• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

በግብረሰዶም ተጠርጣሪዎች ላይ የሳይኮሎጂና የሳይካትሪ ባለሙያ የምስክርነት ቃል ሰጡ

August 5, 2013 09:26 am by Editor 1 Comment

ሁለት የ10 እና የ11 ዓመት ዕድሜ ያላቸው የአራተኛና የአምስተኛ ክፍል ተማሪዎች ላይ የግብረሰዶም ጥቃት ፈጽመዋል በሚል ተጠርጥረው በእስር ላይ በሚገኙት የካራክተር ሆልማርክ አካዳሚ ስድስት መምህራን ክስ ላይ፣ ከዓቃቤ ሕግ ምስክሮች በተጨማሪ አንዲት የሳይኮሎጂና የሳይካትሪ ባለሙያ ሐምሌ 25 ቀን 2005 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ቀርበው የሙያ የምስክርነት ቃላቸውን ሰጡ፡፡

የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ በተጠርጣሪዎቹ ላይ የመሠረተውን የወንጀል ክስ በማየት ላይ ያለው የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ሰባተኛ የወንጀል ችሎት፣ ስማቸው በሚዲያ እንዳይገለጽ የከለከለላቸው የሳይኮሎጂስትና የሳይካትሪ ባለሙያዋ፣ በተጠርጣሪ መምህራን የግብረሰዶም ጥቃት ደርሶባቸዋል የተባሉትን ሁለት ወንድ ሕፃናት፣ ለሦስት ጊዜያት አግኝተው እንዳነጋገሯቸው ገልጸዋል፡፡

ተጠርጣሪዎቹንም ሆኑ የጥቃቱ ሰለባ ናቸው የተባሉት ሕፃናትን እንደማያውቋቸው የገለጹት ባለሙያዋ፣ ሕፃናቱን ከአራት ወራት በፊት ቃለ መጠይቅ እንዲያደርጉ ታዘው ማድረጋቸውን ተናግረዋል፡፡

ባለሙያዋ ከሕፃናቱ ጋር ቃለ መጠይቁን ያደረጉት፣ በጠቅላይ ፍርድ ቤትና በፖሊስ ጣቢያ መሆኑን ጠቁመው፣ መጀመሪያ ከእናቶቻቸው ጋር ቀጥለው ደግሞ ሕፃናቱን ለብቻቸው ማነጋገራቸውን ገልጸዋል፡፡

ሕፃናቱን መጀመሪያ ከወላጆቻቸው ጋር ያነጋገሯቸው ስለማያውቋቸው ለመለማመድ መሆኑንና ቀጥለው ለብቻቸው ቤተሰቦቻቸውን ሳይፈሩ እንዲያነጋግሯቸው ማድረጋቸውን የገለጹት ባለሙያዋ፣ በምክር ወይም ድርጊቱን በማስጠናት የተሳሳተ ማስረጃ እንዳይሰጧቸው፣ ቃለ መጠይቁን ያደረጉላቸው እያጫወቱና ዘና እንዲሉ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ጠዋት ቁርሳቸውን ከበሉበት እስከ ማታ ከትምህርት ቤት ተመልሰው ወደ ቤታቸው እስከሚገቡበት ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ ያደረጉትን አንድ በአንድ እንዲያስረዷቸው በመጠየቅ መሆኑንም አብራርተዋል፡፡ ባለሙያዋ የሚፈልጉትን በጨዋታ ዓይነት ተጎጂ የተባሉት ሕፃናት ምንም ሳይፈሩ የጠየቋቸውን ሁሉ በአግባቡ እንደመለሱላቸው አክለዋል፡፡

በተለያዩ ጊዜያትም ያንኑ ጥያቄ ሲጠይቋቸው በተመሳሳይ ሁኔታ ማስረዳታቸውንም አስታውሰዋል፡፡ ሕፃናቱ እንዴት ቀናቱን ሊያስታውሱ እንደሚችሉ ተጠይቀው ባለሙያዋ ሲመልሱ፣ ሕፃናቱ ቀኑን በትክክል ባያስታውሱም ድርጊቱ ተፈጸመ በተባለበት ጊዜ በዓል ካለ ወይም በዚያን ጊዜ የማይረሳ ነገር ካለ እሱን በማስታወስ እንዲያስታውሱት ማድረግ እንደሚቻል ገልጸዋል፡፡ ከተጠቂዎቹ አንዱ ቀኑን በደንብ አስታውሶ እንደነገራቸው የገለጹት ባለሙያዋ፣ ድርጊቱን ፈጽመዋል ያሏቸውን ሰዎች ስምና ድርጊት እንዳስረዷቸው ተናግረዋል፡፡

ድርጊቱ የተፈጸመባቸው ሕፃናት ከድርጊቱ በኋላ የሚያሳዩት ባህሪ ካለና የጉዳዩ ባለቤት በሆኑት ሕፃናት ላይ ያዩት የባህሪ ለውጥ ወይም ምልክት ካለ እንዲያስረዱ ተጠይቀው፣ ድርጊቱ የተፈጸመባቸው ሕፃናት አራት ባህሪያትን ያሳያሉ፡፡ ፈሪ፣ ኃይለኛ (ተደባዳቢ)፣ ብቸኛ መሆንን መፈለግና ከፍተኛ የሆነ የወሲብ ፍላጎት የማሳየት ባህሪያት እንደሚያመጡ አስረድተዋል፡፡ ሌላው በትምህርት ላይ የሚያሳዩት ሁኔታ ሲሆን፣ በአንድ ትምህርት ላይ ብቻ ጎበዝ የመሆንና ሌላውን የመጥላት ወይም ፍላጎት ያለማሳየትና ደብተራቸውን ጥሎ የመምጣት ባህሪም እንደሚያመጡ ባለሙያዋ ገልጸዋል፡፡

ተጠቂ ከተባሉት ሁለቱ ሕፃናት አንደኛው የወሲብ ፍላጎት እንዳለውና እሱም እንዳረጋገጠላቸው የገለጹት ባለሙያዋ፣ ይኼ ስሜት ሲመጣበት ከማን ጋር ለማድረግ እንደሚፈልግ ጠይቀውት፣ ከወጣት ወንዶችና እንደ አስተማሪዎች ካሉ ወንዶች ጋር ማድረግ እንደሚፈልግ፣ ወንድ ሕፃናትና ትልቅ ሰው እንደማይፈልግ እንዳስረዳቸው ገልጸዋል፡፡ ይኼንንም ጥያቄ ያቀረቡለት በጥናት ሕፃናት የሚጠቁት በአብዛኛው በሚያውቁትና በቤተሰብ፣ ወይም ዘመድ መሆኑን ስለተረጋገጠ በቤታቸው ውስጥ ወንድሞችና አባት ስለሚኖሩ ከነሱ ጋር ያለውን ሁኔታ ለማወቅ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

ሕፃናት ድርጊቱ እንደተፈጸመባቸው ወዲያውኑ የቤተሰብ እንክብካቤ፣ አማካሪ ዘንድ በመውሰድ የምክር አገልግሎት እንዲያገኙ በማድረግ፣ ድርጊቱ እንዳልተፈጸመ ሆኖ እንዲሰማቸው ወይም ጥፋቱ የእነሱ እንዳልሆነ እንዲያስቡ ስለሚያደርጋቸው በቀጣይ ከሚደርስባቸው ተፅዕኖ ማዳን እንደሚቻልም ባለሙያዋ አብራርተዋል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን እያደጉ ሲሄዱ እነሱም ወደ ተመሳሳይ ተግባር እንደሚያመሩ፣ ኃይለኞች እንደሚሆኑ፣ ከቤት ወጥተው ተስፋ በመቁረጥ ወደማይሆን ነገር ውስጥ ሊገቡ እንደሚችሉም አክለዋል፡፡

መምህራኑ የተጠረጠሩባቸው ሁለቱም ሕፃናት ‹‹ትምህርት አስጠልቶኛል፤ ባልሄድ ደስ ይለኛል፤›› እንዳሏቸው ባለሙያዋ ጠቁመው፣ በጥናትም የተረጋገጠው ሕፃናት ድርጊቱ ከተፈጸመባቸው በኋላ ብቸኝነትን እንደሚመርጡ፣ ፈሪና ኃይለኛ እንደሚሆኑ መረጋገጡንና በእነሱም ላይ ምልክቱ ተግባራዊ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

የተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች አንደኛው ተጠቂ ብዙ ትምህርት ቤቶችን እንደቀያየረና በሄደባቸው ትምህርት ቤቶች ጥቃቱ እንደደረሰበት በመጥቀስ፣ የድርጊቱን ፈጻሚዎች እንዴት ሊያውቁት እንደሚችሉ ጠይቀውት ከሆነ ባለሙያዋ እንዲያስረዱ ሲጠይቋቸው፣ በተለይ አንደኛው ተጠቂ ከፍተኛ የወሲብ ስሜት ስላለው፣ ተጠግቶ ስለግብረሰዶም እንደሚያወራቸው ነግሯቸዋል፡፡ ስሜታቸው ከፍተኛ ስለሚሆን ተጠቂዎች አንገት ሥር የመሳም፣ የመነካካት፣ በብልት አካባቢ መመልከትና መቀመጥ እንደሚያዘወትሩ ባለሙያዋ አክለው፣ በአንደኛው ሕፃን ላይም ይህንን ምልክት ማየታቸውን አስረድተዋል፡፡

ድርጊቱ በቤተሰብ ቢፈጸም በሌላ ሰው የማሳበብ ሁኔታ ሊፈጠር የሚችልበትን አጋጣሚ በሚመለከት ለባለሙያዋ ጥያቄ ቀርቦ፣ ‹‹እውነት ነው፣ አድራጊውን በመፍራት በሌላ ሰው ላይ ያሳብባሉ፤›› ካሉ በኋላ፣ በሁለቱ ሕፃናት ቤተሰብ ዙሪያ ስላለው ሁኔታ ሲጠየቁ፣ ድርጊቱ የተፈጸመው በትምህርት ቤት ውስጥ መሆኑን ብቻ መናገራቸውን አውስተዋል፡፡

ስድስት መምህራን በአንድ ሕፃን ላይ ተፈራርቀው ድርጊቱን ከፈጸሙ በኋላ ልጁ ያለምንም ጉዳት ወደ ጨዋታ የሚሄድበት ሁኔታ ካለ እንዲያስረዱ ባለሙያዋ ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፣ አንዳንድ ጊዜ ሊገጥም እንደሚችል፣ ግን የልጁ ሁኔታ እንደሚወስን ካስረዱ በኋላ፣ ይኼ የአካል ጉዳትን የሚመለከት በመሆኑና እሳቸውም በዚህ ዙሪያ ማብራራት እንደማይችሉ ተናግረው፣ የሕክምና ባለሙያ ማብራሪያ ሊሰጥበት እንደሚችል አስገንዝበዋል፡፡ የጥቃቱ ሰለባ የሆኑ ሕፃናት ተፅዕኖው አብሯቸው አድጎ ትዳር በሚመሠርቱበት ጊዜ ከፍተኛ ችግር እንደሚያስከትልባቸው ገጠመኛቸውን በማስረዳት አደገኛነቱን ተናግረዋል፡፡

ሕፃናቱ የግብረሰዶም ጥቃቱ ከተፈጸመባቸው በኋላ በጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታልና ጋንዲ መታሰቢያ ሆስፒታል ምርመራ በማድረጋቸው፣ ፍርድ ቤቱ የምርመራ ውጤቱን ተከትሎ በሰጡት ማስረጃ ላይ ማብራሪያ እንዲሰጡ ሆስፒታሎቹ መታዘዛቸው ይታወሳል፡፡ በትዕዛዙ መሠረት ጋንዲ መታሰቢያ ሆስፒታል ‹‹ባለሙያ የለኝም›› ብሎ ምላሽ ሲሰጥ፣ ጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ግን ባለሙያ ሳይልክ በመቅረቱ፣ በቀጣይ ቀጠሮ እንዲልክ ፍርድ ቤቱ ጥብቅ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

በሌላ በኩል የሪፖርተር ጋዜጣ ዘጋቢ ሐምሌ 17 ቀን 2005 ዓ.ም. የአካዳሚው መምህራን የተጠረጠሩበትን የግብረሰዶም ጥቃት ወንጀል አስመልክቶ ለመዘገብ በፍርድ ቤቱ የተገኘ ቢሆንም፣ ፍርድ ቤቱ ጉዳዩ የሚታየው በዝግ ችሎት መሆኑን ገልጾ እንዲወጣ በማዘዙ ችሎቱን ሊከታተል አልቻለም፡፡

ዘጋቢው በፍርድ ቤት ግቢ ውስጥ በመዋል መረጃውን ከችሎቱ ታዳሚዎች በማግኘት ውሎውን በተመለከተ ‹‹ጋዜጠኞች ችሎት እንዳይገቡ ተከለከሉ›› በማለት መዘገቡ ይታወሳል፡፡ ነገር ግን ፍርድ ቤቱ ችሎቱ ዝግ የሆነው በሌሎች መዝገቦች እንጂ በግብረሰዶም ጥቃት ወንጀል የተጠረጠሩትን እንደማያካትት አስታውቆ፣ ችሎቱ በግልጽ መካሄዱን በመግለጽ ማስተካከያ እንዲያደርግ አዟል፡፡ ፍርድ ቤቱ እንደገለጸው፣ ሐምሌ 15 ቀን 2005 ዓ.ም. ችሎቱ ዝግ እንዲሆን የተደረገው በሕገ መንግሥቱ ተደንግጎ እንደሚገኘው አንዳንድ ክሶች (ጉዳዮች) በዝግ ችሎት መታየት ስላለባቸው፣ የሪፖርተር ዘጋቢ ከችሎት እንዲወጣ የተደረገው በዝግ ችሎት መታየት ለሚገባቸው ጉዳዮች እንጂ፣ በግብረሰዶም ወንጀል ተጠርጥረው ለተከሰሱት ባለመሆኑ፣ ዘገባው ስህተት እንዳለበትና ይኼው እንዲገለጽ በድጋሚ አዟል፡፡

የሪፖርተር ዘጋቢ በዕለቱ ለብይን ተቀጥሮ የነበረውን የግብረሰዶም ጥቃት ወንጀል ተጠርጣሪዎችን ጉዳይ ለመከታተል በሰዓቱ ችሎቱን ታድሟል፡፡ ችሎቱ በዝግ እንደሚታይ በመግለጽ ታዳሚዎች እንዲወጡ ዳኛዋ ሲያዙ ዘጋቢው ወደኋላ በመቅረት ለፍርድ ቤቱ ጋዜጠኛ መሆኑን በመግለጽ መታደም እንዲችል ሲጠይቅ አልተፈቀደለትም፡፡ ውጭ ቆይቶ በተደጋጋሚ ለመግባት ሲሞክር የችሎት ፖሊሶች ‹‹ዝግ ነው›› በማለት ሊያስገቡት ሳይችል ቀርቷል፡፡ ችሎቱ እስከሚያበቃ እዚያው ቆይቶ ከችሎቱ ታዳሚዎች ባገኘው መረጃ መሠረት ሲዘግብ፣ ችሎቱ ጉዳዩን በዝግ ማየቱን በዘገባው አካቷል፡፡ ዘጋቢው የዕለቱን ችሎት በአግባቡ እንደዘገበ ቢታወቅም፣ ፍርድ ቤቱ መስተካከል እንዳለበት በማዘዙ በድጋሚ ለመዘገብ ተገደናል፡፡

ሌላው ፍርድ ቤቱ እንዲታረም ያዘዘውና ሪፖርተርም ስህተት መሆኑን አምኖ ተስተካክሎ እንዲነበብ አንባቢዎቹን የሚጠይቀው፣ የግብረሰዶም ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል በተባሉት ሁለት ወንድ ሕፃናት ዙሪያ ሙያዊ ማብራሪያ እንዲሰጡ የታዘዙትን የጠቅላይ ፍርድ ቤት የሳይኮሎጂና የሳይካትሪ ባለሙያን በሚመለከት ስለተሠራው ዘገባ ነው፡፡

በወቅቱ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ የሰጠው የጠቅላይ ፍርድ ቤት የሳይኮሎጂና የሳይካትሪ ሠራተኛ ሆኖ ሳለ፣ የሪፖርተር ዘጋቢ ግን ቀደም ብሎ የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ በምስክርነት ቆጥሯቸው የነበሩትን የሥነ ልቡና ባለሙያን ጠቅሶ ዘግቧል፡፡ በተፈጠረው ስህተትም ፍርድ ቤቱንና አንባብያንን ይቅርታ ይጠይቃል፡፡ (ምንጭ: ሪፖርተር)

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Law Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Comments

  1. Ermisha Beyene Petros says

    November 18, 2017 11:54 am at 11:54 am

    ግብረሰዶም ፈጽመዋል በሚል ጥርጣሬ ክስ የተመሠረተባቸው መምህራን ነፃ ወጡ
    December 01, 2013
    •ተጠርጣሪዎቹና የችሎት ታዳሚዎች በእንባ ተራጩ
    https://www.google.co.uk/url?sa=t&rct=j&q=&esrc=s&source=web&cd=1&cad=rja&uact=8&ved=0ahUKEwjoxZW43cfXAhXDrxoKHdnvAZ0QFggoMAA&url=https%3A%2F%2Fwww.facebook.com%2Fpermalink.php%3Fstory_fbid%3D1431909613690818%26id%3D1411286192419827&usg=AOvVaw3GJWTVsP_rfsUtSx3tV9zd

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የጃኖ ስጦታና የዶሮ ፖለቲካ በጎንደር March 10, 2026 09:24 am
  • “አዲሷ” ኢህአፓ፤ ከንፈሯን ቀለም የተቀባች አሳማ February 25, 2026 11:24 am
  • የተንጋደደው የገዱ መልስ February 6, 2026 03:05 pm
  • ሻዕቢያ “አክሱም ገብቶ ወጣቶች በጅምላ ሲረሽን ጸብ ተፋፍሟል …” February 4, 2026 01:15 pm
  • አደራ ጠባቂው የኢሉአባቦር ሕዝብ February 4, 2026 12:14 pm
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን January 28, 2026 09:56 am
  • በአሜሪካ ጥምር ዜግነት እንዲቀር ጥያቄ ቀረበ January 27, 2026 03:05 pm
  • “ከህወሓት፣ ከሻዕቢያ፣ ከግብፅ ሰዎች ጋር ሆኖ እንዴት የአማራን ጥያቄ ማስመለስ ይቻላል?” ኮሎኔል ፈንታው January 25, 2026 04:23 am
  • የኢትዮጵያ አየር ኃይል: ለአፍሪካ ሀገራት የመጀመሪያዎቹን የአየር ኃይል አብራሪዎች ያሰለጠነ ተቋም January 25, 2026 03:50 am
  • የአማረ ሪፖርተር እያደረሰ ያለው የብሔራዊ ደኅንነት አደጋ January 22, 2026 01:56 am
  • የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የማርያምን ማዕረግ ዝቅ አደረገች December 12, 2025 09:27 pm
  • ኢህአፓ: ከነጭ ሽብር ወደ “አዲስ አበባ ትናገር” የጎዳና ሽብር? December 12, 2025 09:11 pm
  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule