• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ተጋሩን አትንኩት!

July 20, 2016 07:58 am by Editor Leave a Comment

የኢትዮጵያ ፖለቲካ በገባኝ መጠን፡- በአሁኑ ሰዓት ሀገሪቱን የሚመራት ቡድን ራሱን ወደ ገዥ መደብነት ቀይሯል፡፡ በገዥ መደብ ውስጥ የህወሓታዊያን ኃይል ገኖ የወጣ መሆኑ ለክርክር የሚቀርብ ጉዳይ አይደለም፡፡ ይሁንና ገዥ መደቡን “ያጸኑት”’ ሌሎች ኃይሎች እንዳሉ መካድ ያስተዛዝባል፡፡ የፖለቲካ ኃጢያት ትንሽ የለውም፡፡ የምንግዜም የደረጃ ሁለት ተፋላሚዎች የብአዴን ከፍተኛ አመራሮች፤ የአድርባዮ ኦህዴድ ባለ ስልጣናት፤ ሚዛን አስጠባቂዎች የዲኢህዴን ሰዎች እና የአጋር ድርጅቶች ተቀጥላ ምሁራን (auxiliary elites) አሁን ላይ ወደ ዝግ አምባገነንነት እያዘገመ ላለው ገዥ መደብ ማንአህሎኝ ባይነት የራሳቸዉ የሆነ የማይናቅ ሚና አላቸዉ፡፡ የነዚህ ድርጅቶች ቁንጮ መሪዎች የገዥ መደቡ መሐንዲሶች ናቸው፡፡ ዛሬ ላይ ላለዉ በደልና ጭቆና ዋነኛ ተጠያቂዎችም የገዥዉ መደብ የፖለቲካ መሀንዲሶች ናቸዉ፡፡

በርግጥ አገዛዙ አራት ኪሎ ላይ እግሩን ከተከለበት ግዜ በተለይም ካለፈው አስር ዓመት ወዲህ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ተጋሩዎች የኢኮኖሚ የበላይነት አሳይተዋል፡፡ አንጻራዊ የመንግስት ቁልፍ ቢሮክራሲ ቦታዎችንም ተቆጣጥረዋል፡፡ ግና፤ እነዚህ የገዥው መደብ አባሪ ተባባሪዎች ብዙሃኑን ተጋሩ ይወክላሉ (?) ብሎ ማሰብ የወቅቱ ጥያቄ ነው፡፡ በአሁኑ ሰዓት በአባይ ወልዱ ክልላዊ መንግስት መረጃ መሰረት ስምንት መቶ ሰባ ሺህ የሚሆኑ ዜጎች የምግብ እህል እጥረት አጋጥሟቸዋል፡፡ በየጊዜው ስንዴ፣ ዘይትና አልሚ ምግቦችን በቤተሰብ ብዛት ልክ የሚረዱ ናቸው፡፡ በአንፃሩ የተሻለ አምራች ነው የሚባለው የምዕራብ ትግራይ አካባቢ እንኳ በ2007/8 የምርት ዘመን አጥጋቢ ምርት ወደ ገብያ ሊያወጣ አልቻለም፡፡ ምስራቁን የትግራይ ክፍል እንኳ ብንረሳው ይሻላል፡፡ በከተሞች የሥራ አጡ ቁጥር ከክልሉ ህዝብ ብዛት አኳያ ሲታይ አስፈሪ ያደርገዋል፡፡ ስደት ብቸኛው መፍትሔ እስኪመስል ድረስ ብዙ ትግራዋያን ወጣቶች በሱዳን በኩል እየወጡ የሳራህ በርሃና የሜዲትራሊያን ባህር ሲሳይ በመሆን ላይ ይገኛሉ፡፡ የተሳካላቸው “ኤርትራዊ ነኝ” በሚል በምዕራቡ አለም ለጥገኝነት ጎዳናዎችን ያጨናንቃሉ፡፡

በበኩሌ ትግራዋያንን ባሰብኩ ቁጥር ከመለስ ዜናዊ አገር አፍራሽነት ይልቅ ራስ ስዩም መንገሻ ለሀገረ-መንግስት ግንባታው የከፈለው ዋጋ ጎልቶ ይታየኛል፤ ከሽማግሌው ስብሐት ነጋ ከፋፋይ የፖለቲካ ሚና በተሻለ መልኩ የገሰሰ አየል (ስሁል) የትግል አበርክቶ አይረሴ ይሆንብኛል፡፡ ከሳሞራ የኑስ የትግራይ ብሔርተኝነት ማንአህሎኝነትና ትምክህት በላይ የኃየሎም አርዓያ አልበገር ባይነት ደምቆ ይታየኛል፤ ከነጋዴዋ አዜብ መስፍን የላሸቀ ስብዕና ይልቅ የአደይ አረጋሽ አዳነ የትግል ፅናትና ህዝባዊ ፍቅር ውስጤን ያሞቃዋል፡፡ ከጌታቸው ረዳ ረብ-የለሽ ድስኩር እነ አብረሃ ደስታ፣ አስራት አብረሃም፣ አምዶም ገ/ሰላሴ … ህዝባዊ ስሜትና የመረጃ ተደራሽነት ትጋት በሀገሬ ፖለቲካዊ ተስፋ እንዳልቆርጥ ብረታት ይሰጠኛል፡፡

ትግራይ በቀደመው ዘመን የኢትዩጵያ የስልጣኔ ራስ ነበረች፡፡ ትግራይን አልባ የኢትዩጵያን ቀደምት ስልጣኔ ማስታወስ ከፊልነትን የተሻገረ ሙሉ ቅዥት ነው፡፡ የኢትዩጵያን የቀደመ የግዛት አንድነትና ሉአላዊነት አስጠብቆ ለማቆየት ከተዋደቁ ጀግኖች ውስጥ፡-

‹‹…ከነፋስ የፈጠነ

በወንድነቱ የተማመነ

ክንዱ ብርቱ እንዳንበሳ

በጠላት ሠፈር የሚያገሳ››

የተባለለት ጀግናው አዋጊ ራስ አሉላ አባነጋን ጨምሮ ብዙም ያልተዘመረላቸው የኢትዮጵያ ግዛትና ሉዓላዊነት ባለውለታዎች ከትግራይ ምድር እንደፈለቁ መካድ ከህዋሓት የክህደት ጉዞ የሚተናነስ አይደለም፡፡ የባንድነት ቃለ-ትርጓሜ ተጋሩን አስታኮ ‹‹እየተብራራ›› መምጣቱ ብሎም ጉዳዩ ከኢ-መደበኛ ወግ ወደ መደበኛነት ለመሸጋገር መውተርተሩ የተካደውን መካድ (denial of defrayal) በሚባለው የታሪክ በሽታ ተጠቂው እየበዛ ለመምጣቱ አብይ ማሳያ ይሆናል፡፡ የሀሳብ ተገላባባጩ አፈወርቅ ገ/የሱስ (ለኢጣሊያን ያደረ ባንዳ) ጎንደሬ እንደነበረ ብዙ ግዜ ሲጠቀስ አይታይም፡፡ በሌላው አካባቢ የአደባባይ ሰዎች ከነበሩት ውስጥ ለባዕድ ስርዓት ተገዥና አስገዥ የነበሩ ሰዎች የተጋሩዎችን ያህል ስማቸው ሲነሳና ሲወቀሱ አይስተዋልም፡፡ ምሁራዊ ድባቡ ማንነትን ማጠንጠኛው እያደረገ በመጣበት በአሁኑ ሰዓት የፕሮፖጋንዳ ማሽኖች የአንድ የፖለቲካ ድርጅት መሪዎችን ለማጥቃት ሲባል የብዙሃኑን ታሪክ መደፍጠጥ አመክንዮ የጎደለው ደካም እርምጃ ነው፡፡ የትም የማያደርስ፡፡ አንካሳ፡፡

አንድ እውነት እንቀበል፡፡ ኢትዩጵያ የበዙ የቀደሙ የመበታተን የታሪክ ፈተናዎችን አልፋለች፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ የትግራዋያን ሚና ቀላል አልነበረም፡፡ በትግራውያን ከተበደልነው በላይ የተጠቀምነው ያመዝናል (የቀደመውን የኢትዩጵያን ታሪክ ከዘውጋዊ ማንነት የታሪክ ማስተንተኛ ማዕቀፍ ውጪ ለማየት የሚሞክር ነፃ ግለሰብ የማይክደው ሃቅ ነው) ዛሬ ላይ ዋነኛው በዳያችን የገዥ መደቡ ምሰሶ የሆነው ህዋሓት ነው፡፡ በዳዩን ለይቶ ማጥቃት የተበዳይ ጥልቅ መሻት ነውና በዳዩ ላይ ትኩረት ማድረጉ የተሻለ ነው፡፡ ህዋሓታዉያኑ የሚጋሩትና ሊሞቱለት የሚፈቅዱት አንድ ቡድናዊ ምክንያት አላቸው፡፡ እርሱም፡- በገዥው መደብ ውስጥ ያላቸውን የፖለቲካ የበላይነትና የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ለማስቀጠል፤ ብዙሃኑ ተጋሩ ግን ከሌላው የኢትዩጵያ ህዝብ ጋር የሚጋራውና ሊሞትለት የሚችል የነፃነት ጥማት አለው፡፡

ሌላ እዉነትም እንመርምር፡- ያች የስልጣኔ እምብርት ዛሬ ላይ በህወሓት አጋፋሪነት የፖለቲካ ደናቁርትና የኢኮኖሚ በዝባዥ ጠቅላይ አገልጋዮች መፍለቂያ ብትሆንም ለኢትዩጵያችን አብርሆትን የሚመኙ ባህሩያን (ሊሂቃን) እንዳሉ መዘንጋት የለብንም፡፡ ደናቁርትና በዝባዦች ብዙሃኑን አይወክሉም፡ ብዙሃኑ ተጋሩ ራሱን ከገዥ መደቡ ህወሓት የነጠለ መሆኑን በተግባር እንዲያሳዩ መንገዱን መጥረግ ብሎም አስተቃቃፊ የህዝባዊ ንቅናቄ አጀንዳዎችን መቅረጽ የጋራ የቤት ሥራችን ሊሆን ይገባል፡፡ በተረፈ ብዙዎች እየወደቁለት ያለዉን የነፃነት ትግል ኪ-ቦርድ በመነካካት ለማቃለል መሞከርም ሆነ የነፃነት ትግሉን አንድ ብሔር ለመጨፍለቅ ያለመ አድርጎ መተርጎሙ ‹‹ያላዋቂ ሳሚ…›› እንደሚሉት ይመስላል፡፡ እናም የሳይበር አርበኞች ኳስ በመሬት አድርጉ፡፡ ሁሉም ማህበራዊ ፍትህ ናፋቂ፣ የነፃነት ረሀብተኛ ጣቱን ተጋሩ ላይ ከመቀስር ይልቅ የገዥው መደብ በተለይም የፖለቲካ መሀንዲሶቹና የኢኮኖሚ ጥቅመኞቹ  ላይ ትኩረት በማድረግ ህዝባዊ እምቢተኝነቱን ማቀጣጠሉ አብይ የቤት ሥራችን ይመስለኛል፡፡ የወልቃይት ጠገዴ የአማራነት የማንነት ጥያቄ ህገ-መንግስታዊ ጥያቄ ነዉ፡፡ ጉዳዮ ከገዥዉ መደብ ውድቀት በኃላ በህዝበ ዉሳኔ እልባት እንዲያገኝ ማድረግ ይቻላል፡፡ አሁን ባለዉ ነባራዊ ሁኔታ ታሪካዊ ሰነዶችንም ሆነ ህዝባዊ ፍላጎቱን መሰረት ያደረገ መፍትሄ ይሰጣል ብሎ ማሰብ የወህነት ይመስላል፡፡ ለግዜዉም ቢሆን የወልቃይት ጠገዴ የአማራነት የማንነት ጥያቄ በመላ አገሪቱ ለታፈነዉ አመጽ ማነቃቂያ ደወል ሆኖ እያገለገለ ነዉ፡፡ምናልባትም የፌደራሊዝሙ ዲያሌክቲክ ኢ-ተቀልባሽ በሆነ መንገድ ገኖ እየወጣ እንደሆነ የሰሞኑ ጉዳይ ጉምቱ ማሳያ ይሆነናል፡፡ ዲያሌክቲኩን በማጎን አቻቻይ የፖለቲካ ሥርአት የሚወልድ ሲይንቴስስ (synthesis) ለመፍጠር እንደሌላዉ የኢትዮጵያ ህዝብ ማህበራዊ ፍትህና ነጻነት የተጠማዉን ተጋሩ የዲያሌክቲኩ (ቴንሰሱ) አካል ማድረግ አቋራጭ የድል መንገድ ነዉ፡፡ በፖለቲካዉ አለም ከስሜት ይልቅ ስሌት የድል ማፍጠኛ ነዉ እናም ተጋሩን ለቀቅ የገዥዉን መደብ ምሰሶ ጠበቅ ማድረጉ የተሻለ ይሆናል፡፡

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!


“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡

Filed Under: Opinions Tagged With: Left Column

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

Recent Posts

  • ለሱዳንና ኤርትራ ሲከራከሩ የነበሩት አበባው ባለመመረጣቸው “በጣም ተድጃለሁ” አሉ June 26, 2026 12:29 am
  • “ትህነግ ወደ ዓለምአቀፍ ወንጀለኛነትና አሸባሪነት እየተምዘገዘገ ነው” June 25, 2026 01:00 am
  • አሜሪካ በሕገወጡ ትህነግ አመራሮች ላይ ጠንካራ የቪዛ እገዳ ጣለ June 18, 2026 10:29 am
  • እንደ ሌሊት ወፏ የሚንቀሳቀሰው ኢህአፓ/ትብብር   June 18, 2026 09:36 am
  • የታርጋ ጫጫታ June 15, 2026 05:16 pm
  • ፋንታኹን ዋቄ ከአሜሪካ የሃይማኖት እልቂት አወጁ June 15, 2026 02:12 am
  • ሕገወጡ ትህነግ ወጣቶችን ለዳግም ዕልቂት እያሰናዳ ለፈረንጆች “ኢትዮጵያን አውግዙልኝ” እያለ ነው June 11, 2026 12:57 am
  • በሐዘንና ግልፅ ደብዳቤ ስም የተሸፈነ የድህረ ምርጫ ሀገር የማተራመስ ስትራቴጂ June 10, 2026 12:19 am
  • የጽምዶ ልክፍት June 9, 2026 12:49 am
  • ገዳዩ ማነው? አስገዳዩስ ማነው? June 5, 2026 02:37 pm
  • ጽንፈኝነት ግን በኢትዮጵያ ምድር ፈጽሞ ቦታ የለውም! June 5, 2026 01:47 pm
  • የትብብሩ “ብናሸንፍም ፓርላማ አንገባም” መግለጫ “ወንበር ስታጡ ነው” የሚል ከፍተኛ ተቃውሞ አስነሳ June 4, 2026 12:04 am
  • አዲሱ የትራምፕ የምርጫ መመሪያ፡ የአሜሪካ ዲፕሎማቶችን አፍ ያስዘጋ፤ ተቃዋሚዎች ተስፋ ያስቆረጠ June 3, 2026 08:50 pm
  • “ኢህአፓ ከምርጫው በኋላ ይሰነጠቃል” May 29, 2026 07:07 pm
  • ሪፖርተር፡ “ስውር ተልዕኮ” – በከባድ ወንጀል ሊከሰስ May 6, 2026 11:55 pm
  • የፋኖ ኃይል በደረሰበት ጉዳት ሃምሳ ሺህ የሚጠጋ ትጥቅ ጥሎ ጠፋ April 29, 2026 02:27 pm
  • አዲሱ የቴድሮስ ካሳሁን 888 ኮድ፤ እንደ 666?! April 15, 2026 05:53 am
  • ምኑ ነው ያሳቃችሁ፤ ያስደሰታችሁ? April 2, 2026 10:52 am
  • የጀዋር መሃመድ የፖለቲካ ማንነት እና የባዕዳን ተልዕኮ April 2, 2026 10:16 am
  • ከግብፅ በዳያስፖራ ትርምስ ጠማቂዎች በኩል ፋኖ ወደ አዲስ አበባ የላከው “ስጦታ” March 27, 2026 09:14 am
  • “ሰላማዊ ታጋዮቹ” እነ ልደቱ ከአራጁ ሸኔ ጋር ተጣምረዋል March 25, 2026 01:04 pm
  • ጸረ-ኢትዮጵያዊ የሆነው የሪፖርተር አዘጋገብ March 19, 2026 11:54 am
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ የኦሮሚያ የልማት ድርጅቶች March 18, 2026 10:48 am
  • የጃኖ ስጦታና የዶሮ ፖለቲካ በጎንደር March 10, 2026 09:24 am
Copyright © 2026 · Goolgule