
በፌብርዋሪ 11 እና 12, 2017 በሁለቱ ቀናት ውስጥ በአምስቱም ክፍለ ዓለማት በሚገኙ ከአርባ በላይ በሚሆኑ ከተሞች ለአርበኞች ግንቦት 7 የገንዘብ ድጋፍ ለማሰባሰብ የተደረጉ በዓላዊ ዘመቻዎች መካሄዳቸውን የበረታ በየአካባቢ በተደረጉት ዝግጅቶች ላይ በመገኘት ለዓይን ምስክርነት ሲበቃ የተቀረው ኢትዮጵያዊ ደግሞ በሚዲያዎች የታደመው ይመስለኛል።
በዝግጅቱ ላይ ከድጋፍ ማሰባሰቡ በተጓዳኝ ለአርበኞች ግንቦት 7 ሊቀመንበር ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በስካይፔ ከየአካባቢው ጥያቄዎች እየቀረቡ መልስ ሲሰጥም ስለነበር፤ በዚህ አጋጣሚ ከቀረቡት ልዩ ልዩ ጥያቀዌዎች ውስጥ አንድ ሃሳቤን የሰረቀው ጥያቄ “የትጥቅ ትግሉ በተጠበቀው ፍጥነት አልሄደም” የሚለው ነበር።
ጥያቄው ማንም የባርነት ቀንበር የከበደው ሰብአዊ ፍጡር ሁሉ ሊያነሳው ጥያቄ እንደሆነ የሚያጠያይቅ አይመስለኝም። የመከራና የጭነቀት ጊዜ ሰከንዱ ዘሎ እንደ ሰዓት፤ ሰዓቱ ተስፈንጥሮ እንደሳምንት፤ ሳምንቱ ወራትን ተሻግሮ ወደመንፈቅ ወዘተ … እየዘለለ ስለሚርቅ፤ የመከራውን ጊዜ ለማሳጥር የሚደረገው ሩጫ መከራው እስከልተገፈፈ ድረስ ፈጥኗል ሊባል የሚችልበት አንዳችም አጋጣሚ አይኖርም። ማጠር መርዘሙ የሚገመገመው ከትግሉ ፍጻሜ በኋላ ለመቆየት ዕድል የገጠመው ያለፈበትን የመከራ ጉዞ እያነሳ መወያየት ሲጀምር ነው።
የትጥቅ ትግል የሚመረጠው ይፈጥናል፤ ፈጣን ፈውስ ያመጣል፤ ተብሎ ሳይሆን፤ ሌሎች አማራጮች ሁሉ ተሞክረው ከተገጠመው ክፉ ባለጋራ አቅም ጋር የሚመጣጠኑ ሆነው ባለመገኘታቸው ምክንያት ብቻ የመጨረሻው አማራጨ ሆኖ የሚወሰድ እንደሆነ መገንዘብ በጣም አስፈላጊ ነው። የእብሪተኞች ጦርነት አይደባለቅ።
ከዚያም በተረፈ የትጥቅ ትግልን ጠብመንጃን አንግቦ ሸተት ወደወንዙ ከሚለው አቅጣጫ ብቻ ሳይሆን፤ ከሌሎች ብዙ አቅጣቻዎች ልብ ብሎ ማየት አስፈላጊ ቢሆንም፤ የተነሳሁት ስለትጥቅ ትግል ሰፊ ታሪክና ምሳሌ ለመተረክ ሳይሆን፤ አርበኞች ግንቦ 7ን በተመለከተ ብቻ ጥቂት ማስታወሻ ለማቅረብ ስለሆነ፤ ነገሩ ቀላል እንዲሆን እዚያው አገራችን የተደረጉ የትጥቅ ትግሎችን አንስቼ ቀለል ባለ መንገድ ለሃሳቤ መቋጠሪያ ላብጅለት።
የኤርትራውያን ነጻ ሃገር ለመሆን የተደረገው የትጥቅ ትግል 30 ዓመት፤ ትግራውያን “ወንድሞቻችን” ደግሞ እኛን በባርነት ለመግዛት የሚያስችላቸውን ነጻነት ለመጎናጸፍ ያደረጉት የትጥቅ ትግል 17 ዓመት ፈጅቷል። ታደያም እነዚህ ሃይሎች የቀደመው ያንድ ትውልድ ዕድሜ ሲያስቆጥር፤ የዃለኛው ደግሞ የዚያን ከግማሽ በላይ ሲያገባድድ፤ ሁለቱም በዚያ ጦርነት ውስጥ መኖር ጥሟቸው፤ ፈጥኖ እንዳያልቅባቸው እየቆጠቡ ያካሄዱት ነበር ብሎ ለማሰብ፤ በዓመታት ለጤነኛ እዕምሮ የሚሞከር አይሆንም።
በደፈጣ ውጊያ ተጀምሮ፤ ወደጨበጣ ጦርነት ተሸጋግሮ ውጤት ለማምጣት የሚደረግ የትጥቅ ትግል መጣል መውደቅ፤ መቅደም መቀደም፤ መግፋት ማፈግፈግ፤ ያገኙትን መልሶ ማጣት፤ ከነጭራሹም ለተወሰኑ ጊዜያቶች ከመስኩ እስከመሰወር ተመልሶመ መምጣት፤ የሚያደረስ ውጣ ውረድ ያለበት እሩጫ መሆኑን ከጠቀስኳቸው የሁለቱ አማጽያን የትግል ዘመን በመዘገብነው ልምድ በቂ ግንዛቤ እንዳለን ተስፋ ቀደርጋለሁ። ጥቂት ነገሮችን ላክል፤
የትጥቅ ትግሉ የሚካሄድበት ጊዜ፤ ቦታ፤ የውስጥና የውጭ ሁኔታዎች የሚጫወቱትን ሚናም በቅጡ ማጤን ትልቅ ብልህነት ነው። ለዚህም ከላይ ያነሳዃቸውን ቀደም ሲል በሀገራችን የተደረጉትን ትግሎች እንደምሳሌ ስንወስድ፤ እነዚህ ትገሎች ከየት ነው የጀመሩት? በእነማን መሀከል ሆነው ነበር የሚንቀሳቀሱት? በእነማን ይደገፉ ነበር? መውጫ መግቢያቸው በየት ነበር? እነዚህን ጥያቄዎች በመመለስ ጊዜ አላጠፋም። መልሱን ከልጅ እሰከ አዋቂ የሚያውቀው ስለሆነ፤ ከዚያ ይልቅ አርበኞች ግንቦት 7 የጠቀስኳቸው አማጽያን የነበራቸው አጋጥሚ አለው ወይ? ብለን ብንጠይቅና ከመነሻው ብንነሳ፤ መነሻው በስደት የሚኖርበት የባዕድ አገር፤ መውጫ መግቢያውም ይኸው በስደት የሚኖርበት አገር፤ እርዳታም የሚያገኘው ከዚሁ ካስጠጋው ሃገር፤ ይህ ሃገር የሚያደርገው ድጋፍ ደግሞ ለቀደሙት አማጽያን እርዳታ የሚያጎርፉት በዘይት ብር ከናጠጡ መንተግስታት እንደሚገኘው ዓይነት ሳይሆን፤ ከሚያስተዳድረው ደሃ ሕዝብ ጉሮሮ ተከፍሎ የሚገኝ መሆኑ ሁሉ ተጨማምሮ ሲታይ፤ የአርበኞች ግንቦት 7 ትግል ለፈጣኑም ሆነ ዘግይቶ ለሚመጣው ድል ለመድረስ የሚችለው ነጻነት በናፈቀው ኢትዮጵያዊ ቁርጠኝነት ላይ የተመሰረተ መሆኑ ግልጽ ይመስለኛል።
ስለዚህም ለዚች ማስታወሻ ምክንያት የሆነኝ “ትግሉ በታሰበው ፍጥነት አልተካሄደም” የሚለውን ነጥብ ያነሱት ሰው ትግሉን በሩቁ ሆነው በታዛቢነት በመመልከት ያነሱት ጥያቄ እንዳልሆነ ስለምገምት፤ የሚያደርጉትን እገዛ አጠናክረው ይቀጥሉ፤ በዋናነት የሚፈለገው በትግሉ ማመን ነው። የሚደረገው ትግል ዝም አላሉም ለመባል ያህል የሚደረግ ሳይሆን፤ ውሎም ሆነ አድሮ፤ በእርግጥም የባላጋራን አቅም የሚፈትሽ መሆኑን ማረጋገጥ ነው። ስለዚህም እንግዲህ ዛሬ የሚደረገው ማንኛውም ተጨባጭ ስራ ሁሉ አተኩሮው የመከራውን ጊዜ ለማሳጠር መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ፤ መራዘሙም የትግሉ አካል መሆኑን በሚገባ ማጤኑ፤ በትንሹም በትልቁም ሆደ-ባሻ ሆኖ ተስፋ ከመቁረጥ ያድናል። ይህ አስተሳሰብ አርበኞች ግንቦት 7ን ደጋፊና አባል ብቻ ሳይሆን፤ ማንኛውም ድርጅት ወይም ግለሰብ የነጻነት ታጋይ ሊያጤነው የሚገባ ሂደት ይመስለኛል።
“ዘለዓለም እንደምትኖር ሥራ፤ ነገ እንደምትሞትም አስብ” የሚል ተመክሮ እንዳለ አውቃለሁ፤ አባባሉን ከየት እንደገኘሁት ባላስታውስም። ስለነጻነት ትግሉም “ትግሉን ለማሳጠር ሥራ፤ መርዘም ሊኖር እንደሚችልም አስብ” ቢባል ክፋት አይኖረውም። በነካ እጄ የሚከተለውን ምራቂ ላድርግና ልሰናበት፤-
ሃሳብ
ከትግራይ ሕዝብ ነጻነት ግንባር የባርነት አገዛዝ ነጻ ለማውጣትና የሁሉም የሆነችዋን ዴሞክራሲያዊ እናት አገራችንን – ኢትዮጵያን – ሊያስረክቡን ቆርጠው ለመታገል ለተሰለፉ ተቃዋሚ ድርጅቶች ሁሉ ያለኝ መልዕክት፤-
አንደኛ/ የግድ የዚህንና የዚያን ያህል ጊዜ ጠፍቶበት፤ የዚያና የዚህ አስተባባሪነት ታክሎበት የተዋቀረ የሚለው ትብብር ዓይነት ሳይሆን፤ ምንም ውጣ ውረድ የማያስፈልገው ልታደርጉት የምትችሉት ትብብር እንዳለ ይታለኛል። ይህ ትብብር የሚፈጸመው ተቃዋሚ ድርጅቶቹ ዘረኛውን ስርዓት አስወግዳችሁ የነገይቱን ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን ዕውን ማድረግ አላማችሁ ያደረጋችሁ እስከሆነ ድረስ፤ አንዱ ጠላትን ለመዋጋት የሚከተለውን የትግል ዘዴ አልቃወመውም ማለት ሳይሆን፤ እደግፋለሁ በማለት ትብብርን ማሳየት፤ አልቃወመውም ማለት ብቻውን፤ ትግሉ በለስ ከቀናው በውጤቱ አልጎዳም ከሚል ትርጉም ስለማያልፍ፤ የሚያስከትለው ትዝብት በቀላል የሚታይ አይሆንም።
ሁለተኛ/ በዚህ መደጋገፍ መሃል ደግሞ የሚያጋጭ ነገር ቢፈጠር ግጭቱ የአላማ መዛባትን የሚያሳይ እስካልሆነ ድረስ፤ በምንም ምክንያት በየሚዲያው እየወጡ እንዲህ ሆንኩ፤ እንዲህ ተደረግሁ ማለትን ማቆምና፤ በውስጥ ተነጋግሮ መፍትሄ መስጠት፤
ሶስተኛ/ አንዱ የሚያውቀውና ሌላኛው ያልደረሰበት ጥንቃቄ የሚያስፈልገው ጉዳይ ሲኖርም፤ ማሳሰቢያውን በውስጥ በማስተላለፍ በሚዲያ ላይ ወጥቶ ሃሌ ማለትን ማቆም። የእነዚህ ዓይነቶቹ ትብብሮች ምንም ዓይነት የተለየ ዝግጅት የማይፈልጉ፤ በአመራሮች መካከል በቴሌፎን ተነጋግሮ የሚጨረሱ ናቸው የሚል ዕምነት አለኝ። የሚጫወቱትንም ሚና ቀላል እንደልሆነ መገንዘቡ ጥበበኝነት ነው። ከዚያ አልፎ በየሜዳው ሃሌ ማለት ግን፤ ለጠላት መዝናኛ ከመሆን አያልፍም።
ጥረቴ የታኝን ሃሳብ ከማካፈል አልፎ፤ ትእዛዝ፤ ምክር … ወዘተ የሚል ማንጠልጠያ ተሰጥቶት በምክንያቱ ስራ እንዳትፈቱበት አደራ እላለሁ።
መልካም ጊዜ
ጣሰው አስፋ (tassat@t-online.de)
“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡
Leave a Reply