• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

“ሄዶ ኢትዬጵያ (hej då Ethiopia)”

April 29, 2016 03:10 pm by Editor 1 Comment

በቅርቡ በዚህ በምኖርበት አገር አንድ የልደት በአል ላይ ተጠርሼ ሄጄ ነበር፡፡ በዚሁ ዝግጅት ላይ ከዝህ በፊት በአካል አግኝቼው የማላውቀው የዚሁ አካባቢ ከበርቴ ጋር ስጨዋወት ነበር፡፡ በተለይ ከአመታት በፊት በኢትዬጵያ ታስርው ስለነበሩት የስዊድን ጋዜጠኞች ልቤ እስኪጠፋ ጠየቀኝ፡፡ እኔም የምችለውን ያህል ለመመለስ ሞከርኩ፡፡  ስንሰነባብት ያለኝ ነገር ግን ሰሞኑን በኢትዬጵያ ዙሪያ የሚሰማኝን ውጥንቅጥ ስሜት ቅልብጭ አድርጎ ገለጠልኝ። ምን አለኝ መሰላችሁ… “ሄዶ ኢትዬጵያ”። አለፍ ብሎም ስሜን በወጉ መጥራት እንደከበደው ነገረኝ። በዚህ በስዊድን አፍ “ሄዶ (hej då)” ማለት ቻው ወይንም ደህና ሁን/ሁኚ እንደማለት ነው። ከዚሁ ቤት እየወጣሁ ቃሉን በውስጤ ደጋገምኩት… ሄዶ ኢትዬጵያ … ቻው ኢትዬጵያ … በተመስጦ አሰብኩት። አዎ ልክ ነው። አሁን ሰለ ሃገሬ የሚሰማኝ ስሜት ይሄ ነው። ቻው ኢትዬጵያዬ የሚል አይነት ስሜት። ለማስረዳት ልሞክር።

ሰሞኑን በጋምቤላ ወገኖቼ ላይ የተከሰተው አሰቃቂ ክስተት ለእኔ ከመቼውም ጊዜ በላይ የገለጠልኝ ሁለት ቁም ነገሮች አሉ።

አንድ።

እኛ ኢትዬጵያውያን መከላኪያ ሰራዊት ሳይሆን ማፈሪያ ሰራዊት ነው ያለን። በእጅጉ የሚያሳፍር እና የሚያሸማቅቅ። የማንኛውም አገር መከላኪያ ሰራዊት ተቀዳሚ ተግባሩ እንዲሁም የሰራዊቱ መኖር ዋንኛ ምክንያት የአገሩን ሉአላዊነት ማስከበር መሆኑ ግልብ ነው። ከዚህም በላይ አንድን አገር እንደ አገር (solid state) ከሚያስቆጥሩ ቁልፍ እና ወሳኝ ነገሮች አንዱ ሉአላዊነት እንደሆነ ነው የሚገባኝ። ወደ እኛው ጉድ ስንመጣ ግን  ማፈሪያው ሰራዊታችን ተግባሩ እና አላማው ለየቅል ነው። እስከአሁን እንዳየነው ማፈሪያው ሰራዊታችን ለሰላማዊ ተቃውሞ የሚወጡ ኢትዬጵያውያን፣ ህጻናት እና እናቶች ሳይቀር መግደል ተቀዳሚ ተግባሩ ከሆነ ቆየት ብሎአል። በሙስና እስከ አፍንጫቸው ከተጨማለቁ የመንግስት ተቐሞች አንዱ መከላኪያ ነው። ለእኔ ይኼ ማፈሪያ የሆነ ሰራዊት ንጹሀን ኢትዬጵያውያንን መግደል እና የአገሪቱን ሀብት መዝረፍ የእለት ከእለት ተግባሩ እንደሆነ ነው የሚሰማኝ።

እሺ ሌብነቱስ ይሁን። ከከርስ ባለፈ ማሰብ በማይችሉ የግለሰቦች ስብስብ ከተሞላ መስሪያ ቤት የሚጠበቅ ነው። (በነገራችን ላይ ስለ መከላከያ ሌብነት በማስረጃ ማሳየት እችላለሁ። በግሌም ያየሁት ስለሆነ)። ንጹሀን ኢትዬጵያውያንን በተደጋጋሚ መግደሉ ለአገር ሳይሆን የሕወሀት አሽከር መሆኑን መግለጫ ነው ብለን እንውሰደው። ነገር ግን የታጠቀ የውጭ ሐይል (ያውም ከደቡብ ሱዳን) ስንት እና ስንት ኪሎ ሜትር የኢትዬጵያን ዳር ድንበር በመድፈር ሰሞኑን የሰማነወን አሰቃቂ ጭፍጨፋ በኢትዬጵያውያን ላይ መድረሱ እኛ ኢትዬጵያውያን መከላከያ ሰራዊት እንደሌለን አስረግጦ የሚያሳይ ይመስለኛል። በዚህ መልኩ የኢትዬጵያ ሉአላዊነት መደፈሩ የሚያመላክተው የኢትዬጵያን መለዮ የለበሰው እና የኢትዬጵያን የጦር መሳሪያ የታጠቀው የግለሰቦች ስብስብ (ወታደር ለማለት ስለከበደኝ ነው) መከላከያ ሳይሆን በእርግጥም ማፈሪያ ነው! ይኼን አገራዊ ውርደት ተሸክመን ሌላ አገር ሄዶ ሰላም ማስከበር፤ በእሳት እየተቃጠሉ እሳት የመሞቅ ያህል ቂላቅልነት ነው። ድንቄም አሉ!

ሁለት።

እኛ ኢትዬጵያውያን መንግስት ሳይሆን ማፍያ ነው አገራችንን የሚመራት። ለይስሙላ የሚታይ የመንግስት መዋቅር ቢኖርም፣ ፓርላማውን ጨምሮ። አገሪቱን በትከክክል የሚመራው እና የሚያስተዳድረው የግለሰቦች ስብስብ ነው። ስሙ ሕወሀት ሲሆን ተግባሩ ደግሞ የማፊያ ነው። ይኸ የይስሙላ የመንግስት መዋቅር ከስም ውጪ ሌላ እርባና የለውም። በውስጡ የተሰገሰጉት ግለሰቦች ባዶ ቀፎ ናቸው። (በዚሁ በጎልጉል ጋዜጣ ላይ ከጥቂት ጊዜ በፊት “ቀፎ አይሁኑ” በሚል ሃሳቤን ለማካፈል ሞክሬአለሁ)  ። ይኸ መዋቅር የሕወሀት ፈረስ ማለት ነው። ለዚህም ይመስለኛል ” አባ ዱላ የመለስ ጥሩ ፈረስ” እየተባለ የሚቀለደው … የሚቀለደው ልበል፤ ወይስ የሚታማው፤ ወይስ የሚታወቀው እንዲያውም እንደሚታወቀው ብንለው ይቻላል። ግልጽ ስለሆነ። የበፊት ነገስቶቻችን ከፈረሶቻቸው ስም በፊት “አባ” የሚለውን ተቀጽላ በማስታወስ። ለነገሩ ፈረስ እኮ ጥሩ እንሰሳ ነው። ታዛዥ እንሰሳ። ስለ ፈረስ ካነሳሁ አይቅር … አንድ ነገር ልበል።(የፈለገ ቢሆን አንድ ኢትዬጵያዊ ያልተማረ ፈረስ እንግሊዘኛ ሊናገር አይችልም! ግብጽ ድረስ ዲፕሎማት አድርጋችሁ ብትልኩትም። በዚህ በቅንፍ ውስጥ ያለው ለሚገባው ይገባዋል።) ወደ ጉዳዬ ልመለስ። ይኸ ራሱን ሕወሀት እያለ የሚጠራው የማፊያ ቡድን በዚህ ከላይ በጠቀስኩት ፈረስ ላይ ተቆናጦ ይኸው ለ ሃያ አምስት አመታት እየጋለበን ይገኛል። እንግዲህ ማፊያው እንደማፊያ እየዘረፈ፤ እየዋሸ እና እየገደለ እዚህ ላይ ደርሰናል። ቅጥፈቱ ከመቅረናቱ የተነሳ የሚታየው ረሃብ እና የኢትዬጵያውያን ሰቆቃ በታሪካችን ታይቶ የማይታወቅ መርገም ነው።

