• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

የነጻነት ትግል መጀመሪያው የቀና ልቦና ባለቤትነት ነው

July 27, 2015 01:42 am by Editor 1 Comment

አፄ ቴዎድሮስ ያሠሩትን መድፍ (ሴባስቶፖል) ወደ ተራራው አናት ለማውጣት እየተጣደፉ ነው። እሳቸው ጭምር በጉልበት እያገዙ ሲገፋ ውለው ረፋዱ ላይ ከሰፈር ደርሰው ሲመለሱ አንዱ መድፉን ከሚገፉት ተለይቶ ወደ ሰፈር ሲወርድ መንገድ ያገኙትና ቆም ብለው ወዴት ነው ሥራ ትተህ የምትሄድ? ብለው ይጠይቁታል።

“ወደ ሰፈር፣ ወደ ሰፈር እየወረድኩ ነው ንጉሥ ሆይ!”

“ምነው ደህናም እማይደለህ?”

“ጣቴን ድንጋይ ቀርጥፎኝ ነው ንጉሥ ሆይ!”፤ ትንሽዋን ጣቱን በጨርቅ ነገር ጠቅሎ አንከርፏል።

“ና እስቲ! ቀረብ በልና የተጎዳኸውን አሳየኝ”፤ ሰውየው ንጉሡ ጋ ቀርቦ የቋጠራትን ጨርቅ ፈቶ ጣቱን ሲያሳይ ንጉሡ ትንሽ ጭረት ቢጤ ብቻ ያያሉ።

“ሌላ ቦታም ተጎተሃል እንዴ?”

“የለም! ይሄው ብቻ ነው።”

“እና! ይቺን ቁስል ናት! ብለህ ነው ሥራ ትተህ የምትሄድ?”

“ይችኑስ ቢሆን በማን ልላካት ጌታዬ?” ብሎ ንጉሡን እንዳሳቃቸው ይነገራል። እኔም ለሌላ ሰው የሚላከክ ቢሆን የአቶ መለስን ሙት መንፈስ እዚህ ጋ ባልሸነጎርኩ ነበር። ሆኖም የሳቸው ቁስል ምንም እንኳን አነስተኛ ባይሆንም በማንም ልላክከው ስለማልችል ማንሳት ሊኖርብኝ ነው። አንድ ጊዜ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ምሁራንን ሰብስበው ንግግር አደረጉ። ምሁራኑ በአንክሮ ሰሟችው። የአነጋገራቸውን አካሄድ ተንኮልና ክፋት እንዳዘለ ቢያውቁም ብዙዎቹ ሊናገሩ አልፈለጉም። በኋላ ግን አንድ እጅ ከመሃል ተቀሰረች። አቶ መለስ ምሁሩ እንዲናገሩ ዕድል ሰጡ። ሰውዬው ከማንም ይበልጥ የአቶ መለስ ንግግር አንገብግቦአቸዋል። ማንገብገብ ብቻ አይደለም በእንዲህ አይነቱ መሪ አገሪቷና ህዝቡ ወደፊት የሚደርስበት ውርጅብኝ የበዛ እንደሚሆን በደልና ስቃዩም አስከፊ ደረጃ እንደሚደርስ ተሰምቷቸዋል።

ምሁሩ ዕድሉን ተጠቀሙበት፤ ማለት የሚገባቸውን አጠቃለው እስኪጨርሱ አንዳችም ፍርሃትና መደናገር ሳይታይባቸው “… አሁን ለሁሉ ነገር ጊዜው አልፏል። እርስዎ እያሉ ገበሬው ውስጥ ገብቶ አደራጅቶ ፋይዳ የሚያመጣ ፓርቲ ይኖራል ተብሎ አይገመትም። ስለዚህ ኳሷ በርስዎ ቁጥጥር ስር እስከዋለች ድረስ ከምንም ነገር በላይ ቅንነትዎን ብቻ እንፈልጋለን። ቅንነትዎ አይለየን ቅን ሆነው ይምሩን ይሄን ብቻ ነው የምንጠይቅዎ …” ነበር ያሉት።

ምሁሩ አቶ መለስ እስከወዲያኛው ቀና እንደማይሆኑና በቀናነት ሊመሩ እንደማይችሉ አላጡትም። ነገር ግን ቀና ማድረግ ባይቻል እንኳን ቀና እንዳልሆኑ ለማሳወቅ ፈልገዋል። ሆኖም አቶ መለስ ቀና ባይሆኑ አይገርምም ከሚሰሩት ተንኮል አንጻር ቀናነት ኪሳራ እንጂ ትርፍ ሊያስገኝላቸው አይችልም። ተፈጥሮአቸውም ቢሆን በቀናነት ተቃኝቶ በሥነ ምግባር ጎልብቶ የቀናነትን ጎዳና የተከተለ ስላልሆነ ቀና ልሁን ቢሉ እንኳን አይችሉም። ይህ ብቻ አይደለም ከአመራራቸው ግብና ዓላማም ጋር ቀናነት አብሮ አይሄድም።

ገና ከትምህርት ቤት ጀምሮ የመሰሪነት ባህሪ እንደነበራቸው የሚመሰክሩ ብዙዎች ናቸው። ስንት ታጋይ ጓደኞቻቸውን ወደ እማይመለሱበት እየላኩ ለሥልጣን የበቁም ናቸው። ከሥልጣን በኋላም ሞት እጃቸውን እስከሰበሰበው ድረስ አለ እረፍት ኢትዮጵያዊነትንና ኢትዮጵያን ያዋረዱ፤ ህዝብ የናቁ፣ የከፋፈሉ፣ ያሰሩ፣ የገደሉ፣ ባንዲራን ያቃለሉ፣ ያገር ክብር የደፈሩን ሰው በምንም አይነት ቅንነት ልንመኝላቸው አንችልም።

እንግዲህ ስለአቶ መለስ ቀና አለመሆን ከተፈጥሮቸውና ከዓላማቸው አንጻር ነው ብለናል። ነገር ግን አቶ መለስን የሚያወግዝ፣ ለዲሞክራሲ ለሠላምና ለእኩልነት መከበር የቆመ፣ የተጣመመን ፍትህ አቃናለሁ የሚል፣ በሰው ልጅ እኩልነት የሚያምንና ይህንንም ለማስከበር የተነሳ ለአገሩ ብልጽግናና ነጻ መውጣት የሚያስብ ቅንነት ከጎደለው ከዓላማና ግቡ ጋር የተቃረነ መሆኑ አያጠራጥርም። አቶ መለስ የጣሏትን ቅንነት አንስቶ በጉያው ካልያዘ ልዩነታቸው ብዙም የተራራቀ አይሆንም። ለሳቸው ቅንነት ይጎዳቸዋል እሱ ደግሞ አለቅንነት ምንም አይነት የነጻነት ጉዞ ሊጓዝ አይችልም።

እንደውም ቀና ልቦና የሌለው ታጋይ ጊዜውና ሁኔታው ሲገጥመው አንዳንዴ ብልጭ እያለች የምታሳጣውን መጥፎ ባህሪ ሰው ጥላቻና ክፋት እፊት ለፊት አውጥቶ እማይጠቀምበት ምንም ምክንያት የለውም። ያንን እስከሚጠብቅና ድብቅ ፍላጎቱን እስኪያሟላ ድረስ ተፈጥሮው እያወከው ለትግል ጓዶቹ የማይመች የትግል እንቅፋት ሆኖ መቆየቱ አይቀሬ ነው።

ጎኑ ያለውን የትግል ጓዱን ያልወደደ ለዲሞክራሲ ቆሜያለሁ፣ ለነጻነት እፋለማለሁ፣ ለነፍትህ እዋደቃለሁ፣ … ቢለኝ አላምነውም፤ ባህሪው የገባበትን ዓላማ እንዳያሳካ አንቆ ስለያዘው የሱን ታጋይነት እጠራጠራለሁ። እውነቴን ነው ይህ ሰው ጫፍ ድረስ አይዘልቅም ይሰናከላል። ተሰናክሎም ያሰናክላል።

