• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ጋዜጠኞቹና ጦማሪያኑ ፍ/ቤት ሳይቀርቡ የምርመራ መዝገቡ መዘጋቱ ሕገወጥና አደገኛ መሆኑ ተገለጸ

July 16, 2014 10:32 pm by Editor Leave a Comment

በሽብርተኝነት ወንጀል ተጠርጥረው በክስ ላይ የሚገኙት ሦስት ጋዜጠኞችና ስድስት ጦማርያን ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ፖሊስ ‹‹ምርመራዬን ስለጨረስኩ መዝገቡ ይዘጋልኝ›› በማለት መዝገቡ እንዲዘጋ ማድረጉ ሕጉን ያልተከተለና አደገኛ መሆኑን ጠበቃቸው አስታወቁ፡፡

ተጠርጣሪ ጋዜጠኞች ተስፋለም ወልደየስ፣ አስማማው ኃይለ ጊዮርጊስ፣ ኤዶም ካሳዬና ጦማሪያንና የሕግ መምህር ዘለዓለም ክብረት፣ ናትናኤል ፈለቀና አጥናፉ ብርሃኔ ሐምሌ 5 ቀን 2006 ዓ.ም. በፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት የሚቀርቡበት ዕለት ነበር፡፡ እንደወትሮው ሁሉ የተጠርጣሪዎች ቤተሰቦች፣ የአገር ውስጥና የውጭ አገር ጋዜጠኞች፣ ጓደኞቻቸውና የተለያዩ የችሎት ታዳሚዎች በጠዋት ማልደው በፍርድ ቤት ግቢ የተገኙ ቢሆንም፣ እስከ ቀኑ 5፡30 ሰዓት ድረስ ፖሊስም ሆነ ተጠርጣሪዎቹ ወደ ችሎቱ አልመጡም፡፡ ከ5፡30 ሰዓት በኋላ ሌሎች ፍርድ ቤት የሚቀርቡ ተጠርጣሪዎቹና ፖሊስ ችሎት ቆይተው ሲወጡ፣ የተጠርጣሪዎቹ ጠበቃ አቶ አመሐ መኮንን፣ ደንበኞቻቸው ፍርድ ቤት መቅረብ አለመቅረባቸውን ለማጣራት የዕለቱን ተረኛ ዳኛ ለማነጋገር ገቡ፡፡ ጠበቃው ስለደንበኞቻቸው ፍርድ ቤቱን ሲጠይቁ፣ ፖሊስ ምርመራውን መጨረሱን በማሳወቅ መዝገቡ እንዲዘጋለት ጠይቆ መዘጋቱን ሲያስረዳቸው፣ ‹‹እንዴትና በምን ሁኔታ?›› የሚል ጥያቄ ቢያቀርቡም፣ ከመዘጋቱ ውጪ ምንም ምላሽ ሊያገኙ አለመቻላቸውን ተናግረዋል፡፡

እስረኛ ፍርድ ቤት ሳይቀርብ የምርመራ መዝገቡ ሊዘጋ እንደማይችል የሚናገሩት ጠበቃ አመሐ፣ ተጠርጣሪዎቹ ከሐምሌ 5 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ላይ መሆናቸው፣ በሕግ አግባብ በፍርድ ቤት ምንም ትዕዛዝ ባልተሰጠበት ሁኔታ በመሆኑ ድርጊቱ ሕገወጥና አደገኛ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡

ፖሊስ ምርመራውን ካጠናቀቀ ተጠርጣሪዎቹን ፍርድ ቤት ይዞ በመቅረብ ለፍርድ ቤቱ ማስረዳትና ክስ እስከሚመሠረትባቸው ድረስ በዋስ እንዲቆዩ ወይም የሕግ ሥርዓቱ በሚፈቅደው መሠረት ስለሚቆዩበት ሁኔታ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ መስጠት እንደነበረበት አስረድተዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ባልሰጠበት ሁኔታ ተጠርጣሪዎቹ ባሁኑ ወቅት የት እንዳሉ እንደማይታወቅ የሚናገሩት ጠበቃው፣ በወንጀል ሕጉና በሕገ መንግሥቱ በተጠሰው አካልን ነፃ የማውጣት መብት (ሐቢየስ ኮርፐስ) ክስ ሊመሠርቱ እንደሚችሉ ገልጸዋል፡፡

በሌላ የምርመራ መዝገብ የተካተቱት ጦማሪያን ማህሌት ፋንታሁን፣ አቤል ዋበላና በፈቃዱ ኃይሉ ደግሞ ፍርድ ቤት መቅረብ የነበረባቸው ሐምሌ 7 ቀን 2006 ዓ.ም. የነበረ ቢሆንም፣ ተጠርጣሪዎቹም ሆኑ መርማሪ ፖሊስ ሳይቀርቡ መቅረታቸውን ጠበቃው ጠቁመዋል፡፡

ዘጠኙም ተጠርጣሪዎች ‹‹የመብት ተሟጋች ነን›› ከሚሉ የውጭ ኃይሎች ጋር በሙሉ ሐሳብና ገንዘብ በመስማማት ሕዝብን የማተራመስ፣ አገርንና መንግሥትን የማፍረስ ዘገባ በኢንተርኔትና በተለያዩ ድረ ገጾች ያልሆነ መረጃ ሲያስተላልፉ ተገኝተዋል በሚል ፖሊስ ሚያዝያ 17 እና 18 ቀን 2006 ዓ.ም. በቁጥጥር ሥር እንዳዋላቸው መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ፖሊስ በተጠርጣሪዎቹ ላይ ለሁለት ጊዜ የ14 ቀናት የምርመራ ጊዜ ጠይቆ ከተፈቀደለት በኋላ፣ በሦስተኛው የፍርድ ቤት ቀጠሮ የተጠርጣሪዎቹ ጉዳይ ውስብስብና ድርጊቱም የሽብርተኝነት ድርጊት መሆኑን በመጥቀስ፣ ለተጨማሪ ምርመራ 28 ቀን እንዲፈቀድለት የፀረ ሽብርተኝነት ሕጉን በመጥቀስ ተፈቅዶለት መመርመር ላይ መሆኑን መዘገባችን አይዘነጋም፡፡ ተጠርጣሪዎቹ በቁጥጥር ሥር ከዋሉ 78 ቀናት ሞልቷቸዋል፡፡(ታምሩ ጽጌ፤ ሪፖርተር ጋዜጣ)

በጋዜጠኞቹና ጦማሪያኑ ላይ የተከፈተው የጊዜ ቀጠሮ ፋይል ተዘጋ

“ደንበኞቼ አሁን ያሉበት ሁኔታ ሕገ-ወጥ ነው” ጠበቃ አመሃ መኮንን

ፖሊስ በሽብር ወንጀል ጠርጥሮ በህቡዕ ሲንቀሳቀሱ፤ በማኅበራዊ ድረ-ገጾች መረጃዎችን ሲለዋወጡና በውጪ ሀገራት ከሚገኙ ተቋማት ጋር ስልጠና ወስደው፤ ህዝባዊ አመጽ ለመቀስቀስ የገንዘብ ድጋፍ አግኝተው፤ በሕጋዊ መንገድ ስልጣን የጨበጠውን መንግስት በሕገ-ወጥ መንገድ ለማፍረስ ሲንቀሳቀሱ ደርሼባቸዋለሁ በሚል ከሁለት ወራት በላይ አስሮ በማዕከላዊ ምርመራ ላይ የቆዩት ዘጠኙ ጋዜጠኞችና የዞን ዘጠኝ ጦማሪያን በፖሊስ ተከፍቶባቸው የነበረው የጊዜ ቀጠሮ ፋይል ተዘግቶ፤ ወደ ዐቃቤ ሕግ መመራቱን በድንገት ስለመስማታቸው የተጠርጣሪዎቹ ጠበቃ አመሃ መኮንን አስታወቁ።zone9 ers

ባሳለፍነው ቅዳሜ እና ሰኞ (ሐምሌ 5 እና 7 ቀን 2006 ዓ.ም) በፌዴራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት አራዳ ምድብ 1ኛ ወንጀል ችሎት፤ በሁለቱ ቀናት ተለዋጭ ቀጠሮ የነበራቸው ዘጠኙ ተጠርጣሪዎች ፍርድ ቤት ባልቀረቡበት፤ የአያያዝ ሁኔታቸውን በግልፅ ለችሎቱ ባላስረዱበትና የዋስትና መብታቸውን ጠይቀው ምላሽ ባልተሰጠበት አኳሃን ጠበቃቸው ሲቀርቡ ፖሊስ የጊዜ ቀጠሮ ፋይሉን ስለመዝጋቱና በቀጣይ ጉዳዩ ለፌዴራል ዐቃቤ ሕግ ደርሶ ክስ ሊመሠረትባቸው መሆኑን ከችሎት መስማታቸውን የሚናገሩት ጠበቃ አመሃ መኮንን፤ በፍርድ ቤቱ ፋይሉ የተዘጋበትን ሁኔታ በተመለከተ “የተለመደ አሠራር ነው” የሚል ምላሽ ማግኘታቸውን ያስረዳሉ። ጠበቃው ሒደቱን ስርዓቱን ያልተከተለና የደንበኞቻችንንም ሕጋዊ መብት የጣሰ ነው ሲሉ ይናገራሉ። በተለይም በሰኞው ዕለት (ሐምሌ 7 ቀን 2006 ዓ.ም) ቀጠሮ በፍርድ ቤት ግቢ ውስጥ ቀደም በማለት ተገኝተው እንደነበር ያስታወሱት ጠበቃው፤ ሦስቱም ተከሳሾች ማለትም በዕለቱ የተቀጠሩት ማህሌት ፋንታሁን፣ በፍቃዱ ኃይሉና አቤል ዋበላ ባልቀረቡበት፤ እንዲሁም አንድም የመርማሪ ቡድኑ አባል ባልተገኘበት ከመዝገቡ ጋር ተያያዞ በቀረበ ወረቀት አማካኝነት ብቻ መዝገቡ መዘጋቱንና ወደመደበኛ ክስ ለመግባት ዐቃቤ ሕግ ክስ እስኪመሰረት እየተጠበቀ መሆኑን ተናግረዋል።

መርማሪ ቡድኑ መዝገቡን አጠናቅሮ ከቀረበለት የፌዴራሉ ዐቃቤ ሕግ በቀጣዮቹ አስራ አምስት ቀናት ውስጥ ክሱን መስርቶ በፍርድ ቤት መቅረብ እንደሚኖርበት የአሠራር ሂደት መኖሩን የጠቆሙት ጠበቃ አመሃ መኮንን፤ ደንበኞቻቸው መቼና የት እንደሚቀርቡ አሁን ድረስ አለማወቃቸውን አስረድተዋል። ደንበኞቼን በሙሉ ማግኘት አልቻልኩም። ለዚህም እስረኞቹን ለመጐብኘት ከዕረቡና ከአርብ ቀን ውጪ ክልክል መሆኑና በአንድ ቀን አንድ ሰው አንድ ደንበኛን ብቻ የማግኘት ገደብ መኖሩን እንደመሰናክል በመጥቀስ አሠራሩ ችግር እንዳለበትም አክለው ገልፀዋል።

“ደንበኞቼ አሁን ያሉበት ሁኔታ ሕገ-ወጥ ነው” የሚሉት ጠበቃው፤ ለዚህም የጊዜ ቀጠሮውን ሲሰማ የነበረው ፍርድ ቤት ታስረው ይቆዩ የሚል ትዕዛዝን ባልሰጠበት፤ አልያም ክስ ተመስርቶባቸው ክሱን የሚሰማው ፍርድ ቤት በእስር ሆነው ጉዳያቸውን ይከታተሉ ባላለበት ሁኔታ ውስጥ ከቅዳሜው 4 ሰዓት እና ከሰኞው 8 ስዓት ጀምሮ ጋዜጠኞቹና ጦማሪያኑ ታስረው የሚቆዩበት ሁኔታ ሕጋዊ መሠረት የለውም” ሲሉ አስረድተዋል። ከዚህ ቀጣይ እርምጃቸው የሚሆነው አካልን ነፃ የማውጣት ክስ በመመስረት ደንበኞቻችን ነፃ እንዲሆኑ ለማስቻል እየተዘጋጀን ነው ብለዋል። (አሸናፊ ደምሴ፤ ሰንደቅ ጋዜጣ)

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: News Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የጃኖ ስጦታና የዶሮ ፖለቲካ በጎንደር March 10, 2026 09:24 am
  • “አዲሷ” ኢህአፓ፤ ከንፈሯን ቀለም የተቀባች አሳማ February 25, 2026 11:24 am
  • የተንጋደደው የገዱ መልስ February 6, 2026 03:05 pm
  • ሻዕቢያ “አክሱም ገብቶ ወጣቶች በጅምላ ሲረሽን ጸብ ተፋፍሟል …” February 4, 2026 01:15 pm
  • አደራ ጠባቂው የኢሉአባቦር ሕዝብ February 4, 2026 12:14 pm
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን January 28, 2026 09:56 am
  • በአሜሪካ ጥምር ዜግነት እንዲቀር ጥያቄ ቀረበ January 27, 2026 03:05 pm
  • “ከህወሓት፣ ከሻዕቢያ፣ ከግብፅ ሰዎች ጋር ሆኖ እንዴት የአማራን ጥያቄ ማስመለስ ይቻላል?” ኮሎኔል ፈንታው January 25, 2026 04:23 am
  • የኢትዮጵያ አየር ኃይል: ለአፍሪካ ሀገራት የመጀመሪያዎቹን የአየር ኃይል አብራሪዎች ያሰለጠነ ተቋም January 25, 2026 03:50 am
  • የአማረ ሪፖርተር እያደረሰ ያለው የብሔራዊ ደኅንነት አደጋ January 22, 2026 01:56 am
  • የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የማርያምን ማዕረግ ዝቅ አደረገች December 12, 2025 09:27 pm
  • ኢህአፓ: ከነጭ ሽብር ወደ “አዲስ አበባ ትናገር” የጎዳና ሽብር? December 12, 2025 09:11 pm
  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule