* የሠራዊቱ ሞራል ከፍ ብሏል
ከአርበኞች ግንባር ጋር የተዋሃደው የግንቦት ሰባት ሊቀመንበር ዶ/ር ብርሃኑ ነጋና የፓርቲው የአመራር አባላት የትጥቅ ትግሉን ለመቀላቀል ታጣቂዎቻቸው ወደሚንቀሣቀሱባት ኤርትራ ጠቅልለው መሄዳቸውን የአመራር አባላቱ አስታወቁ፡፡ ብርሃኑ አስመራ መግባታቸው ከተሰማ በኋላ የሠራዊቱ ሞራል ከፍ ማለቱና ከአገር ውስጥ ግምባሩን ለመቀላቀል የሚፈልገው ሕዝብ እየጨመረ መምጣቱ ይነገራል፡፡
ቁጥራቸው ይፋ ያልተደረገ የአርበኞች ግንቦት ሰባት የአመራር አባላትን ይዘው ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ወደ ኤርትራ ያመሩት ሌሎች አማራጮችን ጨምሮ በብረት ትግልና በሕዝባዊ ንቅናቄ የኢትዮጵያን ገዥ ፓርቲ ለማስወገድ መሆኑን የአመራር አባላቱ ይናገራሉ፡፡
“ዶ/ር ብርሃኑ ነጋና ጓዶቻቸው ትግል ወደሚካሄድባቸው አባባቢዎች ያመራሉ” ሲሉ የአርበኞች ግንቦት ሰባት አመራር አባል ዶ/ር ታደሰ ብሩ ለቪኦኤ ገልፀዋል፡፡ “ታጋዮቻችን ወዳሉባቸው ቦታዎች ያመራሉ፤ ታጋዮቻችን ኤርትራ ውስጥም እንዲሁም የኢትዮጵያ ውስጥም የገቡ አሉ፤ … ለመታገል ነው የገቡት፤ ለመሞት ነው የገቡት” ብለዋል፡፡ የቪኦኤው ሄኖክ ሰማግዜር ቁጥራቸው ምን ያህል የሆነ የግንቦት 7 አመራር አባላት ወደ አስመራ እንደሄዱ ላቀረበው ጥያቄ ታደሰ ብሩ ሲመልሱ ከደኅንነት አኳያ እንዲሁም አመራር አባላቱ በተለያየ ጊዜያት የሄዱ በመሆናቸው ቁጥራቸውን ለጊዜው ለመግለጽ እንደሚቸገሩ አስረድተዋል፡፡ ሆኖም የንቅናቄው ማዕከላዊ አመራር እዚያ እንዲሆን በመወሰኑ አመራሩ በሙሉ እዚያ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡
አመራሩም ሆነ ብርሃኑ ነጋ ለምን ያህል ጊዜ እዚያ እንደሚቆዩ ወይም ጠቅልለው ስለመግባታቸው ሲጠየቁ ታደሰ ብሩ የሰጡት ምላሽ “ትግሉ በድል እስኪያልቅ፣ እስኪጠናቀቅ ድረስ እዚያ ይቆያሉ” በማለት አስረድተዋል፡፡ ዶ/ር ብርሃኑም ከበክኔል ዩኒቨርሲቲ የምጣኔ ሃብት መምህርነት ሥራቸውን ለቅቀው ሙሉ ጊዜያቸውን ለትግሉ ለማዋል ጠቅልለው የገቡ መሆናቸውን አረጋግጠዋል፡፡ ከዩኒቨርሲቲው እንዴት እንደለቀቁ ወይም በምን ስምምነት እንደለቀቁ የመሳሰለውን አስተዳደራዊ ሁኔታ ለመመለስ እንደማይችሉ ዶ/ር ታደሰ ብሩ ተናግረዋል፡፡
በአሁኑ ጊዜ ግምባሩ ወታደራዊ እንቅስቃሴ ለማካሄድ አቅሙን ገንብቶ የተዘጋጀ መሆኑን ከግምባሩ ወታደራዊ አማካሪዎች የታመነበት መሆኑን በመናገር ወደፊትም አቅሙን እየገነባ እንደሚሄድ የኢትዮጵያ ሕዝብም ድጋፉን እየሰጠ እያገዘው እንደሚሄድ ጥሪ አዘል መልክዕክት አስተላልፈዋል፡፡ በማስከተልም ትግሉ የአርበኞች ግንቦት 7 ሳይሆን የኢትዮጵያ ሕዝብ የነጻነት ትግል እንደመሆኑ ሕዝቡ ትግሉን የራሱ አድርጎ እንደሚወስደው የሚታመን መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ዋንኛው ለማሳካት የሚፈልጉት ዓላማ ምን እንደሆነ ለተጠየቁት፤ የአርበኞች ግንቦት 7 ገና ከጅምሩ ሲመሰረት ጀምሮ ሊያሳካ የሚፈልገው መንግሥት ለመያዝ ሳይሆን መንግሥት የሚያዝበትን ሥርዓት ለማምጣት ነው፤ እስካሁን ሥልጣን በኃይል ወይም ጉልበት የሚያዝ በመሆኑ አሁን ግን ነጻነት፣ ሰላም፣ እኩልነትና ዴሞክራሲ የሰፈነባት ኢትዮጵያን ለመመሥረት የሚያስችል ሥርዓት ማምጣት ዋንኛ የግንቦት 7 አርበኞች ግምባር ዓላማ እንደሆነ አመራር አባሉ ታደሰ ብሩ አስታውቀዋል፡፡ ጉልበት መጠቀም የግምባሩ ዋንኛ ዓላማ እንዳልሆነ ይህም ግድ ሆኖ የተገባበት መሆኑን በመጥቀስ ዋንኛው ዓላማ የዴሞክራሲ ሥርዓትን መመሥረት እንደሆነ በማስረዳት ቃለምልልሳቸውን አጠናቅቀዋል፡፡
ለተጨማሪ የተያያዘውን የድምፅ ፋይል እዚህ ላይ ያዳምጡ፡፡
በሌላ በኩል ኢሣት ሰኞ ባሰራጨው የዜና ዘገባ መሠረት የብርሃኑ ነጋ ገና አስመራ መግባት በሠራዊቱ ውስጥ ከፍተኛ መነቃቃትን መፍጠሩን፤ ግንባሩንም ለመቀላቀል የሚጠይቀው ሕዝብ ከምንጊዜውም ይልቅ እየጨመረ መምጣቱን ዘግቧል፡፡ የዜናው ሙሉ ንባብ ከዚህ በታች ይገኛል፡፡
የፕ/ር ብርሃኑ ነጋ አስመራ መግባት በሰራዊቱ ውስጥ ትልቅ መነቃቃት ፈጥሯል
የአርበኞች ግንቦት7 ሊቀመንበር የሆኑት ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ “ለነጻነት፣ ለፍትህና ለዲሞክራሲ የሚደረገውን ትግል መሬት ላይ ወርዶ መምራት ይገባል” በሚል እምነት በከፍተኛ ውጣ ውረድ ከአሜሪካ ኤርትራ መግባታቸው እንደተሰማ በአርበኞች ግንቦት7 ሰራዊት ውስጥ ከፍተኛ መነቃቃት መፈጠሩን ፣ አስመራ በሚገኘው የድርጅቱ ጽህፈት ቤት አቀባበል ያደረጉላቸው ሻለቃ አክሊሉ መዘነ ተናግረዋል።
በዋና ጽህፈት ቤቱ የሚሰሩ የፖለቲካ እና የውጭ ግንኙነት ክፍል አባላት ለፕሮፌሰሩ በጋራ አቀባበል እንዳደረጉላቸው የገለጸው ሻለቃ አክሊሉ፣ ከአባላት ጋር ውይይት ማድረጋቸውን ገልጸዋል። በሰራዊቱ ውስጥ የታየው መነቃቃት ለነጻነት የሚደረገው ትግል እንዲፋጠን፣ በተለይም ከተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር የሚደረገውን ተቀራርቦ የመስራት ድርድር እንዲፋጠን እንደሚያደርገው ሳለቃ አክሊሉ ተስፋቸውን ገልጸዋል።
ፕ/ር ብርሃኑ አስመራ አየር ማረፊያ ሲደርሱ ከፍተኛ የኤርትራ ባለስልጣናት ተቀብለዋቸዋል። የፕ/ር ብርሃኑ አስመራ መድረስ ዜና ይፋ ከሆነ ጀምሮ፣ በአገር ውስጥ ከፍተኛ መነቃቃት መፈጠሩን ኢሳት ከተለያዩ አካባቢዎች የሚደርሱት መረጃዎች ያመለክታሉ።
አርበኞች ግንቦት7ትን ለመቀላቀል የሚጠይቀው ህዝብ እየጨመረ መምጣቱንም ከድርጅቱ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
ፕ/ር ብርሃኑ ግንቦት7ትን በሊቀመንበርነት ሲመሩ ቆይተው ፣ አርበኞች ግንቦት7 ውህደት ከፈጸሙ በሁዋላ የውህዱ ድርጅት ሊቀመንበር ሆነዋል። በውህደቱ ላይ ለመገኘት የነበራቸው ውጥን ከጉዞ ሰነድ ጋር በተያያዘ ባለመሳካቱ፣ ለመሪነት የተመረጡት በሌሉበት ነው። ይሁን እንጅ በውህደቱ ወቅት ለጉባኤተኛው በስልክ ባስተላለፉት መልክት፣ አንዳንድ ችግሮች ተፈተው በቅርቡ በረሃ ወርደው እንደሚቀላቀሉዋቸው ቃል ገብተው ነበር።
በምርጫ 97 በተደረገው ምርጫ አሸንፈው የአዲስ አበባ ከንቲባ ሆነው የተመረጡት ዶ/ር ብርሃኑ፣ ምርጫውን ተከትሎ በተፈጠረው ውዝግብ ከሁለት አመት ላለነሰ ጊዜ በእስር ቤት አሳልፈዋል። ከዚያም አሜሪካ በሚገኘው በክኔል ዩኒቨርስቲ በመምህርነት ሲያገለግሉ ቆይተው ከወራት በፊት የሙሉ ፕሮፌሰርነት ማእረግ አግኝተዋል።
ከዚህም ሌላ የአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ ሐምሌ 12፤ 2007ዓም “ሊቀመንበራችን ትግል ሜዳ ውስጥ ነው” በሚል ርዕስ ባሰራጨው መግለጫ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ወደ ትግሉ ሜዳ መውረዳቸውን አስታውቆ ነበር፡፡ የመግለጫው ሙሉ ቃል ከዚህ በታች ይነበባል፡፡
ሐምሌ 12 2007 ዓ.ም./July 19, 2015
ህወሓት በኢትዮጵያዊያን እና በኢትዮጵያ ላይ ያሰፈነው ዘረኛና ፋሽስታዊ አገዛዝ እንዲያበቃ፤ በምትኩም ፍትህ፣ ነፃነት፣ እኩልነትና ዲሞክራሲ የሰፈኑበት የፓለቲካና የኢኮኖሚ ሥርዓት እንዲመሠረት እና የሀገራችን አንድነት በጠንካራ መሠረት ላይ ለማኖር አርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ ተገዶ የገባበት የመረረ የአመጽ ትግል መጀመሩን ይፋ ማድረጉ ይታወቃል። በዚህም መሠረት ኢትዮጵያዊያን የነፃነት አርበኞች በጀግነትና በጽናት እየታገሉ ነው።
ይህ ትግል በባርነትና በነፃነት መካከል የሚደረግ ወሳኝ ትግል ነው። የዚህ ትግል ውጤት የእኛ የዚህ ዘመን ትውልድ ሕይወት ብቻ ሳይሆን የአገራችንን የወደፊት ታሪክ፤ የልጅ ልጆቻችንን ሕይወት ይወስናል። በዚህም ምክንያት ይህንን ትግል በድል መወጣት ግዴታችን ነው። በዚህ ወሳኝ ወቅት ለነፃነት ግድ ያለው ኢትዮጵያዊ ሁሉ ከጎናችን ሊቆም ይገባል።
አርበኞች ግንቦት 7 አመራሩን ሁኔታዎች በፈቀዱ መጠን እና ትግሉ በሚጠይቀው ቦታ እንዲገኙ የሚያደርግ መሆኑ ሲገልጽ ቆይቷል። አሁን ትግሉ በደረሰበት ደረጃ የአመራሩ በትግሉ ሜዳ ውስጥ መገኘት አስፈላጊ መሆኑ ታምኖበት ሊቀመንበሩን ጨምሮ አመራሩን ወደ ትግሉ ሜዳ አንቀሳቅሷል። በዚህም መሠረት የንቅናቄው ሊቀመንበር ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ወደ ትግል ሜዳ ወርዷል።
ትግሉ መሯል። ወሳኝ የሆነ ትግል ውስጥ ገብተናል። የትግሉ መሪዎች የሕይወት መስዋዕትነት እሚከፈልበት ቦታ ይገኛሉ። በአሁኑ ሰዓት የንቅናቄው አመራር በተሟላ ሁኔታ በትግሉ ሜዳ ውስጥ እንዲገኝ ማድረግ ተችሏል። ኢትዮጵያዊያን እጅ ለእጅ ተያይዘን ዘረኛው የህወሓት አገዛዝን ከጫንቃችን ለማስወገድ ቆርጠን እንድንነሳ አርበኞች ግንቦት 7 ጥሪ ያደርጋል።
ኢትዮጵያን ከህወሓት አገዛዝ ነፃ የሚያወጣው አርበኞች ግንቦት 7 ብቻ አይደለም። ስለሆነም ከሌሎች ድርጅቶች ጋር የሚደረገው ትብብር ቀዳሚ ትኩረት ከተሰጣቸው ሥራዎች አንዱ ነው። አርበኞች ግንቦት 7 ከሌሎች ኢትዮጵያዊያን ድርጅቶች ጋር በመተባበር የተቀጣጠለው ሕዝባዊ አመጽ ለድል እንዲበቃ ይታገላል። ኢትዮጵያዊያንም በያሉበትም በተመሳሳይ ልዩነቶቻቸውን አቻችለው በህወሓት ፋሽስታዊ አገዛዝ ላይ ክንዳቸውን እንዲያነሱ አርበኞች ግንቦት 7 ጥሪ ያደርጋል።
እነሆ የአርበኞች ግንቦት 7 ሊቀመንበር ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ በአካል ትግል ሜዳ ውስጥ ይገኛል። የሚችል ሁሉ እንዲከተል፤ መከተል የማይችል በያለበት ሁኖ ሁለገብ ትግሉን እንዲያጧጥፍ አርበኞች ግንቦት 7 ጥሪ ያደርጋል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!
አርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ
Israel n. says
Im proud of u guys indeed war was not an alternative but some times even God also chose it.may God be wt u.
Ewnetu says
I scoured many web sites about Birhanu Nega’s move to the front. It seems a summer vacation for him since his college is closed now. Few bloggers estimate the fighters’ number to 150. Is the photo a merely photo-op? First, why do we see limited number of fighters on the photo. The guy who held Ethiopian flag is an Eritrean army and why? Only 4 memebrs are from patriotic army (EPPF). Be real. Put your emotion aside, are we brainwashed by ESAT and G7. Think rationally. This is a merely joke.
Firew Ayenachew says
I hop your strugle will be succesfule