ላጠቃለው፤ ስጀምር በመግቢያ ላይ ቻው ኢትዬጵያ በሚለው እደምታዬ ነበር።  አዎ የታለች ያአቺ የምናውቅት አገር? ሉአላዊ ኢትዬጵያ ወዴት ነው ያለችው አሁን?  ለመጀመሪያ ጊዜ የጥቁር ሕዝብ ድል አድራጊነት ለአለም ያሳየች ኢትዬጵያ የት ናት አሁን? ከነጻነት ተምሳሌትነት ተንደርድረን ወርደን ይኼው ዛሬ ኢትዬጵያውያን በበርሃ እየታረዱ ነው፤ በአደባባይ በተሰደዱበት በእሳት እየተቃጠሉ ነው፤ በርሃብ እየታረዙ ነው፤ በሜዲትራኒያን ባህር እየተዋጡ ነው፤ ጭራሽ ብለን ብለን ኢትዬጵያ ውስጥ ተጠልለው በሚገኙ የሌላ አገር ስደተኞች፤ ኢትዬጵያውያን እንደሚታደነ የዱር እንሰሳ በየጫካው ለመግለጽ በሚያስቸግር መልኩ እየተገደሉ ነው። ታዲያ እንዲያው ድፍረት አይሁንብኝና ጥያቄ ልጠይቅ። ሁሉንም ኢትዬጵያዊ። እንደዚህ ናት እንዴ የእኛ ኢትዬጵያ? እንዴት ነው ነገሩ? ወዴት እየሄድን ነው? እንጃ?! እኔ ግን አንድ ነገር በእርግጠኝነት ልንገራችሁ። ይኸን ማፊያ መንግስት እና ማፈሪያ መከላከያ ሠራዊት ቆመን የምናይ ከሆነ፤ እውነት እውነት ኢትዬጵያን ቻው እያልናት ነው። ማፍያስ ያው ማፍያ ነው፤ ቀፎም ያው ቀፎ ነው፤ ፈረስም ያው ፈረስ ነው። እኛ ግን ምን ሆነን ነው ቆመን የምናየው?

በዚህ አጋጣአሚ በጋምቤላ ለሚገኙ እናቶቼ፤ አባቶቼ፤ እህት እና ወንድሞቼ ፈጣሪ ጽናቱን እና ብርታቱን ይስጣችሁ።

ፈጣሪ አገራችንን ይባርክ።

ወንድምአገኝ እጅጉ
ከስቶኮልም፥ ስዊድን


“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡

Print Friendly, PDF & Email

60

SHARES
Share on Facebook
Tweet
Follow us
Share
Share
Share
Share
Share

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Comments

  1. ተስፋዬ አበራ says

    May 14, 2016 07:03 pm at 7:03 pm

    ወንድሜ ወንድም አገኝ የፃፍከውን አስተያየት አንብቤዋለሁ ሀሳብህን ሙሉ በሙሉ የምጋራው ሲሆን ” ኢትዬፕያን ቻው እያልናት ነው” የሚለውን ቃል ግን አልወደድኩትም ከእኛ ይልቅ እነዚህን ጉዶች ከሀገራችን እንዴት እንደምናስወግድና እነርሱኑ በሰሩት ግፍ እና ሀጥያት ለፍርድ አቁመን ቅጣታቸውን ሲጨርሱ እነርሱንም ሆነ ስርአቱን በተግባር ቻው ቻው ማለት የለብኝ ይመስለኛል።
    ታዲያ በወሬ ሳይሆን በተግባር ሁላችንም በምንችለው መንገድ መንቀሳቀስ ይጠበቅብናል ሰዎቹ በህዝባችን እና ሀገራችን ላይ እየተፀዳዱብን ይገኛሉ ንቀውናል አዋርደውናል ጭራሽ የጋራ ሀብታችንን እየዘረፉ በውጭ ሀገራት ባንኮች ውስጥ ገንዘብ እንደሚያስቀምጡ ይታወቃል ስለሆነም ለተግባራዊ ትግል እንነሳ !

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • “የገቡበት ገብተን አንድ ሰው አናስቀርም – በተለይ አመራሩን” ጄኔራል ብርሃኑ ጁላ February 15, 2021 11:46 pm
  • የትግራይ ገበሬና የከተማ ነዋሪ በሠራዊታችን ላይ አንድ ጥይት አልተኮሰም – ሪር አድሚራል ክንዱ February 4, 2021 01:51 pm
  • ኢንተርፖል፤ የህወሃት ሳምሪዎች የማይካድራ ጭፍጭፋ ከቦኮሃራም የከፋ ነው February 4, 2021 11:10 am
  • ጄኔራሎች “ተገድለዋል” በሚል የሀሰት መረጃ ሲያሰራጭ የነበረው ግለሰብ በቁጥጥር ስር ዋለ February 4, 2021 08:48 am
  • በትግራይ ክልል በሴቶች ላይ ተፈጸመ የተባለውን ጥቃት የሚያጣራ ግብረ ኃይል መቀሌ ገባ February 3, 2021 12:06 pm
  • ፓርቲዎች የምርጫ መወዳደሪያ ምልክቶቻቸውን ወሰዱ February 3, 2021 10:29 am
  • በአዲስ አበባ የተወረረው መሬት፣ ባለቤት አልባ ቤቶችና ሕንጻዎች ይፋ ሆኑ January 26, 2021 11:16 am
  • የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አክቲቪስቶችን በሕግ ተጠያቂ አደርጋለሁ አለ January 26, 2021 10:32 am
  • የሰባት ቤት አገው የፈረሰኞች ማኅበር 81ኛ የምስረታ በዓል January 26, 2021 07:17 am
  • በጋምቤላ ህወሃትንና ኦነግ ሸኔን ትረዳላችሁ ተብለው የታሰሩ እንዲፈቱ ተጠየቀ January 25, 2021 03:07 pm
  • “…ሰብዓዊ እርዳታ እየቀረበ አይደለም የሚሉ አካላት የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት ነው” – ዶ/ር ሙሉ ነጋ January 25, 2021 01:02 pm
  • የሶማሌና ኦሮሚያ መሥተዳድሮች ወሰንን በተመለከተ የሰላምና የጋራ ልማት ስምምነት አደረጉ January 25, 2021 12:50 pm
  • 125ተኛውን የአድዋ ድል በዓል በድምቀት ሊከበር ነው January 25, 2021 09:34 am
  • በመቀሌ ከ350 ሚሊዮን ብር በላይ የህክምና ግብዓቶች ክምችት መኖሩ ታወቀ January 25, 2021 02:47 am
  • ዊንጉ አፍሪካ (wingu.africa) በዓይነቱ የመጀመሪያ የሆነ የመረጃ ማዕከል ሊገነባ ነው January 24, 2021 01:23 pm
  • ኢትዮጵያ ድሮኖችን ማምረት ልትጀምር ነው January 24, 2021 02:40 am
  • የአየለ ጫሚሶ ቅንጅት ፈረሰ January 18, 2021 02:31 pm
  • ህወሓት ተሠረዘ!!! January 18, 2021 01:32 pm
  • ዓሲምባ፣ ሣልሳዊ ወያኔና ባይቶና ከመፍረሳቸው በፊት ማብራሪያ እንዲሰጡ ተነገራቸው January 18, 2021 01:00 pm
  • ቤተሰቦች አስከሬን መውሰድ እንደሚችሉ ተነገረ January 14, 2021 06:48 pm
  • ስብሃት፤ “ከሞትን ቆይተናል፤ … አሁን የቀብር ሥነ-ስርዓታችን” እየተፈጸመ ነው January 14, 2021 01:37 pm
  • “ተመልሰን እንነሳለን” ያሉት ህወሓቶች ተመልሰው ወደማይነሱበት ተሸኙ January 13, 2021 01:12 pm
  • አፋር ነፃ አውጪ (ኡጉጉሙን) ለመጠቀም የታቀደው የህወሃት ሤራ ከሽፏል January 13, 2021 01:10 pm
  • ህወሃትን ወደ ጅቡቲ ለማሻገር ሲሰሩ የነበሩ የአፋር ታጣቂዎች በሰላም ወደ ክልሉ ገቡ January 13, 2021 06:47 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2021 · Goolgule