• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

እረኛ የሌለው ከብት እና መሪ የሌለው ሕዝብ አንድ ናቸው

May 10, 2015 05:57 am by Editor Leave a Comment

ባለፈው የአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ከኢትዮጵያ ውጪ በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ላይ በተደጋጋሚ የደረሱባቸው ከፍተኛ ሰቆቃዎች አሉ። አምና በሣዑዲ ዓረቢያ፣ ባለፉት ሁለት ወራት ደግሞ በየመን በሚኖሩ የዕለት እንጀራ ፈላጊ በሆኑ በመቶ-ሺዎች በሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ላይ የተጸፈመባቸው ግፍ የተሞላበት ግድያ እና ስቃይ፣ መንስዔው ኢትዮጵያ መሪ አልባ አገር በመሆኗ ነው። የደረሰው ሳይበቃ፣ በዚህ ምክንያትም ኢትዮጵያውያን ከደረሰብን መከራ ሳናገግም፣ ስቃዩ እና አሟሟቱ ከዐይናችን ሥር ሳይጠፋ፣ እናቶች የለበሱት የሐዘን ጨርቅ ሳይለወጥ፣ ሌላ መዓት በደቡብ አፍሪቃ በሚኖሩ መሪ አልባ ወንድም እና እህቶቻችን ላይ የተፈጸመው አሠቃቂ ግድያ የንብረት መውደም ተከተለ። ሰሞኑን ደግሞ ኢትዮጵያዊ እና ክርስቲያን በመሆናቸው ብቻ፣ ፴(ሰላሣ) ኢትዮጵያውያን በሊቢያ እስላማዊ ጽንፈኞች እንደገና ጠቦት መታረዳቸውን በዘመኑ ቴክኖሎጂ ዐየነው ሰማነው። በእነዚህ ድርጊቶች መላው የሞረሽ ወገኔ ዐማራ ድርጅት አባሎች የተሰማን ስሜት በቃላት ይኸን ይመስላል ብሎ ለመግለጽ የሚያስቸግር ነው። በድርጊቶቹ ልባችን ደምቷል፣ እጅግ አዝነናል፣ ተክዘናል፣ ተናድደናል፣ ተቆጭተናል። የሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት አባሎች እና ደጋፊዎች፣ ለሞቱት ወንድም እና እህቶቻችን አምላክ መንግሥተ ሰማያትን እንዲያወርስልን፣ ለተጎጂ ወገኖቻችን መጽናናትን እንዲሰጥልን የኃዘን ተካፋይነታችንን እንገልጻለን።

ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት፣ በሣዑዲ ዓረቢያ፣ በየመን፣ በደቡብ አፍሪቃ እና በሊቢያ በኢትዮጵያውያን ላይ ለተፈጸመው እጅግ ዘግናኛ እና አሠቃቂ ግድያ የድርጊቱ ፈጻሚዎች የየተጠቀሱት አገሮች መንግሥታት እና ዜጎች ስለሆኑ ቀዳሚ ኃላፊነቱ የእነርሱ እንደሆነ ያምናል። ሆኖም እንዲህ ዓይነት ድርጊቶች በኢትዮጵያውያን ላይ እንዲፈጸሙ፣ ኢትዮጵያውያን በዓለም ላይ የነበረንን ክብር እና ዝና አዋርዶ ለዚህ ዓይነቱ ጥቃት ያጋለጠን፣ አንድነት እና ሰላማችን አሳጥቶ ለስደት እና ለመከራ የዳረገን፣ የትግሬ-ወያኔ ዘረኛ አገዛዝ እና የሥርዓቱ አራማጆች መሆናቸውን ልብ ልንል እንደሚገባ ሞረሽ-ወገኔ ለማስገንዘብ ይወዳል። እነዚህ በሊቢያ እስላማዊ ጽንፈኞች የተገደሉ ወንድሞቻችን ኃይማኖታቸው ምንም ይሁን ምን፣ የታረዱበት ምክንያት «ክርስቲያን ናችሁ» የሚል በመሆኑ ብቻ ለኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ኃይማኖት ሰማዕታት ናቸው ብሎ ሞረሽ-ወገኔ በጽኑ ያምናል። ስለዚህም ዘወትር ሕዝበ ክርስቲያኑ በፀሎቱ ሊያስባቸው፣ በኃይማኖቱ ሥርዓትም አስፈላጊው የፍትኃት መታሰቢያ ሊደረግላቸው እንደሚገባ ሞረሽ-ወገኔ በአፅንዖት ያሳስባል።

ኢትዮጵያውያን በዛሬው ዘመን ሥቃይ እና መከራ ለሚቀበሉባቸው አገሮች ሕዝብ፣ በታሪክ ወደኋላ ሄዶ እኛ ምን ዓይነት በጎ ተግባር እንደፈፀምንላቸው ማውሣት ይቻላል። ዛሬ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖችን በአሰቃቂ ሁኔታ የሚያርዱት እና በጥይት ደብድበው የሚገድሉት ሊቢያውያን፣ ከ፪ኛው የዓለም ጦርነት ማግሥት በኋላ ለሦሥት ተከፋፍለው (ትሪፖሊታኒያ፣ ፌዛን እና ሴሬናይካ) በጣሊያን፣ በፈረንሣይ እና በእንግሊዝ ቅኝ ግዛትነት እንዲገዙ የኃያላን መንግሥታት ፍላጎት እና ዕቅድ ነበር። ሆኖም ታላቁ ኢትዮጵያዊ ዲፕሎማት እና ፖለቲከኛ ፀሐፌ-ትዕዛዝ አክሊሉ ኃብተወልድ እና አጋሮቻቸው ባደረጉት ከፍተኛ ዲፕሎማሲያዊ ትግል ሊቢያ ከታሰበላት የዳግም ቅኝ አገዛዝ ሤራ ነፃ ለመውጣት በቃች። የዛሬን አያድርገውና፣ ኢትዮጵያውያንን የመኪና ጎማ በአንገታቸው እያጠለቁ የሚያቃጥሉት ደቡብ አፍሪቃውያን፣ በአፓርታይድ አገዛዝ ሥር በነበሩበት ዘመን፣ ከሟቹ መሪያቸው ከፕሬዘዳንት ኔልሰን ማንዴላ ጀምሮ እስከ ተራ የአፍሪቃ ብሔራዊ ኮንግረስ ተዋጊዎች እና ቤተሰቦቻቸው ድረስ የኢትዮጵያውያን የተከበሩ እንግዶች ነበሩ። ከ፲፱፻፶ዎቹ አጋማሽ በኋላ በነዳጅ ሽያጭ ገንዘብ ናላቸው የዞረው አረቦች፣ ከ፷(ስድሣ) ዓመታት በፊት በገፍ በሚሰደዱበት ዘመን በቅድሚያ መጠለያቸው ኢትዮጵያ ነበረች። «ወርቅ ላበደረ ጠጠር፣ እህል ላበደረ አፈር» ሆነና ዛሬ ኢትዮጵያውያን በዓለም በየትኛውም ክፍል በስደት ለመኖር እንኳን የማንችልበት ደረጃ ላይ ደርሰናል። ስለሆነም ለሚደርሱብን የግፍ ጥቃቶች ምክንያቶቹን መርምረን ተገቢ እርምጃዎችን መውሰድ የእኛ የዘመኑ ኢትዮጵያዊ ትውልድ ኃላፊነት ነው።

በታሪካችን ኢትዮጵያውያን እንደዚህ ዘመኑ ያለ መረገጥ እና መጨቆን፣ መከራ እና ስቃይ፣ ውርደት እና መናቅ፣ መንቋሸሽ እና ከሰውነት በታች መታየት፣ ስደት እና መንከራተት፣ ወዘተርፈ ገጥሞን አያውቅም። አውቀነውም ይሁን ሳናውቀው፣ አምነንም ሆነ ተገደን፣ ለዚህ ሁኔታ በራሳችን ላይ መድረስ እያንዳንዳችን የየበኩላችንን አስተዋጽኦ አድርገናል። እንደ ሰንበት ጠበል ጸዲቅ በቋንቋ ሲሸነሽኑን፣ ታሪካችን ሲደልዙ፣ ባሕላችን ሲያንቋሽሹ፣ አንድነታችን ሲንዱ፣ የወል እሴቶቻችን ሲያወድሙ «ኧረ-ለምን?» አላልንም። የትግሬ ነገድ ልሂቃን ዘመን ጠገብ ታሪካችንን በመቶ ዓመት ሲገድቡ፣ ኤርትራን አስገንጥለው አገራችንን ወደብ አልባ ሲያደርጉ፣ ድንግሉን መሬታችን ለሱዳን በገጸ-በረከትነት ሲቸሩ፣ በአጠቃላይ ለ፳፬(ሃያ አራት) ዓመታት በአገሪቱ እና በሕዝቡ ዕጣ-ፋንታ ላይ እንዲወስኑ ዕድሉን ሰጥተናቸዋል። በዚህ ጊዜ ውስጥ ለፈጸሙት ማናቸውም ነገር የተቀነባበረ እና የተዋሐደ፣ ወጥ የተቃውሞ እና የእምቢተኝነት ስሜት አላሣየንም። ስለዚህ ይህ በሣዑዲ ዓረቢያ፣ በየመን፣ በደቡብ አፍሪቃ እና በሊቢያ በወንድሞቻችን እና በእህቶቻችን ላይ የተፈጸመው ግፍ እንዲፈጸም የራሣችን ቸልተኝነት የበኩሉን አስተዋጽዖ አላደረገም ለማለት አይቻልም።

ከሁሉም በላይ በሐረርጌ፣ በአርሲ፣ በወለጋ፣ በኢሉባቡር፤ በወልቃይት፣ በጠገዴ፣ በጠለምት፤ በሰቲት እና በሌሎችም የኢትዮጵያ ክፍሎች የዐማራ ነገድ አባሎች የሴቶች ጡት ሲቆረጥ፣ የወንዶች ብልት ሲሰለብ፣ ከነሕይዎታቸው ወደ ገደል ሲጣሉ፣ እርጉዞች ሆዳቸው ተቀድዶ ሽል ሲሰለብ፣ ማንም ከቁብ የቆጠራቸው የለም። በመተከል (ጉምዝ) እና በአሶሳ (ቤንሻንጉል)፣ በጉራ ፈርዳ፣ በወለጋ፣ በአምቦ እና አካባቢው፣ በአርሲ ነገሌ፣ ወዘተርፈ ነዋሪ በነበሩ ዐማሮች ላይ ዐማራ በመሆናቸው ብቻ ተነጥለው፣ በዘመን ፍሰት ያፈሩትን ሀብት እና ንብረት «ደጃፍ በመለሰ፣ ማጀት በጎረሰ» ተነጥቀው ሲባረሩ እና ለልምና እና ለችጋር  ሲዳረጉ ያሰማነው ቃል አልነበረም። ስለሆነም «ሞት በእንቅልፍ ይለመዳል» እንዲሉ፣ የትግሬ-ወያኔ በኢትዮጵያ፣ በኢትዮጵያዊነት፣ በዐማራ እና በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ኃይማኖት ላይ ያለውን እጅግ የከረረ ጥላቻ በፕሮግራም ነድፎ የተሰለፈ መሆኑን በተጋጋሚ እየነገረን እና እያወቅን፣ «ልክ አይደለህም» የማለቱ ወኔው እና ቁርጠኝነቱ አንሶን፣ ዛሬ «እሪ! ድረሱልን!» ለምንልለት መከራ ደርሰናል።

የቦታ፣ የገዳዮች፣ እንዲሁም የተገዳዮች ማንነት እና ቁጥር ከመለያየቱ በስተቀር፣ በሣዑዲ ዓረቢያ፣ በየመን፣ በደቡብ አፍሪቃ እና በሊቢያ በኢትዮጵያውያን ላይ የተፈጸመው ግድያ እና የደረሰባቸው ስቃይ፣ የትግሬ-ወያኔ በዐማራው ነገድ ተወላጆች ላይ ካደረሰው የተለየ አይደለም። ባለፉት ፳፬(ሃያ አራት) ዓመታት ብቻ የትግሬ-ወያኔ ከ፭(አምሥት) ሚሊዮን የማያንሱ ዐማሮችን ከምድረ-ገፅ አጥፍቷል። ከዚህ ቁጥር ውስጥ ግማሹን (2.5 ሚሊዮን) ያህል ዐማራዎችን ማጥፋቱን የትግሬ-ወያኔ በራሱ ፓርላማ ተብዬ አምኗል። ከእኒህ ውስጥ በአሰቦት ገዳም፣ በበደኖ፣ በአርባ ጉጉ፣ በወተር፣ በአረካ ወዘተርፈ የትግሬ-ወያኔ በዐማራው ነገድ ላይ የፈጸመውን ግፍ በዐይናችን እያየን፣ በጆሮአችን እየሰማን፣ ስለድርጊቱ ከተለያዩ ዘገባዎች እያነበብን፣ ዝምታን፣ አልፎ አልፎም «እንኳን ደግ አደረገ» እያልን መከራውን መላመዳችንን መካድ የለብንም። በመሆኑም ኢትዮጵያውያን «ከመሞት መሰንበት» ብለው በሚሊዮኖች ወደውጪ አገሮች ለመሰደድ ተገድደዋል። መሰደድም እንደ ቅንጦት ተቆጥሮብን ይኼውና ዛሬ ዘር ሳይለይ ሁሉንም ተሰዳጅ ኢትዮጵያውያን፣ ኢትዮጵያዊ በመሆናችን ብቻ በዚህ ፳፩ኛው(ሃያ አንደኛው) ክፍለዘመን ይፈጸማል ተብሎ ለማይገመት ጥቃት ተጋላጭ እንድንሆን አድርጎናል። አጋላጫችን ማንም ሳይሆን የትግሬ-ወያኔ አገዛዝ ነው። ስለሆነም የወያኔ ትውልድ እና እምነት ተከታዮች በኢትዮጵያ በፖለቲካ ሥልጣን ላይ እስካሉ ድረስ፣ በኢትዮጵያውያን ላይ የሚፈጸሙት እንዲህ ዓይነት ድርጊቶች መቼም ይቆማሉ ብሎ ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት አያምንም።

በመጽሐፍ ቅዱስ እንደተጻፈው፣ ኢዮሱስ ክርስቶስ ሲያስተምር፣ መቶ በጎች ያሉት እረኛ፣ ካሉት በጎች አንዷ ብትጠፋው፣ ዘጠና ዘጠኙን ትቶ፣ የጠፋችውን አንዷን በግ ፍለጋ መሄዱን ነው። ብዙ ንብረት አለኝ ተብሎም ጥቂቱ እንዲጠፋው የሚፈልግ ማንም ሰው የለም። መጀመሪያ እንዳይጠፋ ጥበቃ እና ጥንቃቄ ይደረጋል። ይህ ሁሉ ተደርጎም የመጥፋት አጋጣሚ ከተፈጠረ፣ የጠፋውን ለማግኘት መፈለግ የተለመደ ነው። ይህ በዓለማዊውም ሆነ በመንፈሣዊ ሕይዎት እና ኑሮ የተለመደ የመልካም እረኛ ተግባር ነው። ሰነፍ እረኛ መንጋውን አንድም ለአራዊት፣ ሁለትም ለርሃብ እና ለውኃ ጥም ያጋልጣል። የጠፉትንም መንጋዎች ለመፈለግ እጅግም አይጥርም። ከጅምሩ ሰነፍ ነውና ለጥፋት እንጂ፣ ለጥበቃ ዝግጁ ባለመሆኑ! ብሔራዊ ስሜት፣ የሕዝብ ፍቅር እና አመኔታ የሌለው ገዢም በሕዝብ ጫንቃ ላይ ሲወጣ፣ ገና ከጅምሩ በሕዝብ ፈቃድ እና ይሁንታ ለያዘው ኃላፊነት ያልበቃ በመሆኑ፥ ለጥፋት፣ ለሕዝብ መበደል፣ መገደል፣ መሰደድ፣ መታሰር፣ መሰቃየት፣ መራብ፣ መቸገር፣ ወዘተርፈ ግድ የለውም። እንዲያውም የጥፋቱ እና የችግሩ፣ የግድያው እና የእስራቱ፣ የስቃዩ እና የመከራው ዋና ተዋናይ እርሱ ይሆናል። ባለፉት ፳፬(ሃያ አራት) ዓመታት የትግሬ-ወያኔ በዘረጋው የዘረኝነት ፖለቲካ ምክንያት፣ ኢትዮጵያውያን በአገራችን የመኖር እና የመሥራት መብቶቻችን ተነጥቀናል። ስለዚህም ኢትዮጵያውያን የሚደርስብን መሳደድ፣ መገደል፣ መዋረድ፣ በየትም ቦታ ከአጥፊ እንስሳዎች በታች በሆነ ሁኔታ መታረድ፣ በበረሃ እና በውቅያኖስ ውስጥ የየብስ እና የባሕር አራዊት ቀለብ መሆን ዕጣ ፋንታችን ሆኗል። ለዚህ ሁሉ ያበቁን መልካም መሪ መሆን ቀርቶ፣ ክፉ ጎረቤት ለመሆን የማይበቁ ሰዎች በአገሪቱ እና በሕዝቡ ጫንቃ ላይ በመውጣታቸው ነው።

የተከፋፈለ ሕዝብ ምንጊዜም ለጠላቶቹ በቀላሉ ተጠቂ ነው። እኛ ኢትዮጵያውያን የሚደርስብን ጥቃት በዕውነት ከመረረን፣ ከጥቃት መውጣት የምንችለው የትግሬ-ወያኔ የሰረቀንን አንድነት መልሰን ስንረከብ ነው። ለወደፊትም በኢትዮጵያውያን ላይ ተመሣሣይ ጥቃት እንዳይፈጸም፣ ስደት እና ሥቃይ እንዲቆም፣ ብሔራዊ ውርደት ተወግዶ በመካከላችን የነበረው የጥንቱ የአንድነት እና የአብሮነት ስሜት እንዲጎመራ፣ የመከራችን እና የስቃያችን ቀፍቃፊ፣ የእኛነታችን ፀር የሆነው የትግሬ-ወያኔ አገዛዝ መወገድ አለበት ብለን እናምናለን። ሠሞኑን የአዲስ አበባ ነዋሪዎች በሠላማዊ ሰልፍ ላይ እንዳሉት፦ «መሪ የሌለው እዚህ [ኢትዮጵያ] ብቻ ነው»። ስለዚህ ኢትዮጵያውያን ከገባንበት የታሪክ ማጥ ለመውጣት መልካም እና ቅን ኢትዮጵያዊ መሪ ሲኖረን ይገባል። ለዚህም በግፍ በባዕድ አገር ደማቸው የፈሰሰው የንፁሐን ሰማዕታት ዜጎቻችን አምላክ ይርዳን። «ሁሉም ነገር ለበጎ ነው» የሚባል ነገር አለና፣ የደረሰብን ይህ ሁሉ ክፉ እና አሰቃቂ ድርጊት፣ የእኛን ኅብረት እና አንድነት መልሶ በማጎናጸፍ፣ መከራ እና ስቃይ፣ ስደት እና ዋይታ፣ ብሔራዊ ውርደት ታሪክ የሚሆኑበትን መንገድ ሁላችንም በያለንበት እንድንጠርግ አደራ እንላለን።

ኢትዮጵያ በታማኝ እና ቆራጥ ልጆቿ መስዋዕትነት ለዘለዓለም ፀንታ ትኖራለች!

ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት

mwaoipr@gmail.com

Filed Under: Opinions Tagged With: Left Column

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

Recent Posts

  • ለሱዳንና ኤርትራ ሲከራከሩ የነበሩት አበባው ባለመመረጣቸው “በጣም ተድጃለሁ” አሉ June 26, 2026 12:29 am
  • “ትህነግ ወደ ዓለምአቀፍ ወንጀለኛነትና አሸባሪነት እየተምዘገዘገ ነው” June 25, 2026 01:00 am
  • አሜሪካ በሕገወጡ ትህነግ አመራሮች ላይ ጠንካራ የቪዛ እገዳ ጣለ June 18, 2026 10:29 am
  • እንደ ሌሊት ወፏ የሚንቀሳቀሰው ኢህአፓ/ትብብር   June 18, 2026 09:36 am
  • የታርጋ ጫጫታ June 15, 2026 05:16 pm
  • ፋንታኹን ዋቄ ከአሜሪካ የሃይማኖት እልቂት አወጁ June 15, 2026 02:12 am
  • ሕገወጡ ትህነግ ወጣቶችን ለዳግም ዕልቂት እያሰናዳ ለፈረንጆች “ኢትዮጵያን አውግዙልኝ” እያለ ነው June 11, 2026 12:57 am
  • በሐዘንና ግልፅ ደብዳቤ ስም የተሸፈነ የድህረ ምርጫ ሀገር የማተራመስ ስትራቴጂ June 10, 2026 12:19 am
  • የጽምዶ ልክፍት June 9, 2026 12:49 am
  • ገዳዩ ማነው? አስገዳዩስ ማነው? June 5, 2026 02:37 pm
  • ጽንፈኝነት ግን በኢትዮጵያ ምድር ፈጽሞ ቦታ የለውም! June 5, 2026 01:47 pm
  • የትብብሩ “ብናሸንፍም ፓርላማ አንገባም” መግለጫ “ወንበር ስታጡ ነው” የሚል ከፍተኛ ተቃውሞ አስነሳ June 4, 2026 12:04 am
  • አዲሱ የትራምፕ የምርጫ መመሪያ፡ የአሜሪካ ዲፕሎማቶችን አፍ ያስዘጋ፤ ተቃዋሚዎች ተስፋ ያስቆረጠ June 3, 2026 08:50 pm
  • “ኢህአፓ ከምርጫው በኋላ ይሰነጠቃል” May 29, 2026 07:07 pm
  • ሪፖርተር፡ “ስውር ተልዕኮ” – በከባድ ወንጀል ሊከሰስ May 6, 2026 11:55 pm
  • የፋኖ ኃይል በደረሰበት ጉዳት ሃምሳ ሺህ የሚጠጋ ትጥቅ ጥሎ ጠፋ April 29, 2026 02:27 pm
  • አዲሱ የቴድሮስ ካሳሁን 888 ኮድ፤ እንደ 666?! April 15, 2026 05:53 am
  • ምኑ ነው ያሳቃችሁ፤ ያስደሰታችሁ? April 2, 2026 10:52 am
  • የጀዋር መሃመድ የፖለቲካ ማንነት እና የባዕዳን ተልዕኮ April 2, 2026 10:16 am
  • ከግብፅ በዳያስፖራ ትርምስ ጠማቂዎች በኩል ፋኖ ወደ አዲስ አበባ የላከው “ስጦታ” March 27, 2026 09:14 am
  • “ሰላማዊ ታጋዮቹ” እነ ልደቱ ከአራጁ ሸኔ ጋር ተጣምረዋል March 25, 2026 01:04 pm
  • ጸረ-ኢትዮጵያዊ የሆነው የሪፖርተር አዘጋገብ March 19, 2026 11:54 am
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ የኦሮሚያ የልማት ድርጅቶች March 18, 2026 10:48 am
  • የጃኖ ስጦታና የዶሮ ፖለቲካ በጎንደር March 10, 2026 09:24 am
Copyright © 2026 · Goolgule