• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ቀጠሮ ይዣለሁ

May 23, 2014 01:06 am by Editor 1 Comment

እንደማንኛውም ባለቀጠሮ፤ ቀጠሮዬ ደርሶ፤ ከቦታው ተገኝቼ የማደርገውን የግሌን ጉዳይ እንጂ፤ “ሌላው” ጉዳይ አሁን አላስጨነቀኝም። “ሌላው” ያልኩት ትልቁ ጉዳይ፤ የቀጥሮዬ ቀን መቼ እንደሆነ፣ ለቦታው አደራረሴንና በዚያ ስደርስ የሚጠብቀኝን ነው። እነኚህ ለቀጠሮዬ ሕልውና ወሳኝ ቢሆኑም፤ በኔ ቁጥጥር ሥር ስላልሆኑ፤ ለጊዜው ወደ ጎን ገፋ አድርጌያቸዋለሁ። በተጨማሪም እኒህን ጉዳዮች ከናንተ ጋር የምጋራቸው ስለሆነ፤ አብረን እንድናቃናቸው ለሌላ ጊዜ ትቼ፤ በኔ ቁጥጥር ሥር ስላለውና በአእምሮዬ ስለሚዋልለው እንጨዋወት። ቀጠሮዬ ሀገሬ ኢትዮጵያ ለመግባት ነው። ኢትዮጵያ እስከሆነ ድረስ፤ የተወለድኩባትና ያባትና የናቴ አፅም ያረፈባት ጎንደር – አዘዞ ትሁን የተማርኩበትና ብዙ ጊዜ ያሳለፍኩበት አዲስ አበባ፤ ግድ የለኝም።

የሀገሬ የኢትዮጵያ ትዝታዬ፤ ብዙ ቦታ ይወሰደኛል። ጓደኞች ያፈራሁባቸው ቦታዎች፣ በአራት ዓመት ውስጥ ስንከራተት፤ ያስተማርኩባቸው ሁለተኛ ደረጃና አንደኛ ደረጃ ት/ቤቶችና ያሉባቸው ከተማዎች፣ (ከምባታ – ዋቸሞና ጢምባሮ – ግምቢቹ፣ ይፋትና ጥሙጋ – ደብረሲና፣ መናገሻ – አቃቂ፣ የረርና ከረዩ – ደብረዘይትና ግምቢቹ፣ ተመልሼ መናገሻ – ሰንዳፋ ) እህቴ በዕድገት በሕብረት ዘምታ ሄጄ የጠየቅኋትና ወደኔ ያመጣሁበት ሲዳማ – አለታ ወንዶ፣ በእናቴ የሚዘመዱኝን ልጠይቅ የሄድኩበት እስቴ – ቆማ ፋሲለደስ፣ በአባቴ የሚዘመዱኝን ልጠይቅ የሄድኩበት አዴት – ደብረመይ፣ ሁሉ በትዝታዬ ፊት ይንከራተታሉ። በ፲ ፱ ፻ ፷ ፮ ዓመት ምህረት ሰላማዊ ሰልፍ የወጣሁባቸው መንገዶች፣ በወቅቱ በትግሉ ዙሪያ ያሳለፍኩባቸው ቦታዎችና ያገኘኋቸው ሰዎች፤ በአእምሮዬ አብረውኝ አሉ። ለስደት ወደ ሱዳን የተንከራተትኩበት የአርማጨሆና የጭልጋ ምድር ሁሉ በአእምሮዬ እየተንከራተተ፤ ምንድን ነው ቀጠሮዬ? ምን አደርጋለሁ? ይኼን ነው እዚህ ላይ ያሰፈርኩ።

በአስተዳደጌ፤ ሀገር ምንነት ነው። እንደደም በሰውነቴ ውስጥ፣ እንደጥላ ከሰውነቴ ውጪ፣ ኢትዮጵያዊነቴ ሁሌም አብሮኝ አለ። እናም ኢትዮጵያን ከኔ አውጥቼ፤ ለኔም ሆነ ለሀገሬ ሕልውና መሥጠት አልችልም። ባደኩበት ኅብረተሰብ የኔን ሕልውና ትርጉም የሠጠሁት፤ የኅብረተሰቡ አካል አድርጌ ስለነበር፤ እኔን ከኅብረተሰቡ ለይቼ ዓይቼ አላውቅም። የኔን ሕልውና ከነበሩት ቀጣይና ለመጭዎቹ መሰላል አድርጌ ነው የማየው። ስለዚህ ምንም እንኳ አሁን ቀንድ ካበቀልኩ በኋላ በመጣሁበት ሀገር፤ ሁሉም “ለራሴ ነው የምኖር” ብሎ አማኝ ቢሆንም፤ እኔ አሁንም በግል መኖር ወይንም የኔን ሕይወት የራሴ የግሌ ብቻ አድርጌ አልወሰድም። እኔን እኔ በማድረግ በኩል፤ ከወላጆቼ ቀጥሎ፤ አካባቢዬና የሀገሬ ሰዎች በሙሉ አስተዋፅዖ አላቸው። ለዚህም ነው በኢትዮጵያዊያን ገንዘብ ሕልውናዬ ተጠብቆ፣ አድጌ፣ ተምሬ፣ በተማሪነቴ ታጋይ ሆኜ፣ ከዩኒቨርሲቲ ተባርሬ፣ ሥራም ይዤ አስተማሪ ሆኜ፣ የኖርኩ። ይህ የምንነቴ አምድ ነው። ከዚህ ውጪ እኔ የለሁም። እናም ማንነቴ ይኼ ነው። ለዚህ ሕይወቴን ታሣሪ አድርጌዋለሁ። እናም ይህ፤ ምን ጊዜም በምኞቴም ሆነ በሕልሜ የምመላለስበት የግል የአእምሮዬ ጓዳ ነው። አብረውኝ በትግል ዓለም ውስጥ ያለፉት አሁንም በኑሮዬ አብረውኝ አሉ። ለምን ይኼን ዓይነት ኑሮ እንደምኖርና ወደፊት ሀገሬን እንደምመኝ ግልፅ ነው።

ቀጠሮዬ ደርሶ ኢትዮጵያ ስገባ ምን አድርጋለሁ። በመጀመሪያ ደረጃ ቀጠሮዬ ደርሶ ኢትዮጵያ እንደምደርስ፤ ምንም ዓይነት ጥርጣሬ የለኝም። ዘንድሮ ለግንቦት አስራ አምስት አልደረስኩም። ለመጪው የ፳ ፻ ፮ ዓመተ ምህረት እንቁጣጣሽ ላልደርስ እችላለሁ። አዎ ራሱን “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” ብሎ ከሚጠራው መንግሥት ጋር ጠብ አለኝ፣ ትግራይን አልፎ ተከዜን ተሻግሮ ወልቃይት በገባ ጊዜ፤ ያኔ በነበርኩበት የድርጅት ሠራዊት አባል ሆኜ ጦርነት ገጥመን ቆስያለሁ። ይህ ወገንተኛና አምባገነን ቡድን በሥልጣን ላይ እያለ ሀገሬን ማየቴ አይታሰብም። እርግጠኛ ሆኜ የማምነው ግን፤ ውሎ አድሮ ፀሐይ ነገ መውጣቷ እንደማይቀር ሁሉ፤ ይህ ቡድን ይወድቃል፤ እኔም ሀገሬን አያለሁ። ብቻዬን ደግሞ አይደለሁም። የተለያዬ የግል መንገድ ቢኖረንም፤ ከሞላ ጎደል በዚሁ ጥላ ሥር ያለን ብዙዎች ነን።

የምመለስባት ኢትዮጵያ ከነበርኩባት ኢትዮጵያ የተለየች እንደምትሆን ጥርጥር የለኝም። ሕይወቴን በሙሉ የታጋልኩለት የሕዝቡ ዴሞክራሲያዊ መብት መከበር ሀቅ የሆነባት ኢትዮጵያ ትሆናለች። የእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ መብት በሕግና በተግባር የተጠበቀባት ትሆናለች። የሕግ የበላይነት የሠፈነባት ትሆናለች። የሕዝቡ ሉዓላዊነት ያላንዳች ማቅማማት የተረጋገጠባት ትሆናለች። መቼም እንደኔ ከሀገሩ የወጣ ሁሉ፤ የሀገራችን የኢትዮጵያ መሪ አይሆንም። ሁሉም የኢትዮጵያ ሚኒስቴርና የኢትዮጵያ አምባሳደር አይሆንም። ሁሉም የአዲስ አበባ ባለሕንፃ አይሆንም። ሁሉም በዘመናዊ መኪና ተንፈላሳሽ አይሆንም። ሁሉም በለሙ የኢትዮጵያ መሬት ባለሠፊ እርሻ አይሆንም። ሁሉም ነጋዴ አይሆንም። ሁሉም የኢትዮጵያ የእግር ኳስ ተጫዋች አይሆንም።  እያንዳንዱ የራሱ የሆነ የተማረበት፣ የሠለጠነበትና ልምድ ያካበተበት ሙያ ይዞ እንደሚገባ እርግጠኛ ነኝ። በዚህም ሀገራችንን ኢትዮጵያን ብዙ ወደፊት እንደምናራምዳት ቅንጣት ታክል ጥርጥር የለኝም። እናም ቀጠሮ የያዝኩት ለዚህ ነው።

በቅርቡ እናቴን በቦታው ተገኝቼ ልቀብራት አልቻልኩም። መቃብሯን ሄጄ አያለሁ። ቦታው ባንድ ላይ በሆነው ባባቴ መቃብርም፤ ብዙ ጊዜ እየተመላለስኩ ለማየት ዕቅድ አለኝ። የጠለምትን ውጣ ውረድ እሄድበታለሁ። በደሴ አልፌ አሲምባ – ስንገደን መጎብኘት እወዳለሁ። ወልቃይት ጠገዴን በየመንደሩ እየሄድኩ ሰዎችን ማግኘት፤ ቦታውን መቃኘት እፈልጋለሁ። ኑሮዬን የት እንደማደርግ ቁርጥ ያለ ዕቅድ ባይኖረኝም፤ ሀገራችን ብዙ የተለያየ ሙያ ያላቸው ሰዋች እንደሚያስፈልጋት ስለምረዳ፤ ባንዱ የሙያ ዘርፍ ገብቼ ወገኔን እንደማገለግል ጥርጥር የለኝም። ተማሪ ነበርኩ መምህር ነበርኩ፤ ዋናው ካገሬ ያወጣኝና በውጭ እንድቆይ ያደረገኝ ለሕዝቡ ዴሞክራሲያዊ መብት መታገሌ ነውና፤ ይህ ሲተገበር፤ ራሱ በቦታው ሆኖ ማየቱ፤ የመኖሬን ትርጉም ተጨባጭ ያደርገዋል። እናም በጣም እጓጓለሁ። እዚህም ትንሽ ተምሬ ሙያ አካብቻለሁ። ልምድም ሸምቻለሁ።

ሰዎችን ወደፊት እንዲመለከቱ የሚያደርጋቸው ተስፋ ነው። ተስፋ ደግሞ መነሻው ተጨባጭ የሆነ ክስተት አለው። ወደ ሀገሬ ተመልሼ ለመሄዴ ተስፋዬ፤ አሁን በሀገራችን ያለው የዴሞክራሲ ጥማትና የታጋዩ ብዛት ነው። በዞን ዘጠኝ አርበኞች ምን ያህል እንደምኮራና እንደምቀናባቸው የልቤን አውጥቼ ልናገር ብል፤ መግለጫ ቋንቋው አይበቃኝም። በምንም መንገድ ቢተረጎም ሁላችን የምንፈልገው፤ ረሃብን ከሀገራችን አስወግደን፣ በሺታን በቁጥጥር ሥር አውለን፣ እያንዳንዷ ኢትዮጵያዊት በሀገሯ የትም ሠርታ የመኖር መብቷ ገደብ ሳይኖርበት፣ ሀብት ለማፍራትና ትዳሯን ለመመሥረት አዛዥ ሳይጫናት፣ ልማትና ትምህርት የተሥፋፉባት ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ነው። ይህ ዋናው ዕሴታችን ነው። ይህ በተግባር ላይ ይውላል። ያኔ ዞረን ብዙ ነገሮችን እንቃኛለን። ያኔ የየራሳችንን ፓርቲዎች በሕዝቡ ፊት እያቀረብን እንወዳደራለን። በቃኝ ብዬ የማልተወው ነገ ቢኖር፤ አሁን ፓርቲ ባይኖረኝም ከሚስማማኝ ጋር ተላትሜ፤ በሀገሬ የፖለቲካ ምኅዳር ተካትቼ ዴሞክራሲያዊ መብቴን መጠቀምና፤ ተሳትፎ ማድረግ ነው። ያኔ ያንድ ቡድን አዋቂነትና ብቸኛ ገዥነት በመጽሐፍ የሚነበብ ይሆናል። የሕዝቡን ሉዓላዊነት በተግባር እንረዳለን። ያኔ መምህሮችና ተማሪዎች እንሆናለን። ከዚያች ቀን ጋር ቀጠሮ ይዣለሁ።

ያኔ በየትኛውም የሀገራችን ኢትዮጵያ ክፍል የሚኖሩ ኢትዮጵያዊና ኢትዮጵያዊት ሁሉ፤ አባታቸው ማነው? እናታቸው ማናት? ደማቸው ከየትኛው ወንዝ ይቀዳል? ምን ቋንቋ ይናገራሉ? ሃይማኖታቸው ምንድን ነው? ስንተኛ ክፍል ድረስ ተምረዋል ሳይባል፤ ሁሉም እኩል ኢትዮያዊና ኢትዮጵያዊት፤ እኩል መብት ያላቸው ይሆናሉ። በሕግ ፊት ሁሉም እኩል ይታያሉ። የሀገሪቱ መሪ እንደኔ እኩል ከፍርድ ፊት ይቀርባል/ትቀርባለች። ያኔ ኢትዮጵያዊነት ይከበራል። ያኔ የሃይማኖት ነፃነት በገሃድ ይታያል። ያኔ የማመንም ሆነ ያለማመን፣ የራሱን ፈጣሪ የመሰየምም ሆነ በተሰየመው ለመካተት፤ ሁሉም መብት ይኖረዋል። ያኔ የግል ማንነትን ራሱ ግለሰቡ እንጂ ማንም ሊተረጉምለት እንደማይችል ሕጉ ይደነግጋል። ያኔ በኢትዮጵያ ምድር እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊና እያንዳንዷ ኢትዮጵያዊት በግለሰብ ኢትዮጵያዊት ብቻ የፖለቲካ ተሳትፏቸውን፣ የሥራ ተግባራቸውን፣ የንግድ ስምሪታቸውን ያከናውናሉ። በትምህርት መስክም ሆነ በውትድርና፣ በተቀጣሪነትም ሆነ በቀጣሪነት፤ ኢትዮጵያዊነት ብቻ ይሆናል መለኪያው። ለዚያ ቀን ቀጠሮ ይዣለሁ።

ያ ብቻ አይደለም። ልቤ ትልቅ ነው። በያንዳንዱ የስፖርት ዘርፍ ግንባር ቀደም ከሚሠለፉት ሀገሮች መካከል ኢትዮጵያ ትገኛለች። ያኔ የሚወለዱ ልጆች ረሃብንና በሽታን በታሪክ መጽሐፍት ብቻ ነው የሚያውቋቸው። ያኔ አረንጓዴ ብጫና ቀይ ቀለም ያለው የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ በየቦታው ሲውለበለብ ልባችን በደስታ ይፈነድቃል። በኒው ዮርክ ማራቶን፣ በፊፋ የዋንጫ ሽልማት ጊዜ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ትንንሽ አረንጓዴ ብጫና ቀይ ስንደቅ ዓላማውን አንስቶ፤ ሌሊቱ እንዳይጨልም ይሟገታል። የሳይንስ ሊቆች፣ የሕክምና ፈላስፎች፣ የምርምርና ጥናት አዋቂዎች በየመንገዱ ይታያሉ። ለሙ ያገራችን መሬትና ያገራችን ሆድ ዕቃዎች፣ የምርት መዛቂያ ይሆናሉ። ለዚያ ቀን ቀጠሮ ይዣለሁ።

በነገራችን ላይ፤ አብሮ ከኔ ጋር ቀጠሮ ላማድረግ ለሻ ሁሉ፤ ወጪያችንን ለመጋራትና ለመተባበር ዝግጁ ነኝ።

eske.meche@yahoo.com

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Comments

  1. bezabih molla says

    May 28, 2014 02:51 pm at 2:51 pm

    አለን ከጎንህ ነን በርታ እድሜየን በሙሉ ነፃነቴን አጥቻለሁ

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am
  • ከትግራይ ሾልኮ የወጣው ምሥጢራዊው ሰነድ ምንድነው? May 20, 2025 09:18 am
  • በደቡብ ጎንደር በጸዳሉ ደሴ የተመሩት 72 ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ May 19, 2025 02:24 pm
  • የተመሠረተው የፋኖ አደረጃጀት ዋነኛ ዓላማው ድርድር መሆኑ ተነገረ May 14, 2025 11:07 pm
  • ከፍተኛ የፋኖ አመራሮች መገደላቸው ተነገረ May 6, 2025 10:40 pm
  • ሃይማኖትን ለተራ የፖለቲካ ሸቀጥ ማዋል ውርደት ነው April 24, 2025 12:43 am
  •  የኬሪያ ኢብራሒም ኑዛዜ “ብትንትናችን ወጥቷል” April 22, 2025 12:08 am
  • ለወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞን አመራሮች ወታደራዊ ሥልጠና ተሰጠ April 16, 2025 11:44 pm
  • ዓቅም እንደሌለው የገመገመው ሻዕቢያ ፊቱን ከጦርነት ወደ ዲፕሎማሲ እያዞረ ነው   April 15, 2025 12:32 am
  • “አንድ የፋኖ ተቋም (የእስክንድር) ተመሥርቷል፤ ሌሎቹ ደግሞ እንዲሁ አንድ ተቋም መሥርተው ወደዚህ ይመጡ” አበበ ጢሞ April 11, 2025 12:07 am
  • መለስ (ለገሰ) ዜናዊ – ተዋርዶ ያዋረደን! April 9, 2025 10:28 pm
  • የተከዜ ዘብ: የሉዓላዊነት መጠበቂያ April 8, 2025 11:49 pm
  • አዲስ አበባ አስተዳደር የሪፖርተርን የተዛባ መረጃ ኮነነ፤ ሕጋዊ እርምጃ እወስዳለሁ አለ April 8, 2025 10:06 pm
  • ሀሰተኛውን የሪፖርተር ዘገባ ንግድ ባንክ በጽኑ ተቃወመ፤ እርማትም ጠየቀ April 8, 2025 09:48 pm
  • “ኦሮሚያ ላይ ወይም ሌላ ቦታ ላይ ስታደርገው ከነበረ ትግራይ ወስጥም የማታደርግበት ምንም ምክንያት አይኖርህም” ነው ጌታቸው ረዳ April 7, 2025 10:22 pm
  • “TPLF’s belief in a strong federal government was always tied to its own dominance in Addis Ababa” April 7, 2025 10:15 pm
  • Counter-Video by EBC Challenges EBS Broadcast, Sparks Public Outcry Over Alleged Misinformation March 31, 2025 02:36 am
  • የኤሊያስ መሠረትን ፌክ መረጃ ማን ያጋልጥ? February 19, 2025 06:00 pm
  • አዘርባጃን፡ የሻዕቢያን ሸምቀቆ ማጥበቂያ?! February 19, 2025 12:29 am
  • የአሜሪካ ድምፅ/ቪኦኤ ይዘጋ ተባለ  February 12, 2025 03:37 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule