• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

መርዝ ከውጭ ይረጫል ወይም ከውስጥ ይመነጫል

February 22, 2013 09:37 pm by Editor 3 Comments

በአለፉት ሠላሳ አምስት ዓመታት ኢትዮጵያ ችግሮችን መፈልፈያ መሣሪያ ሆናለች፤ ለብዙ ምዕተ-ዓመታት ይዘናቸው (ምናልባትም አቅፈናቸው ማለት ይሻል ይሆናል) ስንንከባለል የቆዩ ችግሮች ሞልተውናል፤ እያሰብን እነዚያን የቆዩ ችግሮቻችንን በመፍታት ፋንታ ሌሎች አዳዲስ ችግሮችን እየፈለፈልን የተቆላለፉና የተወሳሰቡ፣ ውላቸው የጠፋ ችግሮችን ፈጥረናል፤ እየፈጠርንም ነው፤ አሁን በመፈጠር ላይ ያለው አዲስ ችግር እስላማዊ መንግሥት በኢትዮጵያ የሚል ነው፤ እስቲ እንመልከተው፡፡

(Photo: mesfinwoldemariam.wordpress.com)

በሩቁ እንጀምር፤ እስላማዊ መንግሥታት ያቋቋሙ አገሮች አሉ፤ አንዳቸውም ሰላም የላቸውም፤ እስላማዊ ቡድኖች በምርጫ አሸንፈው ሥልጣን የያዙ አሉ፤ ለምሳሌ በቅርቡ በአረብ አገሮች በተጀመረው የፖሊቲካ እድገት ለውጥ በቱኒስያና በግብጽ እስላማዊ ቡድኖች አሸንፈው ሥልጣን ይዘዋል፤ በዚህም ምክንያት በቱኒስያና በግብጽ የለውጥ ጥያቄ አገርሽቶ አንደገና ሰዎች እየሞቱ ነው፤ በነዚህና በሌሎችም አገሮች የሚገኙት ወጣቶች የሚፈልጉት የሰው ልጆች ሁሉ መብቶች የሚከበሩባቸውና በሙሉ የግለሰብ ነጻነት የተረጋገጡባቸው አገሮች እንዲኖራቸውና በእኩልነት ኩሩ ዜጎች ሆነው እንዲኖሩ ነው፤ የአንድ አገር ዜጎች የተለያየ ዘር፣ የተለያየ የቆዳ ቀለም፣ የተለያየ ቁመትና ውፍረት፣ የተለያየ ጾታና ዕድሜ፣ የተለያየ ቋንቋ፣ የተለያየ ሃይማኖት፣ የተለያየ የፖሊቲካ አመለካከት፣ የተለያየ ትምህርት፣ የተለያየ ሙያና የተለያየ ገቢ ሊኖራቸው ይችላል፤ የጋራ ማንነታቸው ዜግነት ነው፤ እኩልነታቸው በዜግነታቸው ነው፤ አንድነታቸው በዜግነታቸው ነው፤ እኩልነታቸውንና አንድነታቸውን የሚያረጋግጥላቸውና ሚዛኑን የሚጠብቅላቸው ከበላይ ሆኖ ሁሉንም የሚገዛው ሕግ ነው፡፡

በቡድን ወይም በጅምላ የሚያስቡ ሰዎች የሕግን ባሕርይ አያውቁትም፤ ‹‹ክርስቲያኖች እስላሞችን እንጨርሳለን›› አሉ፤ ወይም እስላሞች ክርስቲያኖችን እንጨርሳለን›› አሉ፤ በሚል አሉባልታ ላይ ክስ ተመሥርቶ ሕጋዊ ፍርድ መጠበቅ አይቻልም፤ በየትም ሆነ በማንኛውም ጊዜ ጽንፈኛ እምነትና አስተሳሰብ ያላቸው ሰዎች ይገኛሉ፤ እነዚህ ግለሰቦች ሕልማቸውንም ሆነ ቅዠታቸውን በስውርም ሆነ በአደባባይ ይገልጻሉ፤ ለምሳሌ በአሜሪካ ጥቁሮችንና ይሁዲዎችን ከአገሩ ጠራርገን እናወጣና ንጹሕ የነጮች አገር እንፈጥራለን የሚሉ ግለሰቦች አሉ፤ ይህ እምነት ለአሜሪካ ማኅበረሰብ መርዝ ነው፤ አሜሪካ የነጻነት አገር ነው፤ የነጭ ዘረኞቹ መርዛቸውን ለመንዛት መብት አላቸው፤ የዘረኞቹን መብት ለማፈን የሚወሰድ የጡንቻ እርምጃ ሁሉ አሜሪካ የነጻነት አገር መሆኑን ይሽራል፤ ከዚያም በላይ የአሜሪካ መንግሥት በሚከተለው ዘዴ ከነጭ ዘረኞቹ የተሻለ አይሆንም ነበር፤ ስለዚህም ነጭ ዘረኞችን ለመቋቋም የሚወሰደው አርምጃ አሜሪካ የነጻነት አገር መሆኑን ሳይሽርና ነጭ ዘረኞቹም እምነታቸውን የመግለጽ መብታቸው ሳይደፈጠጥ መሆን አለበት፤ የነጻነት ትርጉሙ ይህ ብቻ ነው፡፡

በሥልጣን ወንበር ላይ ስለተቀመጡ ብቻ አንድ ዓይነት የፖሊቲካ እምነት ብቻ ይዞ ሌላውን መደፍጠጥ፣ መንግሥት የባረከውን አንድ ዓይነት የኦርቶዶከስ ሃይማኖት ብቻ ማደርጀትና ሌላውን ማፈን፣ መንግሥት የባረከውን አንድ ዓይነት የእስልምና ሃይማኖት ብቻ ማደርጀትና ሌላውን ማፈን ልማድና የአሠራር ባህል እየሆነ ሲሄድ ሁሉንም ነገር አንድ ዓይነት ብቻ ለማድረግ የሚታየው ጥረት የኢትዮጵያን ጉራማይሌ ባሕርይ የሚቃረን በመሆኑ ስር አይኖረውም፤ ይህ ሁሉም ሰው ሊያስብበት የሚገባው አንዱ ነገር ነው፤ ሁለተኛው አንድ ወይም ጥቂት ሰዎች በኢትዮጵያ ውስጥ እስላማዊ መንግሥት እናቋቁማለን ቢሉ አገር የሚሸበርበት ምንም ምክንያት የለም፤ ኢትዮጵያን የኦርቶዶክስ ክርስቲያን አገር ለማድረግ የሚመኙም አሉ፤ ኢትዮጵያን ሃይማኖት-አልባ የጉግማንጉግ አገር ለማድረግ የሚፈልጉ አሉ፤ ኢትዮጵያ በአንድ አጋጣሚ ወንበሩ ላይ የወጣ ጉልበተኛ የሚያትምባትን እምነትም ሆነ ሃይማኖት የማትቀበል አገር መሆንዋ ተደጋግሞ የታየ ነው፤ ኢትዮጵያን የይሁዲ አገር ለማድረግ ተሞክሮአል፤ ኢትዮጵያን የክርስቲያን አገር ለማድረግም ተሞክሮአል፤ ኢትዮጵያን የእስላም አገር ለማድረግም ተሞክሮአል፤ ሁሉም አልሆነም፤ ኢትዮጵያ የሁሉም አገር ሆና ዘልቃለች፤ ይህንን በማክሸፍ ለማንም ምንም ጥቅም አይገኝም፤ በአንጻሩ ደግሞ የሥልጣን ወንበሩ ላይ የወጡ ጉልበተኞች ሁሉ የኢትዮጵያ ሕዝብ በጉጉት የሚጠብቀውን የነጻነት ጮራ እያዳፈኑ የነጻነትን፣ የእኩልነትንና የሕግ የበላይነትን ዓላማ ለማክሸፍ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እየቀጠለ ነው፡፡

የነጻነትና የሕጋዊነት መክሸፍ የሰላም ጠንቅ ነው፤ የሰላም መክሸፍ የልማት ጠንቅ ነው፤ የልማት መክሸፍ ደሀነት ነው፤ ደሀነት የሞት አፋፍ ነው፤ ይህንን ለመገንዘብ የሚያዳግተው ሃያ አንድ ዓመት የሞላው ሰው አለ? ኢትዮጵያን ለመምራት የሚደናበሩት ሰዎች ሁሉ ሃያ አንድ ዓመት አልፎአቸዋል፤ ነገር ግን ከላይ የተገለጸው የመክሸፍ ጉዞ ጭራሽ አይታያቸውም፤የሚታየውም ሲነግራቸው የተበለጡ ስለሚመስላቸው አይሰሙትም፤ ስለዚህም የሚታየውን ሳያዩ፣ የሚሰማውን ሳይሰሙ ጊዜ የሚበላውን ጉልበታቸውን ብቻ ተማምነው በጭፍን እንምራችሁ የሚሉትን ተከትለን ለእኛ በሚታየንና ለእነሱ በተሰወረባቸው ገደል ውስጥ ለምን አብረን እንግባ? አብረን ገደል በመግባት አንድነታችንን የምንጠብቅ የሚመስላቸው ሰዎች በሁለት በኩል ይሳሳታሉ፤ አንደኛ ከአገዛዙ መሪዎች ዘንድ የሎሌ ተከታይነትን እንጂ የአኩልነት አንድነትን አያገኙም፤ እኩልነት በሌለበት አንድነት አይፈጠርም፤ ሁለተኛ ወደገደል የሚጨምር አንድነትን መምረጥ ሕይወትን ትቶ ሞትን መምረጥ ነው፡፡

በሃያ አንድ ዓመት ውስጥ መክተፍ-መከታተፍ ሙያ ሆነ፤ ብዙ ሰዎችና ድርጅቶች ሠለጠኑበት፤ መክተፍ-መከታተፍ አብሮ የመኖር ጸር ነው፤ አብሮ የመኖር ጸር የሚሆነው በፍቅር ፋንታ ጥላቻን፣ በሰላም ፋንታ ጠብን፣ በመረዳዳት ፋንታ መጋጨትን፣ በልማት ፋንታ ጦርነትን በመንዛት ነው፤ አንዳንድ ቋንቋ ተናጋሪዎችን በግልጽም ሆነ በስውር እንደጠላት መቁጠርና በእነሱ ላይ ቂምን እንዲቋጥሩ ማድረጉ የማንንም የፖሊቲካ ቡድን፣ የኢትዮጵያን ሕዝብም ይጎዳል እንጂ አይረዳም፡፡

አሁን ደግሞ በአንድ በኩል በኦርቶዶክስ ሃይማኖት ላይ በየገዳማቱና ላይ እየደረሰ ያለው ጥቃትና በሊቀ ጳጳሳት ምርጫው ላይ አገዛዙ እያሳየ ያለው ጣልቃ-ገብነት የኦርቶዶክስ ሃይማኖት ተከታዮችን እያስቀየመና እያስኮረፈ ነው፤ በሌላ በኩል በእስልምና ሃይማኖት ላይም የሚታየውን ጣልቃ-ገብነት ተከታዮቹ ፍጹም ሰላማዊ በሆነ መንገድ በርትተው በመቋቋማቸው እየደረሰባቸው ያለው ግፍ ለጆሮ እየቀፈፈና በጣም አሳፋሪ እየሆነ ነው፡፡

ይህ በሃይማኖቶች ላይ የተጀመረው ዘመቻ ውጤት ይኖረዋል፤ ውጤቱ በአገዛዙ የውስጥም ሆነ የውጭ አመራሩ ላይ ከባድ ተጽእኖ ይኖረዋል፤ የሃይማኖቶቹ ጉዳይ እንደጎሣዎች መከታተፍ በኑሮ ላይ ብቻ ጫናውን የሚያሳርፍና በምድር የሚንከላወስ አይደለም፤ ወደሰማይ ያርጋል፤ የሰማይ ሠራዊትን ይጠራል፤ ያንን ኃይል እንኳን የኢትዮጵያ የጦር ኃይልና የአሜሪካውም አይችለውም፤ ዓይን ያለው ያያል፤ ጆሮ ያለው ይሰማል፤ ልብ ያለው ያስተውላል፤ ዶላር ነፍስን አይገዛም፤ ክብርን አይገዛም፤ ወዳጅንም አይገዛም፡፡

ፕ/ር መስፍን ወልደ ማርያም፤ የካቲት 2005

ምንጭ: Mesfin Woldemariam Blog

Filed Under: Opinions Tagged With: Full Width Top, Middle Column

Reader Interactions

Comments

  1. Lila says

    February 23, 2013 08:00 am at 8:00 am

    በእውነት እንደታላቅ ወንድም ጋሽዬ፤ እንደአባትም አባብዬ፤ እንደምሁርም ፕሮፌሰር ብልህ የማላፍርብህ የእድሜ ጸጋውን ሰጥቶህ እኔ ላለሁበት ዘመን ላደረሰህ ጋሽ መሥፍን፤ አጠር አጠር ባሉ ቃላት ነገር ግን የረጅሙን የ100 ዓመታትን ታሪክ ቅልብጭ አድርገህ እንደፊልም ትእይንት አሳየኸኝ። ዛሬ ላይ አብረኸን ስላለህ የድካምህን ዋጋ ሳናውቀው የተረት ልጆች ሆነን ተረት ብቻ ከኅሊናችን ተከትቦ ድካምህ ባይታየንም ምሁር ካለፈ በኋላ እንደለመድነው ሁሉ ኖረንበት ያልተቀበለውን ሙያና ክብር ለማንገስ እንደሩጫችን ለወሬ የሚቀድመን እንደሌለ ያለፈው ኋላችን ይመሰክርብናል። ጋሼ መሥፍን የምሁርነት ጥግ ግድግዳ ላይ በሚሰቀል የድግሪ ባጅ እንዳማይለካ በአንተ አይተናል። ብዙ ወዳጅ እንዳፈራህ ሁሉ፤ ጠላቶችንም ያፈላብህ ያንን በዘመናት ጥረት ያካበትከውን ማእረግ ከግድግዳ ላይ ሰቅለህ እዚህ አስኳላ ገብቼ እንዲህ ተሸልሜ እያልክ እንደሱቅ በደረቴ ለዝና ሽያጭ ሳታቀርብ ብእርህን መዝዘህ በወረቀት ሰሌዳ ላይ ሻጥ እያደረግህ ስለምትወጋቸው እንጂ አንተ ከእነሱ የከፋ ሰው ሆነህ አይደለም። ፈጣሪ ደጉ የማይሰጡህን እድሜ ቸሮህ የኑሮ መጽሐፋችን ሆነህ እነሆ እናነብሃለን። እድሜና ጤና እግዚአብሔር ይስጥህ። የማታውቀኝ የማውቅህ የዚህ ዘመን ልጅ ነኝ!!!!!

    Reply
  2. koster says

    February 23, 2013 07:06 pm at 7:06 pm

    I hope woyane ethnic fascists will read and try to get rid of their arrogance and come to their senses before it is too late. Woyane ethnic fascists might think that they are mighty but they cannot kill all Amharas or Oromos it is a matter of time they will scramble like the Republican guard of Saddam Hussien or that of DERG. Ethnic and religious unity is a great nightmare for woyane ethnic fascists. 21 years of rule/misrule by cheating and terrorizing should be stopped.

    Reply
  3. inkopa says

    February 24, 2013 11:00 pm at 11:00 pm

    One of few precious lights in the darkness.
    May God keep you and bless you.

    Golguls thank you .

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

Recent Posts

  • ለሱዳንና ኤርትራ ሲከራከሩ የነበሩት አበባው ባለመመረጣቸው “በጣም ተድጃለሁ” አሉ June 26, 2026 12:29 am
  • “ትህነግ ወደ ዓለምአቀፍ ወንጀለኛነትና አሸባሪነት እየተምዘገዘገ ነው” June 25, 2026 01:00 am
  • አሜሪካ በሕገወጡ ትህነግ አመራሮች ላይ ጠንካራ የቪዛ እገዳ ጣለ June 18, 2026 10:29 am
  • እንደ ሌሊት ወፏ የሚንቀሳቀሰው ኢህአፓ/ትብብር   June 18, 2026 09:36 am
  • የታርጋ ጫጫታ June 15, 2026 05:16 pm
  • ፋንታኹን ዋቄ ከአሜሪካ የሃይማኖት እልቂት አወጁ June 15, 2026 02:12 am
  • ሕገወጡ ትህነግ ወጣቶችን ለዳግም ዕልቂት እያሰናዳ ለፈረንጆች “ኢትዮጵያን አውግዙልኝ” እያለ ነው June 11, 2026 12:57 am
  • በሐዘንና ግልፅ ደብዳቤ ስም የተሸፈነ የድህረ ምርጫ ሀገር የማተራመስ ስትራቴጂ June 10, 2026 12:19 am
  • የጽምዶ ልክፍት June 9, 2026 12:49 am
  • ገዳዩ ማነው? አስገዳዩስ ማነው? June 5, 2026 02:37 pm
  • ጽንፈኝነት ግን በኢትዮጵያ ምድር ፈጽሞ ቦታ የለውም! June 5, 2026 01:47 pm
  • የትብብሩ “ብናሸንፍም ፓርላማ አንገባም” መግለጫ “ወንበር ስታጡ ነው” የሚል ከፍተኛ ተቃውሞ አስነሳ June 4, 2026 12:04 am
  • አዲሱ የትራምፕ የምርጫ መመሪያ፡ የአሜሪካ ዲፕሎማቶችን አፍ ያስዘጋ፤ ተቃዋሚዎች ተስፋ ያስቆረጠ June 3, 2026 08:50 pm
  • “ኢህአፓ ከምርጫው በኋላ ይሰነጠቃል” May 29, 2026 07:07 pm
  • ሪፖርተር፡ “ስውር ተልዕኮ” – በከባድ ወንጀል ሊከሰስ May 6, 2026 11:55 pm
  • የፋኖ ኃይል በደረሰበት ጉዳት ሃምሳ ሺህ የሚጠጋ ትጥቅ ጥሎ ጠፋ April 29, 2026 02:27 pm
  • አዲሱ የቴድሮስ ካሳሁን 888 ኮድ፤ እንደ 666?! April 15, 2026 05:53 am
  • ምኑ ነው ያሳቃችሁ፤ ያስደሰታችሁ? April 2, 2026 10:52 am
  • የጀዋር መሃመድ የፖለቲካ ማንነት እና የባዕዳን ተልዕኮ April 2, 2026 10:16 am
  • ከግብፅ በዳያስፖራ ትርምስ ጠማቂዎች በኩል ፋኖ ወደ አዲስ አበባ የላከው “ስጦታ” March 27, 2026 09:14 am
  • “ሰላማዊ ታጋዮቹ” እነ ልደቱ ከአራጁ ሸኔ ጋር ተጣምረዋል March 25, 2026 01:04 pm
  • ጸረ-ኢትዮጵያዊ የሆነው የሪፖርተር አዘጋገብ March 19, 2026 11:54 am
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ የኦሮሚያ የልማት ድርጅቶች March 18, 2026 10:48 am
  • የጃኖ ስጦታና የዶሮ ፖለቲካ በጎንደር March 10, 2026 09:24 am
Copyright © 2026 · Goolgule