
የኮፊ አናን ተልዕኮ በሶሪያ ላለው ትርጉም ያለዉ ዉጤት ማስገኘቱ አያስተማምንም። ይህ፤ ግጭቱ በየትኛዉም መልኩ መመለስ የማይችልበት ጠርዝ ላይ በመድረሱ ብቻ ሣይሆን፤ ከጅምሩም ምናአልባት የሶሪያ ገዥዎች ከወዲሁም ቢሆን በሰላም ሽግግሩ እንዲከናወን ፈቃደኛ አይሆኑምና ነው። የበሺር አል አሳድ ገዢ ቡድን፤ ቅንጣት የለዉጥ ሙከራ ሳያደርግና ተቃዋሚዎችን ሳያግባባ፤ ለምን በኃይል እንቅስቃሴዉን ለማጥፋት የወሰነበትን፤ መረዳት ያስፈልጋል።
ባለፈው ዓመት፤ የመካከለኛው ምሥራቅ አምባገነን ገዥዎችን፤ የተቃውሞ እንቅስቃሴዎች አናግተዋቸዋል። ሶስት ዓይነት ዉጤቶች ተከስተዋል። በቱኒሲያና በግብፅ፤ ያለ ብዙ ሕይወት ጥፋት ፈላጭ ቆራጮቻቸዉን አስወግደዋል። ዚን ኤል አቢዴን ቢን አሊ እና ሆዝኒ ሙባረክ፤ ያለ ሕዝባዊ የርስ በርስ ግጭት ከሥልጣናቸው ተባረዋል። በግብፅ፤ ሙባረክ የመጨቆኛ ክንዱ አድርጎ ያቋቋመው የወታደሩ ክፍል፤ ድጋፉን ወደ ሕዝብ በማዞሩ፤ በበለጠ ሊቀላጠፍ ችሏል። ሆኖም ግን፤ በግብፅ የዴሞክራሲያዊነት የወደፊት ጉዞ አስተማማኝ አይደለም። ይህን ያልንበት፤ አሁንም ቁልፍ፣ ቁልፍ በሆኑት የመንግሥት ልዩ፣ ልዩ ክፍሎች፤ ሥልጣኑን በግልፅ ጨብጠው የሚያሽከረክሩት፤ ሙባረክ የሾማቸው ናቸዉና! ታዲያ አሁንም፤ በፀጥታ ኃይሎችና በተቃዋሚዎች መካከል፤ በተደጋጋሚ ለሚታዩት ግጭቶች፤ መነሻ ሥሩ ይኼ ነው።
ከዚህ ጋር በተያያዘ መልኩ፤ በሳዑዲ ዓረቢያና በባህሬን እንደታየው፤ ያሉት ገዥዎች ተቃዋሚዎችን ከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ በመስጠት፣ የመንግሥታቸዉን አገልግሎት በማስፋፋትና ትንንሽ የፖለቲካ ማሻሻያዎችን በማስከተል፤ ሊደልሏቸው ችለዋል። በሊቢያና በሶሪያ ግን፤ ሁኔታው የተለየ ነበር። የሁለቱም ሀገሮች ገዥዎች፤ ተቃዋሚዎችን በሚያጥለቀልቅ ኃይል ለመደምሰስ ወሰኑ። በሊብያ፤ የውጭ ድጋፍ አማፂያኑ፤ ኮሎኔል ሞዓመር ጋዳፊን በአስተማማኝ እንዲያሸንፉትና እንዲያወርዱት ረዳቸው። በሶሪያ፤ አምና በመጋቢት የተጀመረው አመፅ፤ ዉጤቱ አሁንም አልታወቀም፤ በሕይወት ላይ የሚደርሰው ጥፋትም በየጊዜው ወደ ላይ እዬጎነ ነው።
ሶሪያ አሁን ያለችበት ጎዳና ከሞላ ጎደል የተጠረገውና የመሻሻል ጭላንጭሉ የተዳፈነው፤ የአሁኑ ገዥ የበሺር አባት፤ ሀፌዝ አል አሳድ፤ እንደ አውሮፓዉያን አቆጣጠር፤ በ1970 በፈጠሩት ክን (logic) ነው። በግልፅ የሚታየው፤ በ1963* በወታደራዊ የመንግሥት ግልበጣ፤ ሥልጣኑን በጨበጠው በባዓዝ ፓርቲ ሥር የሚተዳደር የአንድ ፓርቲ መንግሥት ነው። ምንም እንኳ ሳዳም ሁሴንን በኢራቅ ለሥልጣን