገኖች አሉ። ለምሳሌ ፖለቲከኛው ግርማ ሰይፉ ጋር በአንድ ጫወታችን መሐል ‘ተቃዋሚው ከኢሕአዴግ ጋር የግድ መደራደር የለበትም። ኢሕአዴግ መንግሥታዊ ኃላፊነቱን ተወጥቶ ለነጻ ውድድር የምርጫ ሜዳውን በሐቅ ካመቻቸለት ከዚያ በኋላ ያለው የተቃዋሚው ሥራ ነው’። እርግጥ አሁን ከውስጥም ከውጭም ያለው ግፊት ከፊል ፍሬ አፍርቶ፣ “ለውጥ አይመጣም” ከሚል ድፍንፍን ያለ ግዜ “ምን ዓይነት ለውጥ ይመጣ ይሆን?” ወደሚል ጉጉት ተሸጋግረናል። ይህንን የለውጥ ተስፋ ወደ ተግባር እንዲለወጥ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ ብዙ ይጠበቃል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ አሁን ባለው የተዝናና ሁኔታ ለቀጣዩ ምርጫ አገሪቷን ቢያዘጋጁ አገር ውስጥ ያሉ ተቃዋሚዎች አፈር ከላሱበት ተነስተው በውስጣዊ ወጀብ የሚሰቃየውን ኢሕአዴግ መፈተናቸው አይቀሬ ነው። ፈተናው ኢሕአዴግን ወደለመደው ጫወታ የመመለስ ዕድሉም እንዲሁ ሰፊ ነው። ምናልባት አቶ ዐብይ አሕመድ፣ አቶ ለማ መገርሳና ጥቂት የለውጥ ፊቶች በምርጫ ክልላቸው በብልጫ ያሸንፉ ይሆናል። ነገር ግን በሌሎቹ የምርጫ ክልሎች ውስጥ ሕዝቡ ላይ ግፍ ሲያደርሱ የነበሩ የኦሕዴድ ካድሬዎች ለሕዝቡ ጥቅም ሲታሰሩ ሲፈቱ የከረሙትን የኦፌኮ አባላትን አያሸንፉም። ከኦሮምያ ውጪም ተመሳሳይ ሁኔታ ይኖራል። ኢሕአዴግ ይህን ፈታኝ ሁኔታ በተለመደው የማዋከብ፣ የማሳደድ እና የማሰር ስልት ለመጋፈጥ የሞከረ ዕለት ደግሞ የተካበው ተስፋ ሁሉ ይናዳል። ጫወታው ፈረሰ፤ ዳቦው ተቆረሰ!

በአንድ ወቅት ከሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ የሺዋስ አሰፋ ጋር ቃለ ምልልስ ሳደርግ፣ “ኢትዮጵያን የሚያተራምሳት ዴሞክራሲ ማጣት አይደለም፤ የዴሞክራሲ ተስፋ ማጣት ነው” ብሎኝ ነበር። እውነትም የዛሬውን አገራዊ መረጋጋት ስንመለከተው በተስፋ ላይ የቆመ መረጋጋት ነው። የዚህ ተስፋ መፍረስ፣ የሚያፈርሰው ብዙ ነገር ነው።

በሥልጣን መጫወት፣ በእሳት መጫወት!

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሐቀኛ የለውጥ ፍላጎት ካላቸው፣ ‘ይህ በኔ ዘመን አይከሰትም’ ብለው ሊያስቡ ይችላሉ። ይህ ግን የሰውን ራስ ወዳድ ተፈጥሮ እንዲሁም የሥልጣንን አባላጊነት ካለመረዳት የሚመነጭ ነው። ብዙዎቹ የዓለማችን አምባገነኖች በአንድ ወቅት ሐቀኛ የለውጥ አርበኞች ነበሩ። አንዴ የሥልጣን መደላደል ከፈጠሩ በኋላ ግን በምናባቸው በሚፈጥሩት “የለውጡ ጠባቂነት” ሚናቸው ተሸፍነው ከቀዳሚዎቻቸው የበለጠ ጉዳት ያደርሳሉ። ብዙዎቹ የለውጥ አርበኞች የመጣው ለውጥ እንዳይቀለበስ በሚል ሰበብ አስባብ ለረዥም ግዜ ሥልጣን ላይ ይከርማሉ፣ የሚያምኗቸውን ሰዎች ብቻ መርጠው ቁልፍ ቦታ ላይ ይሾማሉ፣ የለውጥ ሒደታቸውን የተቃወሙትን ‘አድኀሪያን’ በፈርጣማ ጡንቻዎቻቸው ይጨፈልቃሉ፣ በመጨረሻም ‘ለውጥ’ የሚሉት የራሳቸውን ሥልጣን ተቆናጦ መቆየት ብቻ እስኪመስል ድረስ ፈላጭ ቆራጭ ይሆናሉ – በአጭሩ አምባገነን ይሆናሉ። ከለውጥ አምጪነት፣ መለወጥ ያለበት አካል ወደ መሆን ይሸጋገራሉ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ ለውጪያዊ መረጋጋት እና ለውስጣዊ መስማማት ግዜ ባገኙ ቁጥር፣ ሰው ናቸውና በሥልጣን የመበላሸት ዕድላቸውም ሰፊ ነው የሚሆነው። የሥልጣን መደላደል “ከእኔ ወዲያ ላሳር” ወደሚል ትምክህት ይመራቸዋል። ስለዚህ ከላይ “አሁን ያለው የተዝናና ሁኔታ” ያልኩት በእርሳቸው ይሁንታ ብቻ የመጣው መልካም ጊዜ ለፈተና ግዜ አይፀናም። ሹመኞች በጭንቅ ግዜ የማይገቡት ቃል የለም። ዕውቁ ፖለቲከኛ አንዷ-ዓለም አራጌ “we are victims of broken promises” (‘እኛ የተከዱ ቃልኪዳኖች ሰለባ ነን’) ያለው በጭንቅ ግዜ የተገቡ ቃል ኪዳኖች፣ በመረጋጋት ግዜ ስለሚዘነጉ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለገቧቸው ቃልኪዳኖች ማስተማመኛ አስቸኳይ ሕጋዊ ዋስትና ይስጡ። የሚሻሩት ዐዋጆች አሁኑኑ ይሻሩ፣ የሚሻሻሉት ዐዋጆች አሁኑኑ ይሻሻሉ፣ የሚጨመሩት ድንጋጌዎች አሁኑኑ ይጨመሩ… የተቋማት ገለልተኝነት ሥራ መሠረቶች አሁኑኑ ይጣሉ… ለቀጣዩ ምርጫ ያለው መሰናዶ በሕግ እና ተቋማዊ አግባብ በአስቸኳይ ይፈፀሙ። የፖለቲካ ዕርቅ ጥሪዎች በነቢብ ሳይሆን በገቢር ይደረጉ።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ እነዚህን ነገሮች በማለዳ ማድረግ ከቻሉ ብዙዎቹ ለውጥ-ፈላጊ የዓለማችን ሰዎች ከወደቁበት ገደል ይተርፋሉ። ሥማቸውም “ከአብዮት ከዳተኞች” ተርታ ሳይሆን፣ ምናልባትም ከዘመን ባንዴ ብቻ ከተከሰቱት “ከጨቋኞች መሐል የወጡ የነጻነት ፋና ወጊዎች” – ከእነ ፍሬድሪክ ደ ክላርክ ተርታ ይመደባሉ። ምርጫው የእርሳቸው ነው፤ ራስን ከራስ ማዳን ወይም በሥልጣን መጫወት።

በፍቃዱ ዘ. ኃይሉ

ምንጭ፤ የበፍቄ ዓለም The Q Perspective

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Uncategorized Tagged With: abiy, Ethiopia, Full Width Top, Middle Column

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am
  • ከትግራይ ሾልኮ የወጣው ምሥጢራዊው ሰነድ ምንድነው? May 20, 2025 09:18 am
  • በደቡብ ጎንደር በጸዳሉ ደሴ የተመሩት 72 ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ May 19, 2025 02:24 pm
  • የተመሠረተው የፋኖ አደረጃጀት ዋነኛ ዓላማው ድርድር መሆኑ ተነገረ May 14, 2025 11:07 pm
  • ከፍተኛ የፋኖ አመራሮች መገደላቸው ተነገረ May 6, 2025 10:40 pm
  • ሃይማኖትን ለተራ የፖለቲካ ሸቀጥ ማዋል ውርደት ነው April 24, 2025 12:43 am
  •  የኬሪያ ኢብራሒም ኑዛዜ “ብትንትናችን ወጥቷል” April 22, 2025 12:08 am
  • ለወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞን አመራሮች ወታደራዊ ሥልጠና ተሰጠ April 16, 2025 11:44 pm
  • ዓቅም እንደሌለው የገመገመው ሻዕቢያ ፊቱን ከጦርነት ወደ ዲፕሎማሲ እያዞረ ነው   April 15, 2025 12:32 am
  • “አንድ የፋኖ ተቋም (የእስክንድር) ተመሥርቷል፤ ሌሎቹ ደግሞ እንዲሁ አንድ ተቋም መሥርተው ወደዚህ ይመጡ” አበበ ጢሞ April 11, 2025 12:07 am
  • መለስ (ለገሰ) ዜናዊ – ተዋርዶ ያዋረደን! April 9, 2025 10:28 pm
  • የተከዜ ዘብ: የሉዓላዊነት መጠበቂያ April 8, 2025 11:49 pm
  • አዲስ አበባ አስተዳደር የሪፖርተርን የተዛባ መረጃ ኮነነ፤ ሕጋዊ እርምጃ እወስዳለሁ አለ April 8, 2025 10:06 pm
  • ሀሰተኛውን የሪፖርተር ዘገባ ንግድ ባንክ በጽኑ ተቃወመ፤ እርማትም ጠየቀ April 8, 2025 09:48 pm
  • “ኦሮሚያ ላይ ወይም ሌላ ቦታ ላይ ስታደርገው ከነበረ ትግራይ ወስጥም የማታደርግበት ምንም ምክንያት አይኖርህም” ነው ጌታቸው ረዳ April 7, 2025 10:22 pm
  • “TPLF’s belief in a strong federal government was always tied to its own dominance in Addis Ababa” April 7, 2025 10:15 pm
  • Counter-Video by EBC Challenges EBS Broadcast, Sparks Public Outcry Over Alleged Misinformation March 31, 2025 02:36 am
  • የኤሊያስ መሠረትን ፌክ መረጃ ማን ያጋልጥ? February 19, 2025 06:00 pm
  • አዘርባጃን፡ የሻዕቢያን ሸምቀቆ ማጥበቂያ?! February 19, 2025 12:29 am
  • የአሜሪካ ድምፅ/ቪኦኤ ይዘጋ ተባለ  February 12, 2025 03:37 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule