
- ሟች – ሊደፍራቸው የመጣ ሳውዲ ወጣት
- ገዳይ – ሚስትና ቤቱን የተከላከለ ጎልማሳ
- ፍርድ ሰጭ – ከፍተኛው የሸሪአ ፍርድ ቤት የወንጀል ችሎት
- እነ ሁሴን እንደገና አልተወለዱ ይሆን?
ልክ የዛሬ 3 ዓመት ገደማ ሳውዲ አረቢያ ጅዳ “ሀበሾች ሳውዲ ገደሉ!” ተባለ፣ መረጃውን የሰማሁት እኔም በእስር ላይ እያለሁ ነበር። እንዴት ገደሉ ብየ ስጠይቅ ቤታቸውን ሊዘርፉና የሀበሻውን አባወራ ቤት ሊዘርፉ የገቡ ሳውዲ ወጣቶች ሴቶችን ሊደፍሩ በተነሳ አምባጓሮ መሆኑን በደፈናው ሰማሁ። ከዚያም የቀረውን ተባራሪ የእስር ቤት መረጃ የማጣራበት መንገዱ ዝግ በሆነበት የጨለማ ወቅት ገደሉ የተባሉት ወደሚታጎሩበትና እኔ ወዳለሁበት ወህኒ እስኪመጡ የታሳሪውን ተባራሪ የማያጠግብ መረጃ ሳነፈንፍና ስኮመኩም ከረምኩ። ከሶስት ወር በኋላ እኔ ከወህኒ እስክወጣ ወደ ማዕከላዊው የብሪማን እስር ቤት ሳይመጡ ቀሩ፣ እኔም ጉዳይ ተጣርቶ ለእስር ወጣሁ . . .
ከእስር ከወጣሁ በኋላ ጉዳዩን ከገዳዮች አንደበት የመስማት እድሉ ገጠመኝ “ከንጋቱ ላይ የኢድ በዓልን ልናከብር ስንዘገጃጅ ቤታችን ተንኳኳ፣ ማነው? ስል ፖሊሶች ነን አሉኝ፣ ከፈትኩላቸው። ግብተው ሴትና ወንድ ብለው ለያይተው አስቀመጡን ፣ ዘረፋ ጀመሩ፣ ዝም አልን፣ ቆዩና ሴቶቻችን ለመድፈር ሲሞክሩ የባለቤቴን ጩኸት ሰማሁ ፣ ዘልዬ ከተዘጋው ክፍል ወጣሁና ከወጣቶች ጋር ግብግብ ያዝን፣ …ሟች ሳውዲ ስለት ይዞ ሊወጋኝ ሲሰነዝር የያዘውን ስለት ቀኝቸ ደረቱ ላይ ወጋሁትና ከቤቴ በር ገፍቸ አስወጣሁት፣ ጓደኞቹ ተረባርበው ወሰዱት፣ ፖሊስ ጠርተው ነበርና በፖሊስ ተከበን ተያዝን …ሚስቴን ሊደፍር ስከላከል ብወጋውም ይሞታል አላልኩም ነበር፣ መሞቱን ሰማሁ፣ አዘንኩ …” ይህን ምስክርነት የሰጠኝ የወንጀሉ ተጠያቂ ገዳይ ወንድም ሁሴን ሃሰን ነበር! ታዲያ ያኔ በሞት ፍርደኞች መካከል የጨለማ ህይወትን ሲገፋ በነበረበት በጭንቋ ሰአት ሆን ብየ ነፍስ አላጠፋሁምና ስለፍትህ ድምጻችን አሰማልን ብሎ ተማጽኖኝ ነበር!
ከዚያ ወዲህ ባሉት ጊዜያት የወንደም ሁሴንን ወንድምና የሁለት ጓደኞቹን የፍርድ ሂደት በቅርብ ተከታትተዋለሁ ፣ መረጃም በሰፊው አቀርብበት ነበር። ሳውዲ መተዳደሪያ ባደባደረጋቸው የሸሪአው ህግ “የገደለ ይገድላል” ቢባልም እንኳ የራሱ ስርአትና ደንብ ስለመኖሩ ይህ ውሳኔ ማሳያ ይመስለኛል፣ ግፍ ሲፈጸምበት ራሱን ሲል ገደለ ትበሎ ይገደል እንደማይባል ትልቅ ማሳያ በመሆኑ ብቻ ሳይሆን በስራ ላይ ውሎ በእኛ ዜጎች ላይ ስላየሁት ደስ ብሎኛል። ለዜጎች መብት የምናስብ ከሆነም ይህ አስተማሪ ነው።
የሳውዲ ህግ አያሰራንም ከሚለው ተራ ቱማታ መውጣት ከቻልን ብዙዎችን መታደግ እንደምንችል ምልክት ነው። ይህን እውነት ተከትለን በህግ አግባብ ፍትህ ማግኘት ስላለባቸው የሞት ፍርደኞች መብት ማስከበር ዙሪያ ተወካዮቻችን እንዳለባቸው ጠቋሚ ነው።
እንደ ቀደሙት አመታት በየስብስባው “የሳውዲ ህግ ለመብት ጥበቃው አይመችም” የሚል ስንካላ ምክንያት ከተወካዮቻችን ሲቀርብ መስማት አንሻም። በተለይ በአረብ ሃገራት ያሉ የመንግሰት ተወካዮቻችን ከዚህ ፍርድ ተነስተው ምን እየሰራን ነው ብለው ራሳቸውን መመርመር ይገባቸዋል! ልብ ያለው ልብ ይበል! የጎዳን የሳውዲ ህግ ሳይሆን ህጉን ተከትሎ መብታችን የሚያስከብር ሁነኛ የመንግሰት ተወካይ ነው፣ ደረቅ እውነቱ ይህ ነው። ዛሬ ከምንም በላይ የዘገየው ፍትህ ርትዕ እንዲህ ተከብሮ በማየት ደስ ብሎኛል፣ ነገም ግፍ ተፈጽሞባቸው የታሰሩት ዜጎቻችን ነጻ የሚወጡበት ተስፋ እንዳለ በሚያነላክተው የፍርድ ውሳኔ እርካታ ተስምቶኛል፣ ተደስቻለሁ!
ሁሉንም በወጉ ከነጻ ከተፈቱት ከእነ ሁሴን ጋር ቁጭ ብለን እናዎጋለን፣ ደስታቸውን እንጋራለን፣ የሞት ፍርደኞችን ህይወት ያለ ተስፋ የሚገፋበትን የጨለማውን የእስር ቤት የአመታት ውሎ አዳር በጨረፍታ ማውጋታችን አይቀርም! በእነ ሁሴን ዙሪያ መረጃ ስንለዋወጥ ትብብራችሁ ላልተለየኝ፣ በጸሎት ለረዳችኋቸው ሁሉ እኔም እነሆ Mission Accomplished እያልኩ በደስታ ምስጋናዬን አቀርባለሁ!
በዝርዝር እስክመለስ ወንድም ሁሴንና ጓደኛ፣ ቤተሰቦቹ እንኳን ደስ አላችሁ፣ እንኳን ደስ አለን!
ዛሬም ዜጎቻችን በደል ደርሶባቸው በየወህኒው ይገኛሉ፣ ስለተበደሉት ድምጻችን እናሰማ!
መጋቢት 13 ቀን 2009 ዓም
Leave a Reply