• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ያስፈራል፤ ግን ኢትዮጵያ አትፈርስም!

August 19, 2016 11:37 pm by Editor 1 Comment

* ከዚህ በፊት ቀድመው ፈራርሰዋል፤ ወደፊትም ይፈራርሳሉ።

ይህንን የፕሮፌስር መስፍን ወልደማርያም ጽሁፍ October 22, 2012 አትመነው ነበር። ሆኖም አገራችን ካለችበት ወቅታዊ ሁኔታ አኳያ አግባብነት ያለው ሆኖ ስላገኘነው እንደገና አትመነዋል፡፡

ይቺ ኢትዮጵያ የምትባል አገር ስንት የመከራ ወንዞችን ተሻግራለች! ገና ስንት ትሻገራለች! ስንት የግፍ ተራራዎችን አቋርጣለች! ገና ስንት ታቋርጣለች! ስንት የበደል ሰይፎችንና ጦሮችን አምክናለች! ገና ስንት ታመክናለች! ስንት የውጭ ኃይሎችን አሳፍራለች! ገና ስንቱን ታሳፍራለች! ስንት አምባገ- ነኖችን እያለቀሰች ቀብራለች! ገና ስንቱን ትቀብራለች! ጭቆና ከኢትዮጵያውያን ደም ሙልጭ ብሎ ወጥቶ በነፃነት፣ በእኩልነት፣ በዳኝነት በጠራ ደም እስቲተካ ድረስ “ኢትዮጵያ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ዘርግታ” ትጸልያለች! እግዚአብሔርም ቃል ኪዳን አለበት ይሰማታል! የኃያላን ኃያል ኢትዮጵያ እንድትፈርስ አይፈቅድም!

የኢትዮጵያን መፈራረስ የሚመኙ ግለሰቦችም መንግሥቶችም ሞልተዋል፤ ኢትዮጵያ እንድትፈራርስ የሚመኙ ጭንጋፍ ልጆችም አሏት፤ ማኅጸንዋ እየደማ እየረገማቸው ሰላምና እንቅልፍ አጥተው አብጠው ይፈነዳሉ፤ የኢትዮጵያን መፈራረስ የሚመኙ መንግሥቶች ሁሉ ከዚህ በፊት ቀድመው ፈራርሰዋል፤ ወደፊትም ይፈራርሳሉ።

የአገራቸው ፍቅር፣ የእርስበርሳቸው ዝምድና፣ የተራራውና የሸለቆው፣ የሜዳውና የገደሉ፣ የበረሀውና የለምለሙ፣ የዝናቡና የወንዙ፣ የዓየሩና የነፋሱ፣ የበዓላቱና የድግሱ፣ ያለውን አብሮ መቋደሱ፣ ተዝካሩ፣ ሙታዓመቱ ለሞቱ፣ መላእክቱ፣ ቅዱሳቱ፣ ሰማዕታቱ፣ እየተሸከሙ ያደረሱት ጸሎቱ፣ ለምዕተ-ዓመታት የተከማቸው እምነቱ፣ ሃይማኖቱ፣ በዚህ ሁሉ የተገነባው ኅብረቱ እንዴት ይፈርሳል! ማን ችሎ ያፈርሰዋል! አፍራሾች ቀድመው ይፈርሳሉ!

አንዳንዶች ቢጨነግፉም፣ አንዳንዶች ቢክዱም፣ አንዳንዶች ሆዳም ቢሆኑም፣ አንዳንዶች ቢወላውሉም፣ ኢትዮጵያ ልጆች አሏት፣ አሁንም የሚሞቱላት፣ ያልበሏት፣ የሚሳሱላት፤ ያልሸሿት፤ አፈሯን የሙጢኝ ብለው አፈርሽ እንሁን የሚሏት፣ ደሀነትም ሆነ ጭቆና ካንቺ አይለዩንም የሚሏት፤ ኢትዮጵያ ዛሬም ልጆች አሏት ስትፈርስ ቆመው የማያዩ፣ ሲያማት ነፍሳቸውን ዘልቆ የሚያማቸው፣ ሳልፈርስ አትፈርስም ነው ቃል ኪዳናቸው!

ቱርክና ግብጽ መጥተው ሄደዋል፤ ፖርቱጋል መጥቶ ሄዷል፤ እንግሊዝ መጥቶ ሄዷል፤ ኢጣልያ መጥቶ ሄዷል፤ ጠላቶች እየመጡ በመጡበት ተሸኝተዋል፤ ወዳጆች በጨዋነት ተስተናግደው ተዋኅደዋል፤ ቤተ ሙሴ፣ ቤተ ክርስቲያን፣ ቤተ እስልምና ኢትዮጵያዊ ሆነዋል፤ ዛሬ እንግዳ አይደሉም፤ ዛሬ ባዕድ አይደሉም፤ ኢትዮጵያ በፍቅር ለመጣ ፍቅር ነች፤ ምቹ ነች፤ በጠብ ለመጣ እሾህ ነች፤ ትዋጋለች።

ኢትዮጵያ፣ ነቢዩ ኢሳይያስ ለአንቺ የተናገረው ይመስለኛል፤ ‹‹ብርሃንሽ መጥቶአልና፣ የእግዚአብሔርም ክብር ወጥቶልሻልና ተነሺ፤ አብሪ፤ እነሆ ጨለማ ምድርን ድቅድቅ ጨለማም አሕዛብን ይሸፍናል፤ ነገር ግን በአንቺ ላይ እግዚአብሔር ይወጣል፤ ክብሩም በአንቺ ላይ ይታያል፤ አሕዛብም ወደብርሃንሽ፣ ነገሥታትም ወደመውጫሽ ጸዳል ይመጣሉ። ዓይኖችሽን አንስተሽ በዙሪያሽ ተመልከቺ፤ እነዚህ ሁሉ ተሰብስበው ወደአንቺ ይመጣሉ፤ ወንዶች ልጆችሽ ከሩቅ ይመጣሉ፤ ሴቶች ልጆችሽንም በጫንቃ ላይ ይሸከሙአቸዋል፤ በዚያን ጊዜ የባሕሩ በረከት ወደአንቺ ስለሚመለስ፣ የአሕዛብም ብልጥግና ወደአንቺ ስለሚመጣ አይተሽ ደስ ይልሻል፤ ልብሽም ይደነቃል፤ ይሰፋማል፤ የግመሎች ብዛት የምድያምና የጌፌር ግመሎች ይሸፍኑሻል፤ ሁሉ ከሳባ ይመጣሉ፤ ወርቅንና ዕጣንን ያመጣሉ፤ የእግዚአብሔርንም ምስጋና ያወራሉ፤ የቄዳር መንጎች ሁሉ ወደአንቺ ይሰበሰባሉ፣ የነባዮትም አውራ በጎች ያገለግሉሻል፤ እኔን ደስ ሊያሰኙ በመሠዊያዬ ላይ ይወጣሉ፤ የክብሬንም ቤት አከብራለሁ።›› (60፡1-7)

ኢትዮጵያ ትወድቅ ይሆናል፤ ግን ያለጥርጥር ትነሣለች፤ በፊትም ወድቃ ተነሥታለችና፤ ኢትዮጵያ ትሰነጠቅ ይሆናል፤ ግን ያለጥርጥር ትገጥማለች፤ በፊትም ተሰንጥቃ ገጥማለችና፤ ለኢትዮጵያ በጎ የማይመኙላት የአየሉ ቢመስሉም የንስሐ ጊዜ ስትሰጣቸው ነው፤ ኢትዮጵያ ዕብሪተኞችንም ትሕትና ታስተምራቸዋለች፤ ዕብሪተኞች ከነዕብሪታቸው በራሳቸው እሳት ቀልጠው እስቲያልቁ ኢትዮጵያ ትእግስትዋ አያልቅም፤ ኢትዮጵያ ትእግስት ነችና።

በበጎ መንፈስ እስከተመራን ድረስ፣ ፍርሃትንና አለመተማመንን፣ ጥላቻን፣ ጠብንና ድብድብን፣ ሊዘሩብን ከሚፈልጉ ርኩሳን መናፍስት ከራቅን ኢትዮጵያችን አትፈርስም፣ የደፈረሰውም ቶሎ ይጠራል።

ምንጭ፡ Mesfin Woldemariam Blog

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Full Width Top, Middle Column

Reader Interactions

Comments

  1. Bereket Tolosa says

    August 28, 2016 11:11 am at 11:11 am

    yes it our responsibility , if once a country cracks it is not easy to make it strong, our naibours somailebis good egample so,

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የጃኖ ስጦታና የዶሮ ፖለቲካ በጎንደር March 10, 2026 09:24 am
  • “አዲሷ” ኢህአፓ፤ ከንፈሯን ቀለም የተቀባች አሳማ February 25, 2026 11:24 am
  • የተንጋደደው የገዱ መልስ February 6, 2026 03:05 pm
  • ሻዕቢያ “አክሱም ገብቶ ወጣቶች በጅምላ ሲረሽን ጸብ ተፋፍሟል …” February 4, 2026 01:15 pm
  • አደራ ጠባቂው የኢሉአባቦር ሕዝብ February 4, 2026 12:14 pm
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን January 28, 2026 09:56 am
  • በአሜሪካ ጥምር ዜግነት እንዲቀር ጥያቄ ቀረበ January 27, 2026 03:05 pm
  • “ከህወሓት፣ ከሻዕቢያ፣ ከግብፅ ሰዎች ጋር ሆኖ እንዴት የአማራን ጥያቄ ማስመለስ ይቻላል?” ኮሎኔል ፈንታው January 25, 2026 04:23 am
  • የኢትዮጵያ አየር ኃይል: ለአፍሪካ ሀገራት የመጀመሪያዎቹን የአየር ኃይል አብራሪዎች ያሰለጠነ ተቋም January 25, 2026 03:50 am
  • የአማረ ሪፖርተር እያደረሰ ያለው የብሔራዊ ደኅንነት አደጋ January 22, 2026 01:56 am
  • የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የማርያምን ማዕረግ ዝቅ አደረገች December 12, 2025 09:27 pm
  • ኢህአፓ: ከነጭ ሽብር ወደ “አዲስ አበባ ትናገር” የጎዳና ሽብር? December 12, 2025 09:11 pm
  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule