
የህወሓትን ሆድ ዕቃ ቦርቡሮ የጨረሰው የውስጥ ትግሉ ነው። አሁን የመጣው ውዝግብ የሥልጣን ጥማት እንጂ ሌላ አለመሆኑንን ዶ/ር ጀማል መሀመድ ገምታ ተናገሩ። ልክ እንደ ሃጫሉ የሞት ማስፈራሪያ ደርሷቸው እንደነበርም ስም ጠቅሰው አስታወቁ። ኦህዴድን የከዱ አክቲቪስቶችን በመጋለብ ኦሮሚያ ላይ ቀውስ የሚፈጥረውን ጃዋርን ሆ ብሎ የሚከተለውን ሲያዩ እንደ ኦሮሞ ኃፍረት እንደሚሰማቸው አስታወቁ።
ባሌ ተወልደው፣ የህክምና ዲግሪያቸውን ካገኙ በኋላ ኦነግን ተቀላቅለው የነበሩት ሐኪም ጀማል ወደ ኦነግ በመሆናቸው ብቻ አስር ዓመታትን በእስር አሳልፈው ወደ ሎንዶን ተሰደዋል። በእስር ወቅት የደረሰባቸውን ስቃይ ለልጆቻቸውና ንጹህ ኅሊና ላላቸው ስለማይጠቅም ከመግለጽ እንደሚቆጠቡ አስታውቀው የተናገሩት ለኢሳት ነው። አሁን በኢትዮጵያም ሆነ በኦሮሚያ የተፈጠረው ችግር የሥልጣን ጥማት እንደሆነ ያብራሩት ዶክተሩ ዋና መነሻ ምክንያቱም ለውስጥ ትግል ዕውቅና ላለመስጠት መሆኑንን አመልክተዋል።
ዶ/ር ዐቢይ ገና ወደ ሥልጣን ሲመጡ “አማራ ለቃቅመህ አባረርህ” መባላቸውን ገልጸዋል። ለውጡን ፊት ሆኖ በብስለት፣ በመመካከርና በመተባበር ለድል ያበቁትን የኦህዴድና የብአዴን አመራሮችን ለመለየት የተፈለገውም ከሥልጣን ጥማት መነሻ ብቻ እንደሆነ በዝርዝር መረጃ እያጣቀሱ ገልጸዋል። እነሱ ባይተባበሩ ኖሮ ለውጡ እንደማይታሰብም አስረደተዋል።
ደጋግመው የኅሊና ጽዳት የጎደለው ሲሉ የሚወቅሱትን የወቅቱን ፖለቲካ “እንደ ህክምና ባለሙያ የተጋገነ ነገር አልወደም” በማለት ስለቄሮ ትግል እውነት ያሉትን አብራርተዋል። “ቄሮ በትግሉ ውስጥ ሚና እንዳለው ባይካድም፣ ዛሬ በቀለና ጃዋር ቄሮ የሚሉት ቀደም ሲል ለሞተው ቄሮ ክብር ሳይሆን ገና ወደፊት ስልጣን እስክንይዝ ድረስ ሙትልን ለማለት ነው” በማለት ድርጊቱን እንደ ኦሮሞ እንደሚጠየፉት አስታውቀዋል። በትግሉ ውስጥ የኦሮ-ማራ ኅብረት ታላቅ ዋጋ እንዳለውም ጠቅሰዋል። ያም ሆኖ ግን ከ85% (ሰማኒያ አምስት በመቶ) በላይ ትግሉ ያለቀው በብልኃት በውስጥ ትግል መሆኑን እንደሚያውቁ ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል። ለዚህ አኩሪ ተግባር ዕውቅና መስጠት እንደማይፈለግም ምሳሌና ምልክት እየሰጡ ጠቁመዋል።
ጃዋር መጠነኛ አስተዋጾ ቢኖረውም እግሩ አገር ቤት ከገባ በኋላ ሁሉንም የድሉን ዝና ጠቅልሎ ለመውሰድ ፈለገና ጩኸት ተጀመረ ያሉት የቀድሞ የኦነግ አባል “ሲንገበገብ ሁሉንም አጣው” ሲሉ ሃዘናቸውን ገልጸዋል። አስራ ሶስት ዓመት እስር ተፈርዶባቸው አስር ዓመት ከታሰሩ በኋላ የተፈቱት ዶ/ር ጀማል “ጥቂት ጯሂዎች አብዛኛውን እያስፈራሩ ነው” ሲሉ ስለታፈኑ ድምጾችም ተናግረዋል።
“ኦ.ኤም.ኤን. የጃዋርና የጫጩቶቹ ወይም የአሉላ ድምጽ ነው፤ ጥቂቶች አብዛኞችን የሚያስፈራሩበት መሣሪያ ነው” ካሉ በኋላ ሚዲያው ለኦሮሞ ሕዝብ የሠራው ነገር እንደሌለ ከአፈጣጠሩ ጀምሮ አስረድተዋል። በኦሮሞ ህዝብ መዋጮ፣ የኦሮሞ ህዝብ ላይ፣ ኦሮሞን የሚያፈርስ፣ የኦሮሞ መሪዎችን እያጣጣለ፣ ለወያኔ የሚሰራ ሚዲያ መሆኑንን አመልክተዋል። በዚሁ የጩኸት ሚዲያ ቀስቃሽነት “የጫት መቃሚያ፣ የጨብሲ የሚከፈላቸው” ቄሮ እየተባሉ ሌላውን እንዲያስፈራሩ ተደርጎ “መንግሥት” መሆናቸውን እስኪያውጁ መድረሳቸውንም አክለዋል። የዚህ ሁሉ ድራማ ባለቤት ጃዋር መሆኑንን በግልጽ አስቀመጠዋል። ንግግራቸው በመንግሥት ሚዲያ የአርሲ አባቶች ከተናገሩት ጋር የሚዛመድ ሆኗል።
በዲኤንኤ ኦሮሞም ሆነ አማራ የሆነ እንደሌለ እምነታቸውን ያሳዩት የህክምና ባለሙያ፣ በጃዋር ዙሪያ የተሰባሰቡት ኦህዴድ ለትምህርትና ለስራ ወደ ውጭ ልኳቸው የከዱ የኦህዴድ አባላትና በደርግ ዘመን ወንጀል የፈጸሙ ግፈኞች መሆናቸውን ጠቁመዋል። አያይዘውም ከዳተኞችና ወንጀለኞች ታዛዥ፣ የሚጋለቡ፣ ከኦሮሞ በላይ ኦሮሞ ልሁን የሚሉ የደረቀ ስብዕና የተላበሱ ሲሉ ስብስቡን የእምነት አጉዳዮች እንደሆነ ገልጸዋል። ከነዚህ ኃይሎች ውስጥ የወጣው አክቲቪዝም ኦሮሞ ደግ ነው በሚል ንግድ ውስጥ መግባቱንና ዛሬ የሚስተዋለው ሩጫና ሤራ ንግዱ ስለሚጣፍጥ ስልጣን ይዞ ለመዝረፍ እንጂ ለኦሮሞ ሕዝብ የተለየ ነገር ለማድረግ ታስቦ እንዳልሆነ አብራርተዋል።
ኦነግ አክራሪ እንዳልነበር ሲናገሩ ዲማ ነገዎ፣ ሌንጮ ለታና ገላሳ ዲልቦን አንስተዋል። እነሱን ገፍቶ ድርጅቱን የተቆጣጥረው የአንድ መንደር ወደ ነፍሰ ገዳይነት መቀየሩን አመልክተዋል። ሌላው ቀርቶ የተለየ ሃሳብ ያላቸውን ሳይመርጡ እንደሚያጠፉ አመልክተዋል። ሃጫሉ የተገደለው በመናገሩ መሆኑንን ያመለከቱት ዶ/ር ጀማል፣ እሳቸውም ማስፈራሪያ በስልካቸው እንደደረሳቸው አልሸሸጉም። ማስፈራሪያው ስልካቸው ላይ እንዳለ፣ ይህም የሆነው በመናገራቸው እንደሆነ ጠቁመው በርካታዎች መታፈናቸውን አስረደዋል። አቶ ሌንጮ ዛሬ ደንቢዶሎ የማይሄዱትም መንግሥት ከልክሏቸው ሳይሆን እነሱኑ ፈርተው መሆኑንን ገልጸዋል።
ሌንጮ ለታን በሃይማኖት፣ በአመላከትና በመንደር ዘመቻ አካሂደው እንደገፏቸው፣ ሌሎችም ላይ ተመሳሳይ ተግባር መፈጸሙን በማመልከት “ጃዋር ሲመጣ ግን አርሲ፣ ሙስሊም፣ …” ያልተባለው ብዙ የሚጮሁለት በማደራጀቱ፣ እነዚህ የሚጮሁ ጥቂቶች ደግሞ የሚከፈላቸው ስለሆኑ እንደሆነ ዶ/ሩ ያስረዳሉ። ከኢሳት ጋር ሰፊ ቃለ ምልልስ ያደረጉት ዶክተር ጀማል ኦነግ ዛሬ ስልጣን ቢይዝ ኦሮሚያን ገንጥሎ የሚመራበት ፕሮግራም፣ ድፍርትና ነባራዊ ሁኔታ እንደሌለ ሲገልጹ “ቱልቱላ ነው” በማለት ነው።
አስራ ሁለት ሺህ (12,000) የሚጠጉ የኦነግ ሰራዊት አባላት፣ እናቶች፣ ወጣቶችና ደጋፊዎች ሁርሶ ታስረው እንደነበር ያወሱት ሐኪም፣ እስረኞች በወደቀ ወታደር ብረት ቆብ (ሄልሜት) ገንፎ አገንፍተው ሲመገቡ ለኮሌራ መጋለጣቸውን አስታውሰዋል። እንደ ሃኪም ሰገራ በጃቸው በማጠብ እርዳታ ሲያደርጉ እንደነበር፣ ያም ሆኖ ግን ከ1,047 በላይ የሞቱ ወገኖችን መቁጠራቸውን ገልጸዋል። እስር ቤቱ የተደራጀ አመራር ስላልነበረው አንዳንዴ የሚመደቡ ተረኞች ህክምና እንዳይሰጡ ይከለክሏቸው እንደነበር አመልክተዋል። በቀላሉ ሊረዱ የሚችሉ ወገኖች አይናቸው እያየ በኮሌራ ማለቃቸው በእስር ዘመናቸው ልባቸው ከተነካበት ጉዳዮች መካከል የሚጠቀስ ነው።
ተቅማጥ ሲያዝቸው ለመጸዳዳት ወደ ውጭ ሲወጡ በርካታ የኦሮሞ ልጆችና ሰራዊት አባላት በቁማቸው በጅብ እንደተበሉ ዶ/ር ጀማል አጋልጠዋል። ይህንን ታሪክ ማንም እንደማያነሳውም አመልክተዋል። የሕክምና ባለሙያ በመሆናቸው በርካታ ለመናገር የማይፈቅዱትና ለአዕምሮ የማይመቹ ጉዳዮች በእስር ቆይታቸው ማሳለፋቸውን አንስተዋል።
“በ30 ዓመት ያየሁት መጥፎ ባህል ውጤታማ ከሆንክ ትጠላለህ። ከተዳፈርክና አሸንፈህ ከወጣህ ይነሱብሃል” በማለት አጠቃላይ ዛሬ ላይ ያለም ችግር ሲገልጹ እስር ቤት ወያኔዎች ሰው በመርፌ ገድሏል ብለው እንደወነጀሏቸው በማስታወስ ነው። ይህ ስሜት ካለመቻል፤ ከዕውቀት ማነስና ከቅናት የሚመነጭ መሆኑንን አመላክተዋል። በተለይም የኦሮሚያ ፖለቲካ የቅናት ውጤት እንደሆነ አጥበቀው ተናግረዋል።
ማንበብና መጻፍ የማይችሉ ተቧድነው በመንጋ አመላከከት አፈና እንደሚያካሂዱ፣ አፈናው አብዛኞችን አንቆ እንደያዘና ይህ የጥቂቶች ጩኸት የአክራሪነትና የተቆርቋሪነት ተደርጎ የሚወሰደው ፍጹም አግባብ እንዳልሆነ ዶክትሩ ሞግተዋል። ሲያስረዱም “አክራሪ አይዶሎጂ አለው። አይዶሎጂውን ይጠብቃል። ሌት ተቀን ላመነበት መርህ ይሰራል። ለፕሪንሲፕል ይሞታል” ካሉ በኋላ አሁን የሚታየው ግን ሌላ መሆኑንን፣ እሱም የፖለቲካ ቁማርና በጩኸት ሌሎችን አስፈራርቶ የማፈን አካሄድ እንደሆነ አስምረው አልፈዋል። “ውሸታሞች” ሲሉ ዘልፈዋቸዋል።
ምንም እንኳ ተመሳሳይ ድርጅት ውስጥ ቢኖሩም ሳይከዳ ባመነበት መንገድ ቆይቶ ወያኔንን ሰርስሮ ለጣለው ኦህዴድ ምስጋና እንደሚያሻው ያስታወቁት ዶክተር ጀማል፣ “… አፈጣጠሩ መጥፎ ቢሆንም ፣ ልጅ ሆኖ ገብቶ በጥበብ፣ በሂደት፣ ለውጥ አመጡ ጀግኖች ናቸው” ካሉ በኋላ አባል ሆነው በጦር ሜዳ ሳይቀር ያገለገሉትን ድርጅታቸውን “ኦነግ አፈጣጠሩ መልካም ነበር ቆይቶ ፌክ ሆነ፤ ገዳይ ሆነ” ገልጸውታል።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
ዶ/ር ጀማል ጠንቀቅ ሱሪ ጠበቅ ነው። የኦሮሞ ጽንፈኞች እውነትን የሚናገር ሰው አይወድም። እልፍ የኦሮሞ ልጆች ለኢትዮጵያ አንድነትና ነጻነት ተዋድቀዋል። የዛሬን አያድርገውና አብረን በልተን፤ ጠጥተን፤ ተጎራብተንና ተጋብተን ኑረናል። ግን እድሜ ለወያኔና ለሻቢያ በውጭ የአረብ ሃሎች እየተመሩ ከአውራ ጣት አመልካች እጣት ትበልጣለች በማለት ዘርና ቋንቋን ተገን አርገው በረጩት መርዝ ዛሬ ላይ ቆመናል። የወታደሩ ስብስብ ደርግ ለእነዚህ ሃይሎች መጎልበትና ብሎም ሻቢያ በአስመራ፤ ወያኔ በአዲስ አበባ አለቆች እንዲሆኑ መንገድን ጠራጊ ነበር። ጊዜ መሽቶ ሰው ረስቶት እንጂ የወታደሩ ስብስብ ገና በይፋ ንጉሱን ማታለሉን ሳይጀምር እውቁ ደራሲን ሃዲስ አለማየሁን ጠርቶ በእንዳልካቸው መኮነን ምትክ የሃገሪቱ ጠ/ሚ እንዲሆኑ ሲጠየቁ እንዲህ ብለው ነበር። ” እኔ የስነ ጽሁፍ እንጂ የአስተዳደርና የፓለቲካ ሰው አይደለሁም። የማልችለውን እንዳደርግ አትጠይቁኝ” ነበር ያሉት። ዛሬ ስልጣንና ወታደራዊ ማእረግ እንደ ሰንበቴ ቂጣ ታድሎአቸው ህዝባችን የሚያሰቃዪ ስንቶች ናቸው? ከአምቦ 30 ኪ.ሜትር ያህል ርቃ በምትገኝ የጅባትና ሜጫ ገጠር ቦዳ አቦ የተወለደው እውቁ ሎሬት ጸጋዬ ገ/መድህን እንዲህ ይለናል
አባይ የምድር አለም ሲሳይ
የቅድመ ጠቢባን አዋይ
አባይ የጥቁር ዘር ብስራት
የኢትዮጵያ ደም ኩሽ እናት
የዓለም ስልጣኔ ምስማክ (እሳት ወይ አበባ 1966 ዓ.ም) ገና ብዙ በሚቀረው ግድብ ዙሪያ አሁን ሰው በአባይ ግድብ ዙሪያ ተሳካ በተባለው ሲፈነድቅ ይህ ግጥም ትዝ ይለኛል።
እኮ ይህ ሰው ዛሬ በህይወት ቢኖር ምን ይለን ነበር? በኢትዮጵያዊነቱና በኦሮሞነቱ ኮርቶ ሁሉን አቅፎ፤ ለሃገር ሰርቶ ያለፈ ይህ ጀግና ከመቃብር ድምጽን ብንሰማ ምን ይል ይሆን? በሃገራችን አሁንም ሆነ ከበፊት የተነሱ የዘርና የጎሳ ፓለቲከኞች አሻሮዎች ናቸው። ቆመንለታል በሚሉት ህዝብ ላይ የፈጸሙት በደል ስታሊን በሩሲያ ህዝብ ላይ ከፈጸመው በደል ይወዳደራል። ግን እንደ እድል ሆኖ ግፍን የማጋለጥና ቋሚ እንዲያውቀው የማድረግ ባህል የለንም። በፓለቲካ ሚስጢር ታፍነን ወደ መቃብር ይዘነው እንወርዳለን። በበረሃ እያለ ስብዕና የሌለው የፓለቲካ ቡድን ከተማ ሲገባ ሰው ይሆናል ብሎ ማመን ተንጋሎ መትፋት ነው። እንዲያውም ይብስባቸዋል እንጂ። የወያኔው አፈ ቀላጤ በአዲስ አበባ (ስልጣን ላይ ወያኔ እያለ) የዜና አውታሮችን ጠርቶ መግለጫ ሲሰጥ እንዲህ ብሎ ነበር “አማራና ኦሮሞ አንድ ሆኑ ማለት እኛ የቤት ስራችን አልሰራንም ማለት ነው” ይህ የሚነግረን ወያኔ በሰው ደም የሚነግድ የማፊያ ድርጀት እንደሆነ ነው። ኦነግ ራሱ ባስታጠቃቸው ሃይሎች ወያኔ ቆሞ በለው እያለ በአርባ ጉጉና በበደኖ የሆነውን እማኝ ማረግ ለጭካኔአቸው ሸረፍታዊ ምስክር ነው። ኦነጎች እድሜ ልካቸውን ለኦሮሞ ህዝብ እየታገልን ነው ይበሉ እንጂ የኖሩት ለራሳቸው ነው። ጃዋር ኦነግን ወደ ጎን አርጎ ከኦፌኮ ጋር የገጠመበት ምስጢሩ አሁን ለአቶ ሌንጮ እና ለገጀራ አብዪት አራማጅ ኦሮሞዎች ግልጽ እየሆነ የመጣ ይመስለኛል። ሰዎቹ ለኦሮሞ ህዝብ ሳይሆን ለራሳቸው የስልጣን ጥማት የቆሙ መሆናቸውን ነው።
በማሳረጊያው ዶ/ር ጀማል ከህይወት ልምዳቸው፤ ከአዩትና ከሰሙት፤ ካነበቡትና ከኖሩበት በመነሳት በኦነግ ዙሪያም ሆነ በኢትዮጵያ ላይ ያላቸውን እውነተኛ የሆነ እይታ ከመረጃ ጋር ለህዝባችን በመጽሃፍ መልክ ቢያካፍሉት ለትውልድ ጠቃሚ ነው። በአንድ ቪድዮ ላይ እንዳየሁትም በአማርኛው የተካኑና ጎንደር ዪንቭርስቲም የተማሩ በመሆናቸው ቋንቋው ቋንቋቸው ነውና ይጻፉበት። አይ በኦሮምኛ እጽፋለሁ ካሉም ተርጓሚ አናጣም። ብቻ መጽሃፉ ይጻፍ። ትውልድ እውነቱን ይወቅ! በቃኝ!