እናም የኢትዮጵያ ህዝብ ከገባበት የእጅ አዙር የባርነት አገዛዝ፣ ከነፃነት እጦት፣ ከእስር፣ ከንግልት፣ ከስደትና ከረሃብ ለማላቀቅ የተነሳህ፤ ፍትህ እንዲከበር፣ ዲሞክራሲና ሰላም፣ እድገትና ብልጽግና እንዲገኝ የምትፈልግ ሁሉ የትግልህ መጀመሪያ የቀና ልቦና ባለቤትነት መሆንን በማመን በቀናነት ከትግሉና ከታጋዩ ጋር ተቀላቀል። ቀና ልቦና ያለው መንገዱ ሁሉ ክፍት ይሆንለታል፣ በቀላሉ አይሰናከልም፣ ልቡ አያውከውም፣ አቀራረቡ ግልጽ ነው። አይፈራም፣ አይዋሽም፣ አያታልልም፣ አይጠራጠርም፣ ለቂም አያደባም፣ ለዝና አይናውዝም፣ ለሥልጣን አይዳክርም …

ይህ ካልሆነ ግን፤ እታገልልሃለሁ በምትለው ህዝብ ፊት ለመቆም ጉልበትህ አይጠናም። ህዝብ የምታደርገውን የትግል እንቅስቃሴ ቢያይም የአስተሳሰብህን ሸካራነት፣ የልቦናህን ክፋት ለመረዳት ብዙ ስለማይፈጅበት ክብርና ፍቅር ሊሰጥህ ይቸገራል፣ አይከተልህም። አይዞህ ልጃችን በማለት አያበረታታህም። እንደውም ልታታልለው እንደተነሳህ፣ ልታሞኘው እንዳደባህ ስለሚቆጥርህ ልቡን ከፍቶ አያሳይህም፤ ስለዚህ ቀና ሁን።

የፖለቲካን ትርጉም ከክፋት ጋር አትቀላቅል። ሌላም የምመክርህ አለኝ፣ የትግል ጓዶችህን አክብር፣ ጓደኛህ ስህተት ካለበት በድብቅ ከማማት ይልቅ ስህተቱን ፊት ለፊት ነግረህ እንዲመለስ አድርግ። ቀጥተኛ ባልሆነ መንገድ አሲረህ አሳድመህ አጥቂ አትሁን፤ ቂመኛ ሀሚተኛ አትሁን፤ መልካምነትን አሳንሰህ ስህተትን አታጉላ፤ የኔ ሃሳብ ይበልጣል፣ የምናገረውና የምሠራው ሁሉ የኔ ልክ ነው አትበል። ለቡዙሃን ድምጽና ሃሳብ ተገዛ፤ ሌላውን ደካማ አድርገህ አትይ፤ ለመወንጀል አትፍጠን፤ ልብህን ለንጹህ ወንድምነት ክፍት አድርግ። መቻቻልን፣ በጋራ መሥራትን አዳብር፤ የትግል ውጤት ተጠቃሚ ለመሆን ለሥልጣንና ለሀብት አትጓጓ፤ ድርሻና ኃላፊነትን ከፍ አድረገህ በመመልከት ሌሎችን አትጫን፤ መልካም ሥነምግባር በማሳየት ሌሎችም አንተን እንዲከተሉ አድርግ። አትወላውል! ለተነሳህበት ዓላማ እስከመጨረሻው ተጓዝ። ወዳጄ ሆይ! ምክር ቢበዛ ባህያ አይጫንምና ይበቃኛል። ለማንኛውም የነጻነት ትግል መጀመሪያው የቀና ልቦና ባለቤትነት መሆኑን አትዘንጋ።

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Uncategorized Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Comments

  1. nes says

    July 29, 2015 11:25 pm at 11:25 pm

    የናንተን የትምክህትና የቂም በቀል ሰበካ ለመስማት ጊዜ የለኝም።

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am
  • Rusted screws, metal spikes and plastic rubbish: the horrific sexual violence used against Tigray’s women July 4, 2025 01:48 am
  • በሞርሞን ቤ/ክ ዕርዳታ የኪዳነምህረት ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ማምለኪያ ሥፍራ አገኘች July 2, 2025 01:28 pm
  • የበረከት ስምዖን “አየር ላይ ትዕይንት” አየር ላይ ተበተነ July 2, 2025 01:24 am
  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am
  • ከትግራይ ሾልኮ የወጣው ምሥጢራዊው ሰነድ ምንድነው? May 20, 2025 09:18 am
  • በደቡብ ጎንደር በጸዳሉ ደሴ የተመሩት 72 ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ May 19, 2025 02:24 pm
  • የተመሠረተው የፋኖ አደረጃጀት ዋነኛ ዓላማው ድርድር መሆኑ ተነገረ May 14, 2025 11:07 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule