በራሳቸው ሕዝብ ላይ ሲደርስ ሰማይ የሚደፋባቸውና ዓለም ሁሉ አብሯቸው እንዲያለቅስ የሚፈልጉት ምዕራባውያን በሌሎች ላይ ለሚደርሰው ሰቆቃ ቅንጣት ታህል ግድ አይላቸውም። አንድ ማሳያ እንጥቀስ፤
የዛሬ 80 ዓመት አካባቢ ጃፓን የአሜሪካንን ድንበር ጥሳ ከሐዋይ ደሴቶች አንደኛዋ ላይ የሚገኘውን ወታደራዊውን የፐርል ወደብ ገና በጠዋቱ በድንገት አጠቃች፤ በወደቡ ላይ የነበሩት 8 መርከቦች ጉዳት ደረሰባቸው፤ አራቱ ሰጠሙ፤ በአጠቃላይ ወደ 20 የሚደርሱ መርከቦችና ጀልባዎች ከጥቅም ውጪ ሆኑ፤ ከ300 በላይ የሚሆኑ አውሮፕላኖች፣ ጀቶችና ሔሊኮፕተሮች ከፍተኛ ጉዳት ደረሰባቸው፤ ከሁሉ በላይ ከ2,400 በላይ የሚሆኑ ባሕረኞች፣ ወታደሮችና ሰላማዊ ሰዎች ሕይወታቸውን አጡ፤ ከ1,000 በላይ የሚሆኑ ደግሞ ቆሰሉ።
በቀጣዩ ቀን ዲሴምበር 8፣ 1941 የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ፍራንክሊን ሩዝቬልት ሁለቱንም ምክር ቤት ሰብስበው ለአሜሪካ ሕዝብ ንግግር አደረጉ። “የጃፓን ንጉሣዊ የባሕርና የአየር ኃይል ሆን ብሎና በድንገት በአሜሪካ ላይ ያደረሰበት የትላንቱ ዲሴምበር 7፤ 1941 ጥቃት በታሪክ በክፋት ሲታወስ የሚኖር ቀን ይሆናል” በማለት ለሕዝባቸው ተናገሩ። ሲቀጥሉም፤ “ይህንን ሆን ብሎና በዕቅድ የደረሰብንን ጥቃት የቱንም ያህል ጊዜ ይውሰድ የአሜሪካ ሕዝብ ባለው ኃያል ጽድቅ በማሸነፍ ፍጹም ድል እንደሚጎናጸፍ ምንም ጥርጥር የለም” ካሉ በኋላ አሜሪካ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ውስጥ መግባቷን ይፋ አደረጉ፤ በቀጣይም ከ4 ዓመታት በኋላ አሜሪካ ሒሮሺማ እና ናጋሳኪ የሚባሉ የጃፓን ከተሞችን በአቶሚክ ቦምብ አወደመች። በመጨረሻም አሜሪካና አጋሮቿ ጦርነቱን በበላይነት አሸንፈው ክብራቸውን አስጠበቁ።
በምዕራባውያን ትከሻ ተንጠላጥለውና በጉልበተኛ ሤራቸው ተደግፈው ወደ ሥልጣን በመምጣት ኢትዮጵያን በግፍ ሲገዙ የነበሩት ትህነጎች በወታደራዊ ብቃታቸውና ጀግንነታቸው ድል እንዳደረጉ ራሳቸውን አሳምነው እንወክለዋለን የሚሉትን ሕዝብ ይህንኑ የውሸት ድል እያጠጡ በስካር አኖሩት። “ተራራ አንቀጥቃጭ”፣ “በድንጋይ ኮሎኔል ማራኪ”፣ ወዘተ በሚል ባዶ ፕሮፓጋንዳ ራሳቸውን ክበው የማይሸነፉ፣ የማይገረሰሱ፣ የማይንኮታኮቱ አድርገው ሕዝብን ለማሳመን ብዙ ጣሩ።
ይህንን ሲጠጣና ሲያጠጣ የኖረው ደጋፊና የጥቅማቸው ተካፋይ ሁሉ የትግራይን ሕዝብ በጦርነት ለመማገድ ከሩቅ ሆኖ “ጦርነት ባሕላዊ ጨዋታችን ነው”፣ “ጦርነትን እንፈጥራለን”፣ “እኛ ከእስራኤል በላይ ነን”፣ ወዘተ በማለት ውድቀቱን በሚያፋጥን ዕብሪት ተወጠረ።
የዚህ ሁሉ ጥርቅም ዕብሪትና ከኢትዮጵያ ተዘርፎ ሲከማች የነበረ በርካታ ገንዘብ፣ የቡድንና የግል የጦር መሣሪያ፣ ተተኳሽ፣ ወዘተ ባንድ በኩል፤ በሌላ ደግሞ የምዕራባዊያን አለሁላችሁ ባይነት ተደምሮ የዛሬ ሁለት ዓመት ትህነግ የሰሜን ዕዝን ጥቅምት 24 ቀን በድንገት አጠቃ። ሲያበላው፣ ሲያርስለት፣ አንበጣ ሲከላከልለት፣ ከደሞዙ ቆጥቦ ትምህርት ቤትና መንገድ ሲያሰራለት የነበረውን ወታደር በግፍ ጨፈጨፈ፣ በተቀናጀና በተጠና ሰዓት በሰሜን ዕዝ ሥር በሚገኙ ክፍሎች ሁሉ የሚገኘውን ወታደር በቁጥጥሩ ሥር በማዋል የእጅ ሥጡ ጥያቄ አቀረበ።
ኢትዮጵያ በዕቅድ፣ በግልጽና በማያሻማ መልኩ የተከፈተባትን ጥቃት ለመመከት ጦርነት ውስጥ መግባት ግድ ሆነባት። በሁሉም የምድር ኃይል የበላይነት የነበረውንና በወታደር ብዛት በትንሹ አምስት የትህነግ ታጣቂ ለአንድ የኢትዮጵያ ወታደር በሆነበት ጦርነት እውነትን፣ ልበሙሉነትንና ኢትዮጵያዊነትን የተጎናጸፉት ልጆቻችን ትህነግን በ15 ቀናት አስተነፈሱት። የትህነግ ዓይነት ትዕቢት ግን ቶሎ አይተነፍስምና አንጋሾቹን ምዕራባውያንን ተማምኖ ደግሞ ደጋግሞ ጥቃት ሰነዘረብን፤ ደግሞ ደጋግሞ አሳፋሪ ወታደራዊ ሽንፈት ተቀበለ። ትላንት ጥቅምት 23 ቀን ደግሞ በፕሪቶሪያ ፖለቲካዊ ሽንፈትን በመቀበል ትጥቅ እፈታለሁ አለ።
ትህነግ በአገራችን ላይ ያደረሰው መጠነ ሰፊና ሁሉን ዓቀፍ ውድመት በአንድ ትውልድ ተዘክሮ፣ በጥቂት መጽሐፍት ተጽፎ፣ በጥቂት ስብሰባ ተወያይቶ የሚያበቃ አይደለም። ላለፉት 80 ዓመታት የናዚ ወንጀል ተወርቶ እንዳላለቀ የትህነግም እንዲሁ የሚያልቅ አይደለም።
ጀርመኖች ናዚ ያደረሰባቸውን ደግመው ደጋግመው ያስቡታል፣ ይጽፉበታል፣ ይተውኑታል፣ በታሪክ ይማሩታል፣ በየዓመቱ ያከብሩታል፤ ወዘተ። ከዚያ አልፎ የዓለም ሕዝብ እንዲማርበት ልዩ ልዩ ማሳያዎችን ያቀርባሉ። በርሊን ከተማ ውስጥ የናዚን ግፍ የሚያስታውሱ ነገሮች በየቦታው አሉ። አንዳንዶቹ በምን ዓይነት ዝርዝር እና ጥንቃቄ ተሰንደው እንደተቀመጡ መመልከቱ እጅግ ያስደምማል።
ጥቅምት 24 የትህነግ የግፍ ቁንጮ የታየባት ቀን ናት። ራሳቸውን “የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጪ ግምባር” ብሎ በመሰየም የትግራይን ሕዝብ ሽፋን በማድረግ፤ “የምታገለው ለአንተ ነጻነት ነው” በማለት፤ መልሶ እታገልለታለሁ ያለውን ሕዝብ ያስጨፈጨፈው፣ ያስራበው፣ የግፈ ሰለባ ያስደረገው፣ … ራሱን ህወሓት እያለ የሚጠራው የወንበዴዎች ቡድን የኢትዮጵያን የሥልጣን መንበር ከተቆናጠጠ በኋላ የትግራይ ሰዎችን በሌላው ኢትዮጵያዊ ለማስጠላትና “ስም ለማሰጠት” እንዲሁም ለማጠልሸት 50 ዓመታት ሲሰራ ቆይቷል።
“እነዚህ” በኮ/ሎ ጎሹ ወልዴ የዛሬ 30 ዓመት አነጋገር “የሰከረ ርዕዮትዓለም የሚከተሉ፣ በብሄርና በጎሳ ፖለቲካ ላይ የተተከሉ ጠባብ ቡድኖች፣ በስታሊናዊ መርህ የተጠመቁ፣ እንኳንስ 50 ሚሊዮን ሕዝብ ያላት አገር ቤተሰብን የመምራትና የማስተዳደር ተሞክሮ የሌላቸው፣ …” የኢትዮጵያን ሃብት እየዘረፉ በትግራይ ኢንቨስት በማድረግ፣ የትግራይ ተወላጆችን የተለያዩ ስልቶችን – ከግድያ እስከ ማስገደድ – እየተጠቀሙ የወንጀላቸው ተባባሪ እንዲሆኑ በማድረግ፤ ትግራዮችን ከሌላው የኢትዮጵያ ሕዝብ በማስጠላት ጉዳዩን ከራሳቸው በማውረድ በሕዝብ መካከል የሚደረግ በማስመሰል እኩይ ተግባራቸውን ሲወጡ ቆይተዋል። ለሆዳቸው ያደሩን በፕ/ር መስፍን አነጋገር “አእምሯቸው የሻገተባቸው” ይህንን ማታለያና ማባበያ እየወሰዱ ከሌላው የኢትዮጵያ ወገናቸው ጋር ሆድና ጀርባ በመሆን “ነጻ አውጣኝ” ብለው በስምምነት ያልሰየሙት ቡድን ባዶ ተስፋ እየሰጠ የውንብድና ተግባር ሲፈጽምባቸው የተግባሩ ተባባሪዎች ሆነዋል።
- የ“ግንቦት 20” ሃያ መርዛማ ፍሬዎች! (ክፍል 1)
- የ“ግንቦት 20” ሃያ መርዛማ ፍሬዎች – የመሬት ነጠቃና ስደት (ክፍል ሁለት)
- የ“ግንቦት 20” ሃያ መርዛማ ፍሬዎች – የመንግሥት ውሸት፣ የሃይማኖት ተቋማት ውድቀት፣ … (ክፍል ሦስት)
- የ“ግንቦት 20” ሃያ መርዛማ ፍሬዎች — የአንድ ጎጥ የበላይነትና የመበታተን አደጋ!
- የ“ግንቦት 20” ሃያ መርዛማ ፍሬዎች! “ክፋት” – በሁሉም መስክ!!
ትህነግ በተለይ ከትግራይ ጀምሮ በመላው ኢትዮጵያ ላለፉት 50 ዓመታት የበተነው መርዝ እንዲህ በቀላሉ የሚረሳና የሚተው አይደለም። ደግሞ እንዳይመጣ ደግሞ ደጋግሞ መታወስና መነገር አለበት። የጉዳቱ መጠን እንዴት አገር አልባ ሊያደርገን እንደነበር አሁን ላለነውም ወደፊት ለሚመጣውም ትውልድ ያለማቋረጥ ሊነገር፣ ሊታወስ፣ ሊዘከር ይገባል።
ስለዚህ ትህነግ ባላሸነፈው ጦርነት ለ27 ዓመታት ደርግን ድል ያደረግሁበት ቀን እያለ የሚያከብረው ግንቦት 20 ተራ የሥራ ቀን መሆን አለበት። መቀየር ያለበት ሕግ በፓርላማው መቀየር አለበት። በምትኩ የጥቅምት 24 ቀን በክብር እና በታላቅ ጥሞና በመላው አገራችን መከበር አለባት።
ድል የተቀዳጀነው ለግማሽ ምዕተ ዓመት በመሣሪያ፣ በሃብት፣ በቁስ፣ በፕሮፓጋናዳ ራሱን ካገዘፈ፣ መርዛማ ሥሩን በመላ አገሪቱና በውጭ ካሉ ጠላቶች ጋር አብሮ በዘረጋ ታሪካዊ ነቀርሳ ላይ ነውና ጥንቃቄ ያስፈልጋል። ጥንቃቄ ብቻ ሳይሆን ብልጠትም ግድ ነው። ባለማስተዋል መርዙ እንዲያገረሽ ምቹ ሁኔታ ልንፈጥር እንደምንችል መረዳት ያስፈልጋል። ስለዚህ ጥቅምት 24 ታስቦ የሚውል ሳይን ተከብሮ የሚውል ቀን መሆን ያለበት።
ትህነግ ቢወላልቅም ጭራሽ ዓመድ እስኪሆን ጊዜና ጥበብ ስለሚያስፈልግ ከተራ የብሽሽቅ፣ “ድሉ የኔ ነው” ከሚል ያበጠ ስሜት መላቀቅና የፈራረሰው ትህነግን ብቻ በመለየት ከትግራይ ሕዝብም ጋር የቀደመውን መርዝ ያላጎደፈው ግንኙነት ለመመሥረት መሥራት ከዜጎች ሁሉ ይጠበቃል። ትህነግ ያከማቸውን ብረት ለማስረከብ የተገደደው ልክ የዛሬ ዓመት በክህደት በታረደው ኩራታችን የመከላከያ ሠራዊትና ጥምር ኃይሎች ደምና መስዋዕትነት በመሆኑ፣ አስተዋይነትን ማጣት ማለት በዚህ ውድ የሕይወት ዋጋ እንደመጫወት ይቆጠራልና ድሉን በብልሃትና በማስተዋል እናጽናው። ከዚህ አኳያ ድሉን ለማኮሰስና በሳንቲም ለቀማ ላይ በመሰማራት ያልተፈጠሩ ወሬዎችን በማኅበራዊ ሚዲያ በማሰራጨት የተሰማሩትን፤ ሕዝብን የሚያሸብር የሤራ ትንተና የሚሰጡን ሁሉ መንግሥት በሕግ እኛም እንደ ዜጋ በንቃት ልናስተናግዳቸው ይገባል።
ጥቅምት 24ን አንረሳም ስንል በጥቂት ደቂቃዎች የእጅ በደረት ሥርዓት ብቻ የሚታለፍ መሆን የለበትም። ግንቦት 20ን ተክቶ ጥቅምት 24 በይፋ በመላው ኢትዮጵያና በዳያስፖራው ዘንድ የሚከበር በዓል መሆን አለበት። ጥቅምት 23 ትህነግ ያሸብረን የነበረበትን ትጥቅ እፈታለሁ ብሎ ዕብሪቱ የተነፈሰበት ትልቅ የድል ቀን ነው። የካቲት 23 የምዕራባውያንን ዕብሪት ያስተነፈስንበት የዓድዋ ድል በዓላችን ቀን ነው። ጥቅምት 24 ደግሞ አገራችን እንድትፈርስ ከተደገሰላት የክፋት ድግሥ ዓድዋን እያሰብን ድል ያደረግንበትና መቼም የማንረሳው ቀን የዘመናችን ዓድዋ ነው። ሥራ የማይሠራበት ቀን ሆኖ ይከበር ዘንድ ጥሪ እናቀርባለን።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
ይህ ርዕሰ አንቀጽ የ“ጎልጉል: የድረገጽ ጋዜጣ™” አቋም ነው።
Leave a Reply