ያበቃው የባዓዝ ፓርቲ፤ የሶሺያሊዝም ከባድ ጫናን ያዘለ ብሔርተኛ አፍቃሪ-አረብ ፍልስፍና ቢያውለበልብም፤ በሶሪያ የተከሰተው እውነታ፤ የአንድ የተለይ የሶሪያ ክፍል፤ አላዊዎች፤ መገልገያ መሆኑ ነው። የሀገሪቱን 10% ሕዝብ የሚሆኑትና በሶሪያ ሰሜን ምዕራብ የተኮለኮሉት አላዊዎች፤ በአንድ የተለዬ የእስልምና ዘርፍ የሚያምኑ ናቸው። በአላዊዎች ተጥለቅልቆ የነበረው የባዓዝ ፓርቲ፤ በ1963* ሥልጣኑን በጨበጠበት ጊዜ፤ ለዘመናት በኦቶማን ሀገር ገዥዎችና ለጥቂት ጊዜ ደግሞ፤ ከ1920* እስከ 1946*፤ በፈረንሳይ ቅኝ ግዛትነት ማቅቆ የተቀረፀ ግዛት ነው የወረሰው። ይህ መንግሥት፤ ሀገሪቱን ለማልማት ሳይሆን፤ ጥቂቶቹ የሀገሪቱን ንብረት፤ ከብዙኀኑ የኅብረተሰብ ወገን የሚነጥቁበት፤ ቀልጣፋ የምጣኔ ሀብት ተቋሞች ላይ የተፈናጠጠ ነበር። በኦቶማንና በፈረንሣዮች ወቅት፤ ይህ አናሳ ቡድን፤ የቅኝ ገዢዎችን ሥልጣንና የሶሪያዊ አጋሮቻቸዉን ያካትት ነበር። በባዓዝ ግዛት ከሞላ ጎደል አላዊዎችን ብቻ ያዘ።
እኒህ ቀልጣፋ የምጣኔ ሀብት ተቋሞች ብዙ የሚያስከትሏቸው ጉዳዮች አሏቸው። በጣም በዋናነት የሚቀመጠው ድህነት ነው። የሕዝቡን 10% ለመጥቀም ሲባል፤ የምጣኔ ሀብቱን ያዋቀረ ኅብረተሰብ፤ ብልፅግናን ሊያመጣ አይችልም። ለማደግና ለመበልፀግ፤ አንድ ኅብረተሰብ ማድረግ ያለበት በጣም ወሳኝ ጉዳይ፤ በሕዝቡ ውስጥ በሰፊው የሚገኘዉን የተፈጥሮ ስጦታና የታመቀ ንብረት ማቀፍ ነው። ምንም እንኳ ከነፃነት ወዲህ የተከተሉት የሶሪያ ገዢዎች፤ በፖለቲካ ልፍለፋቸው በአያሌው በተበረዘ የትምህርት ዙሪያ፤ ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ ቢያፈሱም፤ ከገዢዎቹ ጋር ትስስርና ግንኙነት ያላቸው ብቻ፤ የመንግሥት ተሿሚዎችና የራሳቸዉን ንግድ አቋቋሚ ሆነው ለመጠቀም ችለዋል።
እኒህ ቀልጣፋ የምጣኔ ሀብት ተቋሞች ከሚያስከትሏቸው ጉዳዮች ሁለተኛው የፖለቲካው ነው። መጥማጭ የምጣኔ ሀብት ተቋሞች፤ ከእውነት ተገንጥለው በሕዋ አይኖሩም። መዥገር በሆኑ የፖለቲካ ተቋሞች፤ በዚሁ ሥልጣኑን በሙሉ አሰባስቦና ጠፍርቆ በያዘና ይኼንኑ የፖለቲካ ሥልጣኑን አንደፈለጉው ከመጠቀም የሚያግደውን ማናቸዉንም እንቅፋት ገፋፎ የሀገሪቱን ምጣኔ ሀብት በሚቆጣጠር ጠባብ የአለቆች ቡድን መደገፍ አለባቸው። ማስኬጃ ክኑ (መንገዱ) ቀላል ነው። ያለዚያ ይህ የአለቆች ቡድን እንዴት አድርጎ ቀሪዉን የኅብረተሰብ ክፍል አብሮት እንዲጓዝ ሊያሳምነው ይችላል? እናም ሶሪያ፤ ሁሉንም የሥልጣን ኮርቻ በሚቆጣጠር ያው ኃላቀር አምባገነን ያለቆች ቡድን መጠመዷ፤ ያጋጣሚ ጉዳይ አይደለም። ያ ሁሉ ጭቆና ኖሮም፤ መዥገር የሆኑ የፖለቲካ ተቋሞች ሙሉ በሙሉ የተረጋጉ አይደሉም። ግልፅ የሆነው ያለመረጋጋት መንስዔው፤ ተቋሞች፤ መጥማጭ ሲሆኑ፤ ከሥልጣኑ ቁንጮ ላይ የተቆናጠጡት፤ በዚሁ ሂደት ይበለፅጋሉ። ይህ ደግሞ፤ ሌሎች እነሱን ተክተው የምዝበራው ተጠቃሚዎች፤ ራሳቸው እንዲሆኑ ይፈልጋሉ ማለት ነው። ይህ ከኦቶማን ግዛት ወደ ፈረንሳይ ግዛት፣ ቀጥሎም ወደ ባዓዚዎች፤ ከዚያም የአላዊዎች ግዛት ሽግግርን መመልከቻ አንድ መንገድ ነው። ከነዚህ ቡድኖች መካከል አንዳቸው የኅብረተሰቡን በመዝበራ የተመሠረተ አደረጃጀት መቀየር ይችሉ ነበር፤ ነገር ግን፤ ሳይነኩት መተው ጥቅማቸዉን ስለሚጠብቅላቸው፤ እንዳለ ተውት። ያ ሁሉ ምዝበራ፤ ሕዝቡ ዕድላቸዉንና ምኞታቸዉን የዘጉባቸዉን ተቋሞች ለመለወጥ፤ በኅብረተሰቡ ውስጥ ሥር የሰደደ ቁስልና ቂም ፈጠረ።
በሶሪያ ያለው የገዢ ቡድን፤ ተደጋጋሚ እምቢተኝነቶች ከአምና መጋቢት 2011* በፊት ገጥመዉታል። እንደተለመደው፤ ሁሌም በተመሣሣይ መንገድ፤ በጉልበቱ በማፈን፤ መጥማጭ ተቋሞቹን ለመጠበቅ፤ አፀፋ ሠጥቷል። በ1982* የሃማ ነዋሪ የሱኒ እስልምና ተከታዮች፤ በሀፌዝ አል አሳድ ላይ አመፁ። እሱም የጦር ሠራዊቱን ልኮ ደመሰሳቸው። ምን አልባትም አርባ ሺህ (40,000) ሰዎች ተገድለዋል። ሌሎች አመፃዎችም በእስልምና ወንድማማቾች በ1970* ዎቹና በ1980* ዎቹ፤ በድሩዚ በ2000* እና በኩርዶች በ2004* ተቀስቅሰው ነበር።
ለምንድን ነው እኒህ ሁሉ መነሣሣቶች ዉል ወዳለው ለውጥ ያላመሩት? ለምንድን ነው የሶሪያ አለቆች፤ እንደ ግብፅ ጦር ሠራዊት የሚቆጣጠሩት ሽግግር ለማምጣት ያልሞከሩት? ከፊል መልሱ፤ የሶሪያው የገዢ ቡድን፤ ልክ እንደ ሊቢያዉ ቡድን፤ ከግብፆቹና ከሊቢያኖቹ የበለጠ በዝባዥና የበለጠ ጨቋኝ ሆኖ፤ ከብዝበዛው ጋር በመቆራኘቱ፤ ነፃነት ቢመጣ ብዙ የሚጎዳ በመሆኑ ነው። የመጨቆኛ መገልገያዎቻቸው እንዳሉ ሆነው፤ አማፂያኖችን ለማንበርከክ ኃይል መጠቀሙን፤ አስፈላጊ ነው ብለው አመኑበት። ምን አልባትም እኒያ ቀልጣፋ መጥማጭ ተቋማት በሶሪያ ኅብረተሰብ ላይ ያደረሱት፤ በበለጠ የዋናነት ዋጋ ያለው መሆኑ ነው። ምንም እንኳ በሙባረክ ዙሪያ የተሠለፉት ፖለቲከኞች፣ ከርሱና ከልጆቹ ጋር ተጣብቀው የተሠለፉ ነጋዴዎችና የወታደሩ ክፍል በሙሉ የግብፅ ገዢ አለቆች አካል ቢሆኑም፤ አንድ ወጥነት ያለው ቡድን አልነበሩም፤ ሁሉንም የግብፅ የኅብረተሰብ ወገን በአንድነት ጠቅልለው አልረገጡም። እናም አመፁ በተጀመረ ጊዜ፤ የኅብረተሰብ ማኅበራት ነበሩ፤ የመሪነትን ሚና ሊጫወቱ የሚችሉ፤ አንደ የእስልምና ወንድማማቾች የመሳሰሉ። ታዲያ የአለቆቹ የተወሰነ ክፍል፤ በተለይም ከጦር ሠራዊቱ ክፍል፤ ሙባረክንና አንዳንድ የቆዩ ባለሥልጣኖችን በማጋፈጥኅ ጥቅማቸውን ከሞላ ጎደል የሚያስጠብቁበት መዉጪያ ቀዳዳ ሊታያቸው ችሏል። የሶሪያ ገዢ ክፍል አለቆች፤ አንድ ወጥ በመሆናቸዉና ጠፍርቀው የያዙት ሥልጣን ከጥንካሬው ከላላ፤ የለውጡ ማዕበል አጥለቅልቆ እነሱን ማበራዬቱ የበለጠ ስለሚያደላ፤ ምን ጊዜም ቢሆን በነሱ ቁጥጥር ሥር የተቀናጀ ለውጥና ሽግግር መከሰቱ፤ ጠባብ ዕድል ነው የነበረው። አጥለቅላቂ ኃይል የመጠቀሙ ምርጫ ከተወሰደ ወዲያ፤ ቅንጣትም ታክል ዕድል የነበረው የድርድር ስምምነት ቀዳዳ በኖ ጠፋ፤ በሶሪያ ኅብረተሰብ መካከል የነበረው ክፍፍል የበለጠ ሠፋ።
በዚህ አመለካከታችን የምናቀርበው፤ ሰላማዊ መፍትሄ ቦታው እንዳልሆነ ነው። የአሳድ መንግሥት ወዶ ሥልጣኑን መልቀቁ፤ የሕልምና የቅዠት እንጂ፤ የእውነትነት ዕድል የለውም። ስለዚህም፤ የዓለም አቀፍ ድርድሮች፤ ይኼን የአሳድን በሰላም ወዶ መልቀቅ ያስከትላል ብሎ መመፃደቅ – ያው መመፃደቅ ነው።
ፈረሱ ሜዳ ገብቷል። መጋለቡን የሚያግተው የለም። ይኼ መንግሥት፤ የተፈጠረውን ሕዝባዊ መነሣሣት ሊቋቋመው አይችልም። መቼ እንደሚገለበጥ የታወቀ የጊዜ ወሰን የለም። የዛሬ ዓመት በዚህ ሰዓት፤ ምንአልባት በሥልጣን ላይ ሊሆን ይችላል፤ ከሆነ ግን ብዙ አካባቢዎችን የመቆጣጠር ችሎታው በጣም የሟሸሸ ይሆናል፤ አሁን፤ ምንአልባት የአሳድን መንግሥት የመጨረሻ መጋረጃ መዘጊያ ሰዓት፤ እያዬናት ነው።
ሶሪያን አሁን ፈጦ ያገጠጠባት፤ የሚቀጥለው ምን ይሆን የሚለው ነው። የዓለም አቀፍ ኅብረተሰብ ሣይሆን፤ ሶሪያዊያን ናቸው አዲስ ተቋሞችን መገንባት፣ መከላከልና መጠበቅ ያለባቸው። ከዚህ መርዘኛ ገዢ የሚደረገው ሽግግር፤ ከዚህ በፊት ከፈረንሣይ በዝባዥ አገዛዝ ተከትሎ የበለጠ የከፋ የባዓዞች እና የአላዊዎች አገዛዝ እንደተከተለው እንዳይሆን፤ መጠንቀቅ አለባቸው። ታላቅ ፈተና ነው!
*ይህ የዘመን አቆጣጠር በአውሮፓዊያን ስሌት ነው።
በዳሮን አሽሞሉ እና ጀምስ ሮቢንሰን
ትርጉም በአንዱ ዓለም ተፈራ ለጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ የተላከ
(በደራሲዎቹ ፈቃድ የተተረጎመ)
ፅሑፉን በሚከተለው አድራሻ አግኝቶ ማንበብ ይቻላል።
http://whynationsfail.com/blog/2012/3/9/is-the-one-percent-the-same-everywhere.html
http://whynationsfail.com/blog/?currentPage=2 ( Article # 4 ሁለተኛው ገፅ፤ አራተኛው ፅሑፍ )
Leave a Reply